• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ይድረስ ለፈጣሪ!

January 10, 2013 09:07 am by Editor 2 Comments

ተጣፈ ተኔ «ወተህ ወርደህ የላብህን ወዝ ትበላለህ» ብለህ ወደ መሬት ከላከው የአዳም የልጅ፤ ልጅ፤ ልጅ፤ ልጅ፤ ልጅ፤ … አንዱ፤ ላንተ በሰማዬ ሰማያት ላለኸው አምላክ::

እነሆ ይችን ደብዳቤ በመልክተኛህ በመላኩ ገብርኤል በኩል ላንተ ስልክ፤ ካገኘህ ለራስህ በእጅህ እንዲሰጥ፤ ካጣህም ለእናትህ ለወላዲት አምላክ፤ እንዲሰጣትና እሷ እንድትሰጥህ አደራ ብዬዋለሁ::

አምላክ ሆይ !
ከጭቃ አድቦልቡለህ የፈጠርከው ሰውን ያህል ጨካኝ ፍጡር አንቱ እያልኩ፤ አንተን አንቱታ በመንፈጌ ከድፍረት እንደማትቆጥርብኝና ቁጣህ እንደማይበረታ አውቃለሁ፤ አንተታዬ የመውደዴና ላንተ ያለኝ የክበር መግለጫ መሆኑን አንተው ታውቃለህና!

ይኸውልህ ጉዳዩ እንዲህ ነው:
ፈጣሪ በጆሮው ላይ ተኝቶ የሕፃናትን ለቅሶ፤ የዕናቶችን ዋይታ፤ ያባቶችን ጣር፤ አልሰማ ብሏል፤ … ሕዝብ መከራው በዝቶ፤ የበደል ገፈቱ ገንፍሎ እየፈሰሰ፤ ዋይታውና ለቅሶው እንደ እሳተ ጎሞራ ላንቃውን ከፍቶ፤ የሰማዩን በር ሲለበልብ፤ ጮኸት በርክቶ፤ ፈጣሪ አልሰማ አለ::

ቤተ መቅደሱ ሲደፈር፤ ጽላቱ ሲቃጠል፤ ገዳማት ሲታረሱ፤ የሰማዕታት መቃብር ሲፈነቀል፤ እሱን ብለው ቅጠል በልተው ለሱ ያደሩ ባህታዊያን፤ በጃቸው መስቀል፤ በቀሚሳቸው ስር ሽጉጥ ባነገቡ ሃሳዊ መሲሃን … ሬሳቸው እንደ ፍሪዳ በቤተ መቅደሱ ሲዘረር፤ ሕዝብ በፀጉሩ ልክ መከራው በርክቶ፤ ችግር አጉቡጦ ሲደልቀው፤ ሆድና ጀርባው በረሃብ ሙጫ ተጣብቆ ሲያቃስት፤ የጎድን አጥንቱን ተደግፎ እየተንገዳገደ ወዳንተ ሲማጠን፤ በውሃ ጥም የደረቀ ምላሱን እየመጠጠ ወዳንተ ሲያንጋጥጥ፤ የነጠተፈ ኩሬ ከመሰሉ ዓይኖቹ ዕንባውን እየጨለፈ ወዳንተ ሲረጭ፤ መሬት እንኳን ቀብጣ፤ አፏን ከፍታ የምትውጠው፤ የድሆችን የደረቀ አጥንትና ጅማት ብቻ ሆኖ፤ ፈጣሪ በዓይኖቹ ማየት ተሳነው፤ እያሉ ያሙሃል::

ምን ማማት ብቻ ! በየመቅረዙ ጠዋትና ማታ ተጎልተው የሚያንሾካሹኩት ይኸንኑ ነው :: አልፎ ተርፎም ተደብቀው የሚያሽሟጥጡህም አልጠፉም፤ እንግዲህ እኔም ተደብቄ አብሬ ከማማህና ከማሽሟጥጥህ ይልቅ ልንገርህ ብዬ ነው፤ ይችን ደብዳቤ ልጥፍልህ የደፈርኩት::

ይኸው ገብሬል ምስክሬ ነው !
እነዚህ ልበ ድፍን የህሊና አልቦዎችና ገንዘብ አምላኩዎች፤ በመጥሃፍ ቅዱስህ ውስጥ ኢትዮጵያ የምትባል የጥቁሮችን ምድር፤ ከ 40 (ከአርባ ጊዜ በላይ) እንደጠቀሰካት እንኳን አይረዱም::

በተለይ፤ በትንቢተ ኤርምያስ ምዕራፍ 13 ቁጥር 23 ኢትዮጵያዊ መልኩን፤ ወይስ ነብር ዝንጉርጉርነትን ይለውጥ ዘንድ ይቻላልን? ያልከው ልቤን ጧፍ ሆኖ ያሞቀዋል፤ እራሴን ቀና፤ ትከሻዬን ከፍ አድርጌ እንድሄድና በኢትዮጵያዊነቴ ኮርቼ፤ እንድኖር ከሚያደርጉኝ ጥቅሶችህ አንዱ ሲሆን፤ … ላንተ ሁሉንም መንገር አያሻም ብዬ ተውኩት እንጂ፤ እኔ ባሪያህ ሁሉንም መደርደር አይገደኝም::

እናማ ይኸውልህ!
«የጠሏችሁን ውደዱ ብትለን » እሺ ብለን ብንወዳቸው እነሱ ጠሉን፤ « ቀኝ ጉንጫችሁን በጥፊ ቢመቷችሁ ግራውን ስጧቸው» ብትለን፤ ግራ ጉንጫችንን ብንሰጣቸው አልበቃ ብሏቸው፤ ሰውነታችንን በጥይት በሳሱት፤ በሳንጃ ዘከዘኩት፤ ተማሪዎች ልጆቻችን ከግድያ ለመዳን ወደ ቤተ መቅደስህ ቢሸሹ ከቤተ መቅደስህ እየጎተቱ ወስደው ለሞትና ለእስር ዳረጓቸው::

ምን ይኸ ብቻ!
ሕፃናት ለባርነት ተሸጡ፤ ሴቶች ልጆቻችን ለዝሙትና ለግርድና ተሰደዱ፤ ወንዶች ልጆቻችን ለአሽከርነት ተዳረጉ፤ በግፍ ብዛት የእናቶች አንጀት ተቋጠረ፤ ያረገዙበትን ማህጸን ረገሙ፤ ያጠቡበት ጡቶቻቸውን ጎንበስ ብለው በምሬት ነከሱ! ጎልማሶች በራሳቸው፤ በወላጆቻቸው፤ በምሽቶቻቸውና በልጆቻቸው ላይ በደረሰው በደል፤ ቁጭትና ንዴታቸው ገንፍሎ፤ መሬቷን በፍም አሎሎ ሊለበልቧት ቀኑ ተቃርቧል፤ በዛን ዕለት ከእሳቱ ወላፈን የሚያመልጡ እነማን ይሆኑ?!

ወይ ጉድ! ለካ ለዚህ ነበር፤ አያቴ ሃዘኑ በዝቶ፤ የዕምነት ዛቢያው ጠሞበት ሲንገዳገድ፤ ባንተ ላይ ያለውን የተደባለቀ ስሜት ሲገልጽ:

«የለህም እንዳልል ይመሻል ይነጋል፤
አለህም እንዳልልህ እንዲህ ይደረጋል፤» ብሎ ያዜመው? ሆሆይ!

ዛሬ ነው የተገለጠልኝ፤ ያኔ ትንሽ ልጅ ስለነበርኩ ልብ አላልኩትም ነበር! ዛሬ እኔ የልጅ ልጁም ልደግመው ምን ቀረኝ ብለህ?! በዕውነቱ ዝምታህ በእጅጉ በዛ፤ ትዕግሥትህ ከልክ አለፈ፤ ሕዝቤ ተሰቃየ፤ ለተፈጸመ ግፍ፤ ፍርድ ከሌለ ተጠያቂነት አይኖርምና ፍርድህ የግድ ይላል፤ የዘሩትን ሙጃ የሚያጭዱበት ቀን መቅረቡን ንገራቸው … ::

ደግሞ «የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው» እያልክ የልብ ልብ ሰተህ አቀበጥካቸው፤ ከበሯቸውን እየደለቁ ጣቶቻቸውን አሹለው ዓይንህን ለመደንቆል የሚዳዳቸው ቀበጦች ፍጡሮችህን አደብ ግዙ በላቸው! በአምሳልህ የተፈጠርን ፍጡራን መሆናችንን እያወቁ፤ እኛን ሲበድሉ አንተን እንደበደሉ መሆናቸውን እንዴት አያውቁም ትላለህ? እነሱ የሚያደርጉትን ሁሉ ልቅም አድርገው ያውቃሉና፤ ፍርዱን ለአባትህ ተውለት::

ቆይ ቆይ የረሳሁት ጥያቄ አለኝ፤ ለመሆኑ መቼ ነው የምትመጣው?! የተወለድክባት ምድር አልናፈቀችህም? አቤት ያንተ ነገር፤ ለሰው ልጅ የሳሳ ልብ እየሰጠህ፤ ለራስህ በድርብ የተሰራ ልብ ነው ያለህ ልበል? እኔ ግን የተወለድኩባት አገሬና ሕዝቤ ይናፍቁኛል፤ የሕዝቤ መከራው መከራዬ፤ ሃዘኑ ሃዘኔ፤ በደሉ በደሌ፤ ስለሆነበኝ ነው ወዳንተ የምጮኸው፤ እናም ጩኸቴን አድምጥ!

የኔ ነገር እረስቼው ሳልነግርህ!
አንተ «ከበጎቼ መሃል አንዷ እንኳን ብትጠፋ እሷን ፍለጋ እሄዳለሁ ብለሃል»፤
እነሆ በጎችህን ጠብቁ ብለህ አደራ የሰጠሃቸው እረኞችህ፤ በጎቻቸውን የትም በትነው ለዚች ምድር ስልጣን እርስ በርሳቸው ሲጎነታተሉ፤ ሲወነጃጀሉ፤ ሲረጋገሙ … አብዛኞቹ በጎችህ በተኩላዎች ተበሉ፤ ብዙዎቹም ከቤተመቅደስህ ፊታቸውን አዞሩ::

እርስ በርሳቸው ይቅር መባባል ያልቻሉ፤ እንዴትስ አርገው ይቅር ማለትን ሊስብኩ፤ ይደፍራሉ? ሠላም፤ ፍቅር፤ መቻቻልን፤ የሚያስተምር ያንተን ቃል መሰበክስ እንዴት ይቻላቸዋል?

እግዚኦ መሃረነ ክርስቶስ!
በእንተ እዚትነ ማርያም መሃረነ ክርስቶስ! እንበል አሥራሁለት፤

የነገሩህን የማትረሳ የለመኑህን የማትነሳ አምላክ ሆይ !
ፍርድህን ሳላይ ብትጠራኝ እንደማልመጣ ካሁኑ ልንገርህ፤ ነገር ግን ፍትህ ለጎደለበት ሕዝቤ ፍርድህን በሰጠህ ማግስት፤ አንተ ሳትጠራኝ እኔው እራሴ መጥቼ በርህን አንኳኳለሁና ጠብቀኝ:: እኔን ቢያሻህ እንደ ሎጥ ሚስት የጨው ሃውልት፤ ከፈለክም በዕቶን እሳት ውስጥ ወርውረህ፤ ልንደድ፤ ልቃጠል፤ ብቻ ሕዝቤን አድን፤ ሕዝቤን መከራ በቃህ በለው፤ የእናቶችን ዕንባ በምህረትህ አብስ፤ የሕፃናትን ለቅሶ በደስታ ለውጥ፤ የአባቶችን የቆሰለ ልብ አሽር፤ በስደት የሚጉላሉ ወገኖቻችንን ወደ ጥቁሯ እየሩሳሌም ወደ አገራቸው ኢትዮጵያ መልስ፤ አገራችንን የፍቅር፤ የሠላም፤ የወንድማማችና የተስፋ ምድር አድርጋት:: ሠርተን የምንኖርባት አገር እንጂ፤ እሷን የምንሸሽ ምድር አታድርጋት::

ጨካኞችን ወደ ልቦናቸው መልስ፤ ይቅር ማለትን አስተምራቸው፤ የታበየ ልቦናቸውን አስተንፍስ፤ ያቄመ ልባቸውን በይቅርታ ሙላው፤ በስስት የታወሩ ዓይኖቻቸውን ከፍተህ አብሮ ማእድ መቅረብን አስተምራቸው::

እነሆ በመጨረሻ:
ይችን ደብዳቤ ላንተ በመጣፌ፤ ለፈጣሪ አሳበቀ ብለው የሚከፋቸው ቢኖሩ፤ ባንተ አምሳል የተፈጠሩ፤ ልበ ድንጋዮችና የተንኮል ጎተራዎች ናቸውና፤ ለወገኖቻቸው የሚራራ ልቦና ለግሳቸው::

በአብ፤ በወልድ፤ በመንፈስ ቅዱስ፤

አሜን!

ተጣፈ በዕለተ ልደቱ ታኅሳስ 29 ቀን 2005 ዓ.ም. (07/01/2013)

(ፎቶ: በጸሃፊው የተላከ)

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions

Reader Interactions

Comments

  1. tefera says

    January 12, 2013 05:06 am at 5:06 am

    Betam teru naw. Hule tafelet.

    Reply
  2. እስከመቼ says

    January 12, 2013 11:41 pm at 11:41 pm

    ከቤተ ክርስትያን የሚመለሱትን መነኮሳት አየኋቸው። እርስ በርሳቸው ይነጋገራሉ። ቤተ ክርስትያኑም አልሄድኩም፤ አነሱንም ቀርቤ አሳልሙኝ አላልኩም። ንግግራቸው ግን ሳበኝ። በተለይም ኢትዮጵያ የሚል ቃል ሲናገሩ ስሰማ ቀንዴ ቆመ። መነኩሴን ደግሞ ፖለቲካ ውስጥ ምን አስገባው ብዬ!
    መቼም ዛሬ ግዜና፤ ኢትዮጵያ ያለ ሁሉ ፖለቲከኛ፤ ኢትዮጵያ ማለት ፖለቲካ ሆኖ የለ! ታዲያ ጠጋ ብዬ በደንብ አዳመጥኳቸው። ደሞ ሰላይ የበዛበትና ሁሉም ነገር የስለላ ጉዳይ ስለሆነ ጠርጣሪው ብዙ ነው። እናማ እንዳይጠረጥሩኝ ብዬ፤ ፊቴን ወዲያ የጀሮዬን ቀንድ ወደነሱ አደረግኩና አዳምጥኳቸው። ያዳመጥኩት ጣመኝ። የበለጠ ተጠጋሁ። ሶስት መነኩሴዎች ነበሩ። በመቅመቆ የቀለመና አደፍ ያለ የመናኝ ልብሳቸውን በመልበሳቸው፤ ከየት እንደመጡና ምን እንደሆኑ ጠርጥሬያለሁ። እኩል ከነሱ ጋር መራመዴን ቀጥያለሁ።
    “እናማ ይኼን ፈጣሪያችንን የሚያማውና የሚለምነው መብዛቱ!” አሉ የመጀመሪያው መነኩሴ።
    “መጣፉ ያለውን እኮ ባያውቁት ነው።” አሉ ሁለተኛው መነኩሴ።
    “እና እኛ ማስተማር አለብን። ለዚህም አይደል የመጣነው!” አሉ ሶስተኛው። ቀጥለውም፤ “መቼም ገዳማችን መመለሻ እማይኖርበት ደርሷል። ግና የኛ ሥራ ሰውን ማዳን ስለሆነ፤ እንመለሳለን ብለን ሳይሆን ማሰብ ያለብን፤ እንደወጣን እንቀራለን ነው። መቼም የሱ ፈቃድ አይታወቅምና፤ ብንሰቃይም፣ ብንገረፍም፣ ብንወቀርም፤ የሥጋችን ጉዳይ ነው።” አሉ።
    ምን ይዘውት የመጡት ነገር አለ ብዬ፤ የጀሮዬን ግድግዳ በደንብ አስልቼ የበለጠ ተጠጋኋቸው። የመጀመሪያው መነኩሴ፤
    “የመጀመሪያው ሥራችን ሰውን የራሱ ኃላፊ እንዲሆን ማስተማር ነው። እሱ ራሱ ተጠያቂ መሆን ያለበትን ጉዳይ ላምላኩ እየሠጠ፤ አምላክ ሁሉን አንተ አድርግልኝ ብሎ መለመኑን ያቁም።” አሉ።
    “አዬ የርስዎ ነገር። የሰው ጉዳይ መቼ ተለወጠና! ያም ለኔ ያም ለኔ እኮ ማለቱ ነው እኛንም አስመርሮን ምነና ያስኬደን። ይኼው በመነንንበት አላስቀምጠን ብሎ ያስቸገረንና መልሶ ወደ መካከላቸው ያስመጣን ይኸው አይደል?” አሉ ሆነተኛው መነኩሴ።
    ይቺን ይወዳል! እኒህ መነኩሴዎች ሰማዩን ሊያርሱት ነው፤ አልኩና ቀንዴን የበለጠ አሾልኩ።
    “በመጣፉ፤” አሉና ሶስተኛው መነኩሴ ጀመሩ። “በመጣፉ ‘እኔ ሁላችሁም ስትመጡልኝ፤ እዚሁ ፍርዳችሁን እሠጣለሁ። ባላችሁበት ግን ተግባራችሁን እመዘግባለሁ እንጂ ጣልቃ አልገባም።’ ብሏል። ታዲያ ይኼንኑ ነው ማስተማር ያለብን። የሰው ልጅ ሁሉም እኩል ነው።” አሉ።
    “አዩ አባታችን!” ሲሉ የመጀመሪያው መነኩሴ ጀመሩ። “ይች ሀገር ብዙ ችግር ደርሶባታል። ሰው እርስ በርሱ እየተላለቀ ነው። አጥፊውና ጠፊው ያንድ ሀገር ሰው ነው። ባንድ እንዲኖሩና ተግተው ሠርተው እንዲከብሩ ጥሩ ሀገር ሠጥቷቸው ነበር። ነገር ግን አንዱ በዳይ ሌላው ተበዳይ ሆኖ ልቅሶ ሀገሯን ሞልቷታል። ታዲያ የነፍሳቸውን እሱ ፍርድ ይሠጣል። ለሥጋቸው ግን፤ እርስ በርሳቸው መነጋገር አለባቸው።” አሉ።
    “ይስሙንጂ!” ጠበቅ ባለ አነጋገር ሁለተኛው መነኩሴ ቀጠሉ። “እርስ በርሳቸው የሚባል ነገር የት አለ። ለኛ ተርፈውን የለ! ተኛ መጥተውብን ይኸው ከገዳማችን ወጣን። ዝም ብለን አናይ እንግዲህ። የነፍስ ቦታችንን የሥጋ አደረጉብን እኮ! እናማ እኛ ዝም እንዴት አንላለን? ሰውን አግጠህ ወደላይ አትይ። በጎንህ ያለው እንዳንተ ሰው ነው። እያልን እናስተምር።” አሉ።
    አንገታቸውን ደፋ አድርገው ሲያዳምጡ የነበሩት ሶስተኛው መነኩሴ፤ “ድንቅ ብለዋል አባታችን። አኛም የወገናችን አካል ነን። ጥቂቶች ብዙኀኑን ሲያጠቁ ዝም ካልን እኛም ያጥቂዎች ወገን ሆንን ማለት ነው። ሰውን የምንነግረው፤ ‘የዴሞክራሲ መብትህን ካምላክህ ስይሆን ከራሰህ እጅ ነው ብለን ማስተማር አለብን።” ሲሉ ሁለተኛው መነኩሴ ከት ብለው ሣቁ።
    “አባቶቼ! እኔ ከናንተ አላውቅም። እስኪ በሞቴ! እንዴት ብለን እኛስ አስተማሪዎች እነሱስ ደግሞ ተማሪዎች ሆነው፤ ከኛ የዴሞክራሲ ትምህርት ይፈልቃል? አምላክስ እንዴት ለሰው የሥጋ ፍላጎት ተጠያቂ ይሆናል?” አሉ።

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የማርያምን ማዕረግ ዝቅ አደረገች December 12, 2025 09:27 pm
  • ኢህአፓ: ከነጭ ሽብር ወደ “አዲስ አበባ ትናገር” የጎዳና ሽብር? December 12, 2025 09:11 pm
  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule