• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

እነ ጃዋር መሐመድና ተቋማቱ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ “ፈጽመናል አልፈጸሙም” በሚል ተካካዱ

August 23, 2020 06:44 pm by Editor Leave a Comment

 “በግል ሐኪሜ ካልሆነ አልታከምም ማለታቸው እንድንጠራጠር አድርጎናል” ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ

“አዕምሮዬን ብስት እንኳን በማላውቀው ሐኪም መነካት አልፈልግም” ተጠርጣሪ አቶ ጃዋር መሐመድ

“ፍርድ ቤት በተደጋጋሚ የሚሰጠው ትዕዛዝ እየተከበረ አይደለም” ተጠርጣሪዎች

“መርህ አክብረን ሁሉንም ነገር በአግባቡ እየፈጸምን ነው” የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን

በተጠረጠሩበት የአመፅ ጥሪ ማድረግ፣ የሰው ሕይወት ማጥፋት፣ የእርስ በርስ ግጭት መፍጠር፣ የንብረት ውድመትና ሌሎችም የወንጀል ድርጊቶች ተጠርጥረው በቁጥጥር ሥር ውለው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የሚገኘው እነ አቶ ጃዋር መሐመድና ሁለቱ የመንግሥት ተቋማት (ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግና ፌዴራል ፖሊስ) የፍርድ ቤት ትዕዛዝ “ፈጽመናልና አልፈጸሙም” በሚል ተካካዱ። ሁለቱ ተከራካሪ ወገኖች “ፈጽሜያለሁና አልፈጸሙም” በሚል ሊተማመኑ ያልቻሉት፣ የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ተረኛ ወንጀል ችሎት ነሐሴ 11 ቀን 2012 ዓ.ም. ከአቶ ጃዋር መሐመድ መታመም ጋር ተያይዞ ሰጥቶት በነበረው ትዕዛዝ ላይ ነው።

ፍርድ ቤቱ ነሐሴ 11 ቀን 2012 ዓ.ም. በነበረው ችሎት ሰጥቶት የነበረው ትዕዛዝ ተጠርጣዎቹ በሙሉ የኮሮና ቫይረስ ምርመራ እንዲያደርጉ፣ አቶ ጃዋር እንዲታከም፣ ከባለቤቱና ከልጁ ጋር የቪዲዮ ኮንፈረንስ ተመቻችቶለት እንዲነጋገርና ተጠርጣሪዎች ካሜራ ባልተገጠመበት ቦታ ሆነው ከጠበቆቻቸው ጋር በነፃነት እንዲነጋገሩ ነበር።

ፍርድ ቤቱ ከአራት ቀናት ቆይታ በኋላ ነሐሴ 14 ቀን 2012 ዓ.ም. ከሰዓት በኋላ እንደተሰየመ (ቀደም ብሎ በነበሩት ችሎቶች ሲሰየሙ የነበሩ ዳኛ ተቀይረዋል) ትዕዛዞቹ መፈጸም አለመፈጸማቸውን ሲያረጋግጥ የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ወንጀል ምርምራ ቢሮ በተወካዩ በኩል ለፍርድ ቤቱ በላከው ደብዳቤ አቶ በቀለ ገርባ፣ አቶ ጃዋር መሐመድ፣ አቶ ሐምዛ አዳነና አቶ ሸምሰዲን ጠሀ የኮሮና ቫይረስ ምርመራ ተደርጎላቸው ነፃ መሆናቸው መረጋገጡን አስታውቋል። ስለሌሎቹ ተጠርጣሪዎች ግን ያለው ነገር የለም።

አቶ ጃዋር በራሱ ወጪ የቪዲዮ ኮንፈረንስ ተዘጋጅቶለት ባለቤቱንና ልጁን አግኝቶ መነጋራቸውንም ፖሊስ ማረጋገጡን ዳኛው ለታዳሚው ተናግረዋል። ሕክምናን በሚመለከት ግን በፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ መሠረት እንደማንኛውም ተጠርጣሪ በፌዴራል ፖሊስ ሪፈራል ሐኪም ቤት እንዲታከም ተጠይቆ “በራሴ ሐኪም ካልሆነ አልታከምም” በማለት ፈቃደኛ አለመሆኑንም የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቢሮ በደብዳቤ ማሳወቁን ፍርድ ቤቱ ገልጿል።

የፌዴራል ፖሊስ በተወካዩ በኩል ለፍርድ ቤቱ የላከውን ደብዳቤ በመቃወም መጀመርያ የተናገረው አቶ ጃዋር ነው። እንደገለጸውም እሱ ካለው የፖለቲካ ተሳትፎ አንፃር ሲደረግበት ከነበረው ከፍተኛ የሆነ የስም ማጥፋት ዘመቻ አንፃር ለሕይወቱ ሥጋት አለው። ምክንያቱንም ለፖሊሶችና ለዓቃቤ ሕግ አቅርቦ በግል ሐኪም እንዲታይ ተስማምተው ነበር። ለጊዜው ሐኪም እንዳልተገኘ ነግረውት የቆየ ቢሆንም፣ ነሐሴ 13 ቀን 2012 ዓ.ም. እነሱ ቢስማሙም በበላይ ኃላፊዎች ትዕዛዝ በግል ሐኪም የመታየቱ ነገር መሰረዙን እንደነገሩት ለፍርድ ቤቱ አስረድቷል። “እኔ በግል ሐኪም ልታይ ያልኩት የመንግሥትን ሐኪም በመናቅና የራሴን ከፍ ለማድረግ ሳይሆን ሥጋት ስላለብኝ ነው፤” ብሏል። በሚንቀሳቀሱበት ጊዜ ከፊትና ከኋላ በተደቀነ መትረየስ ታጅበው የሚንቀሳቀሱት ሥጋት ስላለ እንጂ ጃዋርና በቀለ ያመልጣሉ ተብሎ እንዳልሆነ እንደማሳያ ጠቁሟል።

አቶ ጃዋር እንደገለጸው፣ ነሐሴ 11 ቀን 2012 ዓ.ም. መታመሙን ለፍርድ ቤት ማሳወቁንና በዕለቱም ሲመለስ ሕመሙ ፀንቶበት ሲያስመልሰው ማደሩን ተናግሯል። በዚህ ሁኔታ ላይ እያለ “አላመመውም” የሚል መግለጫ እንደተሰጠበት ጠቁሞ “አዝናለሁ” ብሏል።

እዚህ አገር የእሱን ያህል ጠላት ያለው እንደሌለና ቤቱ በፌዴራል ፖሊስ እየተጠበቀ መሆኑን የተናገረው አቶ ጃዋር፣ ጠላቱ መንግሥት ሳይሆን በመንግሥት ውስጥ ያሉ ሰዎች መሆናቸውን ጠቁሟል። “መድኃኒት ብወስድ ልመረዝና ልገደል ስለምችል እኔ በማላውቀው ሐኪም መታከም አልፈልግም፤” ብሏል። ምግብ ሲበላ ስለሚያስመልሰው መመገብ ማቆሙን አስታውቆ፣ “አዕምሮዬን ብስት እንኳን በማላውቀው ሐኪም መነካት አልፈልግም፤” በማለት የሚናገረው ለሪከርድ እንዲያዝለት መሆኑንም ገልጿል።

አቶ ጃዋር፣ አቶ በቀለ ገርባና አቶ ሐምዛን ጨምሮ ለ14 ተጠርጣሪዎች የቆሙት ጠበቆችም ለፍርድ ቤቱ ባቀረቡ አቤቱታ፣ ፍርድ ቤቱ ሰጥቶት በነበረው ትዕዛዝ መሠረት ደንበኞቻቸውን ለማግኘት በተለይ አቶ ጃዋርና አቶ በቀለን ጨምሮ አራት ተጠርጣሪዎች ታስረው በሚገኙበት የቀድሞ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት በተደጋጋሚ ቢመላለሱም፣ በሚገናኙበት ቦታ ላይ ተገጥሞ የነበረው ካሜራ አለመነሳቱን ተናግረዋል። ካሜራው እንደተነሳ ከፖሊሶች ተደውሎላቸው ተመልሰው የሄዱ ቢሆንም፣ ተጠርጣሪዎቹን ሊያገናኟቸው እንዳልቻሉ ጠቁመው “የፍርድ ቤት ትዕዛዝ አልተከበረም” ብለዋል። ፖሊስ ሲጠየቅ ከሥልጣኑ ውጭ መሆኑን እየገለጹና በሌላ አካል ትዕዛዝ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ እየተጣሰ ባለበት ሁኔታ “ተባብረን በቅንነት ካልሠራን በዚህ ሁኔታ ወደፊት መራመድ አንችልም፤” ብለዋል።

የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቢሮ ተወካይ ለፍርድ ቤቱ በሰጡት ማብራሪያ እንደገለጹት፣ እነ አቶ ጃዋር የታሰሩበት ቦታ (ቢሮው) አዲስ ነው። ካሜራ የተገጠመው ከፍተኛ ዋጋ ያላቸው መጽሐፍት ያሉበት ቤተ መጽሐፍት (ላይብረሪ) ስላለ እሱን ለመጠበቅ እንጂ፣ ጠበቃንና ተጠርጣሪዎችን ለመቆጣጠር እንዳልሆነ አስረድተዋል። ካሜራ የሌለበት ቦታ አመቻችተው መገናኘታቸውንና ይህንንም በማስረጃ ለማረጋገጥ ከተፈለገ ሲገቡ የፈረሙበትን ሰነድ ማቅረብ እንደሚቻል አክለዋል።

ሕክምናን በሚመለከት ተወካዩ መኮንን እንደተናገሩት፣ ማንኛውም በወንጀል ተጠርጥሮ በእስር ላይ የሚገኝ ዜጋ ሕክምና የሚያገኘው በፌዴራል ፖሊስ ሪፈራል ሐኪም ቤት ነው። መንግሥት በጀት በጅቶ የእስረኞችን ሰብዓዊ መብት ባከበረ ሁኔታ ሕክምና እንዲያገኙ እያደረገ ነው። ለዚህ ማሳያ የሚሆኑት አቶ በቀለ ገርባ ሲሆኑ፣ በሐኪም ቤቱ በተደረገላቸው ሕክምና በመልካም ጤንነት ላይ እንደሚገኙም ገልጸዋል። መርሕ እንደሚከበርና ሁሉም ሰው በሕግ ፊት እኩል መሆኑን የጠቆሙት የፌዴራል ፖሊስ ተወካይ መኮንን፣ የተጠርጣሪውን ሰብዓዊ መብት የመጠበቅ ግዴታ እንዳለባቸውና ማንኛውንም ኃላፊነት ተቋሙ እንደሚወስድም ተናግረዋል። አቶ ጃዋር ጤነኛ እንዲሆን እንደሚፈልጉ ነገር ግን ሁሉንም ነገር የሚያደርጉት መርህን አክብረው መሆኑን  አክለዋል።

የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ደግሞ ለፍርድ ቤቱ እንደተናገረው አቶ ጃዋር የሕክምና አቅርቦቱ እያለ “አልፈልግም” ብለዋል። ዓቃቤ ሕግ በግል ሐኪም እንዲታከሙ ወይም ይታከሙ የሚል ትዕዛዝ አልሰጠም። ምክንያቱም የግል ሐኪም ቤትና ሐኪም የሚፈቀድበት የራሱ የሆነ አካሄድ ስላለውና ያንን አልፎ ትዕዛዝ መስጠት ሥልጣንን አላግባብ መጠቀም ስለሚሆን  ተጠያቂነትን ስለሚያመጣ መሆኑን ገልጿል።

አቶ ጃዋር “እኔ በመረጥኩት ሐኪም ብቻ ካልሆነ አልታከምም” ያለው የተጠራ አመፅ ስለነበር (በ12/12/12) ያንን ለማቋቋም መሆኑን ዓቃቤ ሕግ ጠቁሞ፣ በቤተሰቦቻቸው (በእህታቸው) ጭምር “አቶ ጃዋር ተመርዘዋል” እየተባለ ያልሆነ ነገር በድረ ገጾች እየተናፈሰ ከመሆኑ አንፃር “እኛም ታመዋል ወይስ አልታመሙም?” በሚለው እየተጠራጠርን መሆኑን ተናግሯል። በዓለም አቀፍ አሠራር መርህ መሠረት አንድ ታሳሪ ሲታመም ሐኪም ቤት መቅረብ እንዳለበትና እንዴት በመረጠው ሐኪም መታከም እንዳለበት በተቀመጠው መሥፈርት መሠረት፣ አቶ ጃዋርም የማይታከሙበት ምክንያት እንደሌለ ጠቁሞ፣ መንግሥት ባቀረበላቸው ሐኪም ቤትና ሐኪም እንዲታከሙ እንዲተባበሩ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ እንዲሰጥለት ጠይቋል።

አቶ ጃዋር በድጋሚ ባቀረበው አቤቱታ በታሰሩበት ቦታ የተገጠመው ካሜራ አለመነሳቱንና ካሜራ በሌለበት ቦታ ከጠበቆች ጋር እንዲገናኙ እንደሚዘጋጅ ቢነገረውም፣ እንዳልተዘጋጀ ተናግሮ የጠበቆቹን አቤቱታ አጠናክሯል። ሕክምናን በሚመለከት የግል ሕክምና በሚመለከት ለፖሊስም ሆነ ለዓቃቤ ሕግ የተናገረው፣ “ለሕይወቴ ስለሚያሠጋኝ በግል ሐኪሜ ልታይ” እንጂ ሌላ ነገር እንደሌለ በድጋሚ አጽንኦ ሰጥቶ ለፍርድ ቤቱ ገልጿል።

የኦኤምኤን ጋዜጠኛ የነበረው ተጠርጣሪ ጋዜጠኛ መለሰ ድሪብሳ ደግሞ ባቀረበው አቤቱታ እንዳስረዳው፣ ከቤተሰቦቻቸው ጋር እንዲገናኙ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ የሰጠ ቢሆንም ትዕዛዙ አልተፈጸመም። በስልክ እንዲገናኙ የተሰጠው ትዕዛዝም እየተመረጡ ለአንዳንድ እስረኞች እንጂ “ሁሉም ሰው በሕግ ፊት እኩል ነው” የሚለውን መርሕ ባከበረ መልኩ እየተፈጸመ አለመሆኑንም ተናግሯል። ፍርድ ቤቱ ሁሉም ተጠርጣሪዎች የኮሮና ቫይረስ ምርመራ እንዲያደርጉ ትዕዛዝ የሰጠ ቢሆንም ተግባራዊ አለመደረጉን ገልጾ፣ አብረዋቸው ታስረው የነበሩና ሁሉንም ነገር በጋራ ሲጠቀሙ የነበሩ ተጠርጣሪዎች ተመርምረው ቫይረሱ ተገኝቶባቸው ሳለ፣ የፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ተከብሮ ለእነሱም ምርምራ መደረግ እንዳለበትም አመልክቷል። በኮሮና ቫይረስ መያዛቸው የታወቁ ተጠርጣሪዎች አሁን ያሉበት ሁኔታ አሳሳቢ መሆኑን የጠቆመው ተጠርጣሪው ጋዜጠኛ መለሰ፣ ያሉበት ቦታ እንዲስተካከልለትና አስፈላጊው እንክብካቤ እንዲደረግላቸውም ጠይቋል። ምግብ እንደማይገባላቸውም ጠቁሞ፣ የፍርድ ቤት ትዕዛዝ እንዲከበርና ሊደረግላቸው የሚገባ ሁሉ እንዲደረግላቸው ትዕዛዝ እንዲሰጥ ደጋግሞ አመልክቷል።

የግራ ቀኙን ክርክርና አቤቱታ ያዳመጠው የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ተረኛ ወንጀል ችሎት አንድ ተጠርጣሪ ከጠበቆቹ፣ ከሃይማኖት አባቱ፣ ከቤተሰቡ፣ ከጓደኞቹና ከሐኪሙ ጋር የመገናኘት መብት እንዳለው በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 21(2) ሥር መደንገጉንና በአንቀጽ 13 (2) ድንጋጌ መሠረት ተፈጻሚ መሆን እንዳለበትም በመጠቆም፣ አቶ ጃዋር በግል ሐኪማቸው ሕክምና እንዲያገኙ ጥብቅ ትዕዛዝ ሰጥቷል። ጠበቆችና ተጠርጣሪዎችም በሕጉ ድንጋጌ መሠረት ሚስጥራቸው ሊጠበቅ በሚችልበት ቦታ እንዲገናኙ እንዲደረግ በመግለጽ፣ ፌዴራል ፖሊስ ይህንን ሳይፈጽም ቢቀርብ ሕጋዊ ዕርምጃ እንደሚወሰድም አስጠንቅቋል።

ፍርድ ቤቱ ከላይ የተገለጸውን ሒደት ከጨረሰ በኋላ ዓቃቤ ሕግ ያቀረባቸውን በቀዳሚ ምርመራ መዝገብ ላይ የሚመሰክሩለትን ምስክሮች መስማት ጀምሯል። በዕለቱ ከሰዓት በኋላ እስከ 11፡30 ሰዓት ድረስ ሁለት የዓቃቤ ሕግ ምስክሮችን በዝግ ችሎት ሰምቶ እንዳጠናቀቀ ትዕዛዝ ሰጥቷል። ከላይ የተገለጹት ተጠርጣሪዎች ባቀረቧቸው አቤቱታዎች፣ ዓቃቤ ሕግና ፖሊስ የሰጡትን ምላሽ መርምሮ ብይን ለመስጠትና ቀጣይ የዓቃቤ ሕግ ምስክሮችን ለመስማት ለነሐሴ 18 ቀን 2012 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል።

(ታምሩ ጽጌ፤ ሪፖርተር)

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Law, Middle Column Tagged With: chilot, jawar, jawar massacre, ችሎት

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ጎርጎራ – የመጻዒው ዘመን ሙሽራ! የዉበት ፈርጥ! January 17, 2023 04:18 pm
  • ሁለተኛው መስቀል አደባባይ January 17, 2023 04:13 pm
  • በአቡዳቢ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን January 17, 2023 04:08 pm
  • በንፋስ ስልክ ላፍቶ ስምንት የመሬት ሌቦች ተያዙ January 16, 2023 11:36 am
  • ሺሻ ሲያስጨሱ በተገኙ ሆቴሎችና የምሽት ጭፈራ ቤቶች ላይ እርምጃ ተወሰደ January 16, 2023 08:50 am
  • በሐሰተኛ መታወቂያ የደኅንነት አባል ነን ብለው ሲያጭበረብሩ የነበሩ ተያዙ January 13, 2023 02:03 pm
  • ተሽከርካሪ ወንበር ለትግራይ – “ናይ ኣካል ጉዱኣት ተሽከርካሪ ዘለዎ ወንበር” January 12, 2023 07:17 pm
  • የአማራው ኩራት፣ የኢትዮጵያ ዘብ፣ የትህነግን ቅስም ሰባሪ! January 12, 2023 04:00 pm
  • በኢትዮጵያ ላይ የተጣሉ ማዕቀብ እና ሌሎች አስገዳጅ ሕጎች ሙሉ ለሙሉ ተሰረዙ January 12, 2023 01:52 pm
  • የቻይና ዕዳ ስረዛ “Payday Loan Diplomacy” ወይስ ኢትዮጵያን ያዳነ ተግባር? January 12, 2023 11:00 am
  • የአዲስ አበባ አስተዳደር ከቋንቋ ጋር በተያያዘ ውሳኔ አስተላለፈ January 12, 2023 10:46 am
  • “አምባሳደሩ” የቀድሞ ጌቶቻቸውን እንዲያቋቁሙ ተሾሙ January 11, 2023 03:47 pm
  • መከላከያ ሸኔን የሚዋጉ ሚሊሻዎችን አሠልጥኖ አስመረቀ January 10, 2023 05:37 pm
  • በሰባት ተጠርጣሪዎች ላይ ከባድ የሙስና ወንጀል ክስ ተመሰረተ January 10, 2023 03:36 pm
  • የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አቅጣጫ January 6, 2023 03:26 pm
  • “ከዕብሪቱ አስተንፍሰነዋል” – ኢሳያስ January 2, 2023 07:29 pm
  • [ኢትዮጵያን] “አስታክኮ ኤርትራን መውጋት ለሚፈልግ ኃይል አንተባበርም” January 2, 2023 07:11 pm
  • የ፰ ወር ሕጻንና ጨቅላ ወንዶች የሚደፈሩባት ትግራይ December 14, 2022 02:49 pm
  • “ሰውን ለመርዳት ሰው መሆን ብቻ በቂ ነው” የደጎች አውራ የመቄዶኒያው ቢንያም በለጠ December 14, 2022 09:59 am
  • “የሀብት ምዝገባ መረጃው ለሕዝብ ክፍት ይደረግ “ December 13, 2022 10:30 am
  • የኢትዮጵያ ዓለምአቀፋዊ የሌብነት ደረጃ December 13, 2022 09:42 am
  • ለብረት አቅላጮች ለመሸጥ በኤሌክትሪክ የብረት ማማዎች ስርቆት የ100 ሚሊዮን ብር ኪሳራ December 13, 2022 09:26 am
  • በትግራይ የሰላም ስምምነቱን መሠረት ያደረገ የሽግግር ፍትሕ እንደሚፈጸም ተገለጸ December 13, 2022 09:20 am
  • ከ30 ሚሊየን ብር በላይ በሚሆን ሌብነት የተከሰሱት የደኅንነት መ/ቤት ሠራተኞች ክስ ተመሰረተ December 13, 2022 09:06 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2023 · Goolgule