• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

የፍርድ ቤት የችሎት ውሎ በቀጥታ የቴሌቪዥን ሥርጭት እንዲተላለፍ ምክረ ሐሳብ ቀረበ

August 23, 2020 03:27 am by Editor Leave a Comment

በድምፃዊ ሃጫሉ ሁንዴሳ ሞት ምክንያት ተጠርጥረው በእስር ላይ የሚገኙ ተፅዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦችን ጨምሮ በርካታ ተጠርጣሪዎች የፍርድ ቤት ውሎ በቀጥታ የቴሌቪዥን ሥርጭት ለሕዝብ ተደራሽ እንዲደረግ ምክር ሐሳብ ቀረበ።

የፍርድ ቤት ውሎ በቀጥታ ሥርጭት ለሕዝብ ተደራሽ እንዲሆንና ሌሎች አማራጮችን ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ያቀረበው፣ የኢፌዴሪ የሕዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም ነው።

በተቋሙ ዋና እንባ ጠባቂ እንዳለ ኃይሌ (ዶ/ር) ተፈርሞ ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የተላከው ደብዳቤ እንደሚያስረዳው፣ ለዳኞችና ዓቃቢያነ ሕግ፣ ለተጠርጣሪዎችና ለችሎት ታዳሚዎች ደኅንነትና ጥበቃ አመቺ በሆነ ሰፊ አዳራሽ ችሎት ማስቻልን የመጀመርያ አማራጭ አድርጓል። የፍርድ ቤቱን ውሎ ሁሉም የመንግሥትና የግል፣ የሕትመትና የኤሌክትሮኒክስ መገናኛ አካላት ብቻ እንዲዘግቡት ማድረግና በዘገባዎቻቸው የችሎቱን የምርመራ ሥራ በሚያውኩ ወይም በሚያደናቅፉ፣ የችሎቱን ነፃነትና ገለልተኛነት ጥያቄ ውስጥ እንዲገባ በሚያደርጉ ትክክለኛ ያልሆነ ዘገባን በማያሠራጩት ላይ ሕጋዊ ዕርምጃ በመውሰድ ለሕዝብ ሚዛኑን የጠበቀ መረጃ እንዲቀርብ ተቋሙ ሁለተኛ አማራጭ አድርጎ አቅርቧል። ይህ የማይሆን ከሆነ ግን በአንድ ወገን በመንግሥትና በግል የኤሌክትሮኒክስ መገናኛ ብዙኃን በሌላ በኩል በመንግሥትና በግል የሕትመት መገናኛ ብዙኃን መካከል የጨረታ ውድድር አድርጎ፣ አሸናፊው ሚዲያ በቀጥታ ሥርጭት የፍርድ ቤት ውሎ ለሕዝብ ተደራሽ እንዲደረግ ሦስተኛ ምክረ ሐሳቡን አቅርቧል። በችሎት ተገኝተው የፍርድ ቤት ውሎን መከታተል ለሚፈልጉም ደግሞ በፕላዝማ ቴሌቪዥን ተደራሽ ማድረግም ሌላው አማራጭ መሆኑንም እንባ ጠባቂ ተቋም አክሏል።

የሕዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም ስለዴሞክራሲ ሥርዓት አሠራር እንዳብራራው፣ ግልጽ የሆነ የመንግሥት አሠራርና ተጠያቂነት የዴሞክራሲ ሥርዓት መገለጫ ነው። ግልጽ የሥልጣን ክፍፍል ባለባቸው ዴሞክራሲያዊ አገሮች ደግሞ ነፃነቱ የተጠበቀ፣ የግልጽነትና የተያቂነት አሠራር የተላበሰ የዳኝነት አካል (ፍርድ ቤት) መኖር፣ የሕግ የበላይነትን ለማረጋገጥና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመገንባት እንደ ቁልፍ መሣሪያ ተደርጎ እንደሚቆጠር ጠቁሟል። የፍርድ ቤቶች የግልጽነትና የተጠያቂነት መገለጫ ተደርገው ከሚወሰዱት መካከል፣ በግልጽ ችሎት ማስቻልና በምክንያት የተደገፉ ውሳኔዎችን ለሕዝብ ተደራሽ ማድረግ መሆኑንም ገልጿል። ከመዝገብ መክፈት እስከ ፍርድ አፈጻጸም ያለው የፍርድ ቤቶች የዳኝነት አሰጣጥ አሠራር፣ በአደባባይ በግልጽ ችሎት የሚከናወን መሆኑን ከማንኛውም ተቋም በላይ በባህሪው፣ ለግልጽነትና ለተጠያቂነት የተጋለጠ ተቋም እንደሚያደርገውም አክሏል።

በሕገ መንግሥቱ እንደተመለከተው ፍርድ ቤቶች ከሦስቱ የመንግሥት አካላት አንዱ መሆኑን ያስታወሰው እንባ ጠባቂ ተቋም፣ በዜጎች ላይ ሊወሰን የሚገባን ጉዳይ ለነፃና ገለልተኛ ፍርድ ቤት የማቅረብና ውሳኔ ወይም ፍርድ የማግኘት መብት፣ የፍርድ ቤቶችን የፍርድ ሒደትና ውሳኔ አስመልክቶ መረጃ የመጠየቅ፣ የማግኘትና የማሠራጨት ነፃነት፣ በሕገ መንግሥቱ ዕውቅና የተሰጠ መሆኑን ጠቁሟል። ፍርድ ቤቶችም ሕግ የመተርጎም ኃላፊነታቸውን ከማንኛውም የመንግሥት አካል፣ ባለሥልጣንም ይሁን  ወገን ጫናና ተፅዕኖ ነፃ ሆነው በተከራካሪ ወገኖች የሚነሱ፣ የሕግና ፍሬ ነገር ክርክሮችን፣ ሕግንና ሕግን ብቻ መሠረት አድርገው፣ ሉዓላዊ የሥልጣን ባለቤት ለሆነው ሕዝብ ግልጽ በሆነ መንገድና በተጠያቂነት መንፈስ የማከናወን ተቋማዊና የሙያ ኃላፊነት እንዳለባቸው አጽንኦት ሰጥቷል።

የፍርድ ቤቶች የፍርድ ሒደት እንዴትና በምን አግባብ ለሕዝብ ግልጽ በሆነ መልኩ መከናወን እንዳለበት፣ በፌዴራል ፍርድ ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅና በመረጃ ነፃነት አዋጅ፣ እንዲሁም በወንጀል ሕግ ድንጋጌዎች በግልጽ መደንገጉን ተቋሙ አስታውሷል። የተጠርጣሪ የወንጀል ክስና የፍርድ ሒደትን አስመልክቶ መረጃን ለሕዝብ ይፋ ማድረግ፣ የወንጀል ክሱን የሚያሰናክል፣ ፍትሕን የሚያጨናግፍ፣ የፍርድ ሒደቱን ሚዛናዊነት ወይም ገለልተኛነት የሚያዛባ ካልሆነ በስተቀር ማንኛውም መረጃ ለሕዝብ ሊቀርብ እንደሚገባ ተናግሯል። ለሕዝብ፣ ለሰላምና ፀጥታ አስጊ ወይም ለሕዝብ መልካም ፀባይ ወይም ግብረገብነት አስፈላጊ ካልሆነ በስተቀር ማንኛውም የፍርድ ሒደትና የፍሬ ነገር ክርክር ለማንኛውም ሰው ግልጽ በሆነ ችሎት መታየት እንዳለበት በአዋጅ ቁጥር 590/2000 አንቀጽ (21) እና በአዋጅ ቁጥር 25/1988 አንቀጽ (25 እና 26) መደንገጉንም ተቋሙ አስታውቋል።

ፍርድ ቤት ውሳኔ ሲወስን፣ ሊወስን የሚገባውን የሕግና የፍሬ ነገር ክርክርና የፍርድ ሒደትን ለሕዝብ ግልጽ በሆነ ችሎት የማስቻል መሠረታዊ ዓላማ፣ በውስን ክልከላና በሰፊ ግልፀኝነት መርህ፣ የፍርድ ቤቶችን የፍርድ ሒደትና ውሳኔ ሉዓላዊ የሥልጣን ባለቤት የሆነው  ሕዝብ ወቅታዊና ትክክለኛ መረጃ የማግኘትና የማሠራጨት መብትን ተግባራዊነት፣ የችሎቱ ነፃ፣ ገለልተኛና ፍትሐዊ የፍርድ ሒደት ላይ የሕዝብን የመወሰን አቅም ማጎልበት መሆኑንም ተቋሙ አስታውቋል። የወንጀል ጉዳይ የፍርድ ሒደት በግልጽ ችሎት ማስቻል ወንጀል ያልፈጸሙ ሌሎች ዜጎች ከመሰል የወንጀል ድርጊት እንዲቆጠቡ በማስተማር ረገድ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑንም አክሏል። በአጠቃላይ የፍርድ ሒደት በግልጽነትና ተጠያቂነት ስለመከናወኑ ለሕዝብ መረጃ በማቅረብ ነፃና ገለልተኛ የመገናኛ ብዙኃን የአንበሳውን ድርሻ እንደሚይዙም እንባ ጠባቂ ተቋም ገልጿል።

በግልጽ የፍርድ ቤቶች አሠራርና ተጠያቂነት ወይም መረጃ የማግኘትና የማሠራጨት መብት ተጠቅሞ የችሎትን ነፃ፣ ገለልተኛና ፍትሐዊ የፍርድ ሒደትን ሕጋዊ ባልሆነ መንገድ አደጋ ላይ መጣል የተከለከለ መሆኑን ጠቁሞ፣ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ በንግግር፣ በሕትመት ወይም በሌላ መንገድ ችሎቶችን ወይም የፍርድ ሒደትን ካወከ ወይም በሌላ ካደናቀፈ በወንጀል ሕግ አንቀጽ ከ449 እስከ አንቀጽ 451 ለተቀመጠው ድንጋጌ መሠረት በወንጀል ተጠያቂ እንደሚሆንም አስታውቋል።

የድምፃዊ ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያን ምክንያት በማድረግ በደረሰው የሕይወትና የንብረት ውድመት ተጠርጥረው ታዋቂ ግለሰቦች፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና አባላትን ጨምሮ በርካታ ሰዎች በሕግ ቁጥጥር ስር መዋላቸውንና ጉዳያቸው በግልጽ ችሎት እየተካሄደ መሆኑን የጠቆመው እንባ ጠባቂ ተቋም፣ ነገር ግን አንዳንድ ተጠርጣሪዎች  የችሎት ውሎን ለመዘገብ በፍርድ ቤት የሚገኙት የመንግሥት የመገናኛ ብዙኃን ብቻ መሆናቸውን እየገለጹ መሆኑን ተናግሯል። እነሱም ለሕዝብ ይፋ የሚያደርጉት መረጃ የመርማሪ ፖሊስን የምርመራ ውጤትና የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ ብቻ መሆኑንና ይህም ሚዛናዊነት የጎደለው ዘገባ መሆኑን መግለጻቸውን አክሏል። በመሆኑም ተጠርጣሪዎቹ የችሎቱን ውሎ የሚዘግቡና የሚፈልጓቸው ሚዲያዎች እንዲገቡ ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው ለፍርድ ቤቱ ቅሬታ ማቅረባቸውንም ተቋሙ ገልጿል። የድምፃዊውን ግድያ ተከትሎ በአንዳንድ የክልል ከተሞች በደረሰው የሰውና የንብረት ጉዳት፣ በርካታ ታዋቂ ግለሰቦች፣ ተፎካካሪ የፖለቲካ አመራሮችና አባላቶች፣ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች መታሰራቸውን አስታውሶ፣ ድርጊቱ ተራ ወንጀል ሳይሆን በተቀነባበረ መንገድ አገርን ለማፍረስ፣ አንድነትን ለመበታተንና የሕዝቦችን አብሮነት አደጋ ላይ ለመጣል የተፈጸመ ከባድ ወንጀልና ከባድ የሰብዓዊ መብት ጥሰት መሆኑን በሁሉም ሚዲያ ለሕዝብ ጆሮ  እንዲደርስ መደረጉንም ተቋሙ አብራርቷል።

ከፖሊስ የምርመራ ውጤት ጀምሮ ያለውን የፍርድ ሒደትና የመጨረሻ ውሳኔ በችሎት በአካል ተገኝቶ መከታተል፣ መዘገብና ሚዛናዊ መረጃ እንዲቀርብለት የሚፈልገው ዜጋ ቁጥር እጅግ በጣም ከፍተኛ ሊሆን እንደሚችል መገመት ቀላል መሆኑንም ተቋሙ ጠቁሟል። ከወቅታዊው የኮሮና ችግርና የማስቻያ አዳራሽ ችግር አንፃር ፍርድ ቤቶች በችሎት ተገኝቶ የፍርድ ቤቱን ውሎ ለመከታተል የሚፈልገውን ሁሉ ማስተናገድ እንደሚከብድና እንደማይቻል ተቋሙ እንደሚረዳ ጠቁሞ፣ የሰጣቸውን ምክረ ሐሳቦች (አማራጮች) በመጠቀም ፍርድ ቤቱ እንዲያስተካክል ጠይቋል። የችሎት ውሎ ሒደት ከሳሽና ተከሳሽ ለችሎቱ የሚያቀርቡትን በማስረጃ የተደገፈ ክርክር፣ ዳኞች በችሎት የሚሰጡትን ትዕዛዝና ውሳኔ እንደሚያካትት ገልጾ፣ ሚዛናዊ መረጃ የማግኘትና የማሠራጨት ነፃነት በዘር፣ በቋንቋ፣ በቀለምና በዜግነት ልዩነት ሳይደረግ ለማንኛውም ሕጋዊ ሰው የተሰጠ ሕገ መንግሥታዊና የተፈጥሮ ሕግ መሆኑን አስረድቷል። በመሆኑም የችሎቱን ውሎ ሊዘግቡ ፍርድ ቤት የተገኙትን ገሚሶቹን ከልክሎ ገሚሶቹን ማስገባት በሰዎች መካከል ሕጋዊ ያልሆነ ልዩነት እንዲፈጠር ምቹ ሁኔታ እንዳይፈጠር፣ በችሎትም አሠራር ላይ የነፃነትና ገለልተኛነት ጥያቄ እንዳያስነሳ ፍርድ ቤቱ በትኩረት ሊያጤነው እንደሚገባ የሕዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም አሳስቧል። (ታምሩ ጽጌ፤ ሪፖርተር)

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Law, Middle Column Tagged With: chilot, jawar massacre, live court transmission, ችሎት

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ሤራ አክሻፊው ጎንደር ለሦስተኛ ጊዜ ታሪክ ሠራ May 10, 2023 09:25 am
  • ማር በከፍተኛ ደረጃ የኮንትሮባንድ ሰለባ ሆኗል May 9, 2023 09:24 am
  • ኦነግ በኦሮሚያ ሪፈረንደም እንዲካሄድ መጠየቁ ለሰላም ንግግሩ ዕንቅፋት ሆነ May 4, 2023 01:12 am
  • መረጃ ቲቪ ያጋራው አሳሳች መረጃ May 2, 2023 12:37 pm
  • “ከፈጣሪ በታች መከላከያ የሁላችን ዋስ ጠበቃ ነው፤ ትልቅ ይቅርታ እንጠይቃለን” April 13, 2023 10:19 am
  • በትግራይ የ”ልጆቻችን የት ናቸው?” ጥያቄ እየተሰማ ነው April 13, 2023 08:56 am
  • በትህነግ የፈረሰው የአክሱም ኤርፖርት ያስከተለው ዘርፈብዙ ኪሣራ April 13, 2023 03:21 am
  • “የከተማው ነዋሪ በመሰላቸቱ ተፈናቃዮች ከፍተኛ የምግብ ችግር” ገጥሟቸዋል April 12, 2023 09:23 am
  • ከዕድሜ ልክ እስከ 20 ዓመት ቅጣት ተበይኖባቸዋል April 11, 2023 02:58 pm
  • የኡጋንዳ የክልሎች ሚኒስትር በቆርቆሮ ሌብነት ተጠርጥረው ታሰሩ April 10, 2023 03:59 pm
  • ታከለ ከተነሳ በኋላ የመዐድን ሌቦች እየተያዙ ነው April 6, 2023 02:53 pm
  • አገር ለማተራመስ ያለመ የምሁራን፣ የሚዲያ ባለቤቶችና አክቲቪስቶች ህቡዕ ቡድን ተያዘ April 4, 2023 10:07 am
  • በ10 ዓመት ውስጥ ከ44 ቢሊየን ዶላር በላይ ሸሽቷል April 4, 2023 09:26 am
  • አየር ጨብጦ አሁን ያለውን መንግሥት ከሥልጣን ልቀቁ አይሆንም March 29, 2023 09:47 am
  • ሦስት ትውልድ የበላ የሐሰት ትርክት! March 23, 2023 11:59 am
  • “ሽብርተኝነቱን ማንሳቱ በትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ለማቋቋም ይረዳል” – ዶ/ር ጌዲዮን March 22, 2023 05:05 pm
  • አስነዋሪ ተግባር ሲፈጸምባቸው የነበሩ የምሽት ክለቦች ተዘጉ March 22, 2023 12:57 pm
  • ህወሓትን ከሽብርተኝነት እንዲሰረዝ የወሰናችሁ ሁሉ ተጠያቂዎች ናችሁ – ኢዜማ March 22, 2023 12:06 pm
  • የኡጋንዳ ፓርላማ የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነትን በእስር የሚያስቀጣ ወንጀል የሚያደርግ ረቂቅ ሕግ አጸደቀ March 22, 2023 12:44 am
  • በጌታቸው ምርጫ ማግስት በትግራይ ሕዝባዊ ዐመፅ ተጀመረ March 21, 2023 11:01 pm
  • በትግራይ ሥልጣንና ንጉሥ ፈጣሪነት ከአድዋ ወደ ራያ ተሻገረ March 19, 2023 03:45 am
  • ኤርሚያስ ከጌታቸው ረዳ ጋር ምሥጢራዊ የስልክ ግንኙነት ነበረው March 19, 2023 02:44 am
  • እየተገባደደ ያለው የምስራቅ አፍሪቃ የትራንስፖርት ኮሪደርና ለውጥ የናፈቃት ኤርትራ March 15, 2023 04:44 pm
  • በባዶ እግር በሮም አበበን ለመድገም March 15, 2023 01:40 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2023 · Goolgule