• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

“ተጠርጣሪዎቹ” እነ ጃዋር “ተከሳሽ” ሊባሉ ነው

September 10, 2020 09:07 am by Editor 1 Comment

እነ ጃዋር መሐመድ መንግሥትን ኮንነው የፍትሕ ተቋማትንና ፍርድ ቤትን አመሠገኑ

ዓቃቤ ሕግ ክስ መሥርቶ እንዲቀርብ ትዕዛዝ ተሰጠ

በድምፃዊ ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያ ማግሥት ከሰኔ 23 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ ላለፉት 71 ቀናት በእስር ላይ ያሉት እነ አቶ ጃዋር መሐመድ የጊዜ ቀጠሮና የቅድመ ምርመራ የፍርድ ቤት ሒደቶች መጠናቀቃቸውንና የምርመራ መዝገቡ መዘጋቱን አስመልክቶ፣ “ያለ ጥፋታችን እንድንታሰር አድርጎናል” ያሉትን መንግሥትን ኮንነው የፍትሕ ተቋማትንና ፍርድ ቤትን አመሠገኑ።

ተጠርጣሪዎቹ ቅሬታቸውንና ምሥጋናቸውን የገለጹት ከሰኔ 24 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ የጊዜ ቀጠሮ ችሎቱን ሒደት ሲያይ የነበረው የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ወንጀል ችሎት፣ ሰኞ ጳጉሜን 2 ቀን 2012 ዓ.ም. በምርመራ መዝገቡ ላይ የተለያዩ ትዕዛዞችን ሰጥቶ ሲዘጋ በሰጡት አስተያየት ነው።

አቶ ጃዋር መሐመድ አስተያየት መስጠት እንደሚፈልግ ለፍርድ ቤቱ ገልጾ ሲፈቀድለት እንደተናገረው፣ ሲታገሉ የነበረው የፍትሕ ሥርዓቱ እንዲስተካከል ነበር። አሁን በታሰሩበት ወቅት ባዩት የፍርድ ቤት ሒደት ተስፋ ስላገኙ ደስተኞች ነን ብሏል። ይህ በፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት የታየው መሻሻል እስከ ወረዳ ፍርድ ቤቶች እንዲተገበር መሠራት አለበት ብሎ፣ “ያላችሁበትን ጫና እናውቃለን፣ ለእኛም ያሳያችሁንን ክብር ዓይተናል፣ እናመሠግናለን፤” ሲል ተናግሯል።

ዳኞች ለሕግና ለሕገ መንግሥቱ ብቻ ታማኝ ሆነው ያለ ማንም ጣልቃ ገብነት እንዲሠሩም አደራ ብሏል። ለሁሉም ተጠርጣሪዎች የፌዴራል ፖሊስ አባላት ላደረጉላቸው እንክብካቤ አክብሮትና ጥበቃ እንደሚያመሠግኑ የገለጸው ተጠርጣሪ አቶ ጃዋር ጠበቆቻቸው ሳይጠሯቸውና ሳያውቋቸው ስላደረጉላቸው የሕግ ድጋፍ ምሥጋና አቅርቧል።

መንግሥት ያሰራቸው ሰርቀው፣ ገድለው ወይም ደፍረው ሳይሆን በፖለቲካ አቋማቸው ስለተጣሉና ሥጋት ስለሆኑበት መሆኑን የገለጸው አቶ ጃዋር፣ ዜጎችን ወይም የፖለቲካ ተቃናቃኞችን በማሰር፣ በመግደል ወይም በማባረር የተገነባ አገር እንደሌለ ጠቁሞ፣ የፍትሕ ሥርዓቱን በመጠቀም የፖለቲካ ባላንጣ ለማስወገድ ጥረት ማድረግ የትም እንደማያደርስ ተናግሯል። እንደ ኦሮሞ ሕዝብ የታሰረና የተገደለ ሕዝብ እንደሌለና በድምፃዊ ሃጫሉ ግድያ እንኳን በመቶ ሺሕ የሚቆጠሩ ሰዎች በእስር ላይ መሆናቸውን አክሏል።

“በመግደልና በማሰር ለውጥ የሚመጣ ቢሆን ኖሮ የት በተደረሰ” ያለው አቶ ጃዋር መግደልና ማሰር አገር እንደሚያፈርስና እንደሚጎዳ፣ ልማትም ሆነ ብልፅግና ሊመጣ ስለማይችል አዋጭ የሚሆነው በልዩነቶች ዙሪያ ቁጭ ብሎ መወያየት መሆኑን ጠቁሟል። ሕዝብና አገር እንዲኖሩ ከተፈለገ ፍትሕን ማክበር አማራጭ የሌለው ነገር መሆኑን በመጠቆም፣ ዳኞችም ቢሆኑ ለሕጉና ለሚለብሱት ጋወን ታማኝ ሆነው እንዲሠሩ አደራውን አስተላልፏል።

አቶ በቀለ ገርባም ተመሳሳይ ምሥጋና ለፍትሕ ተቋማትና ለፍርድ ቤቱ በማቅረብ፣ እሳቸው ቀደም ብሎ በነበረው የአገር አመራር ወይም ሥርዓት ውስጥም በእስር ማሳለፋቸውንና ችሎቶች ጭፈራ ቤት የሆኑበት፣ መሳቂና መሳለቂያ እንደነበሩ አስታውሰው፣ አሁን ግን ያ በመቅረቱ የተሻለ የፍርድ ቤት ሥራና ችሎት በማየታቸው ቆመው ማመሥገን እንደሚፈልጉ ተናግረዋል። “ክብር ለሰጠ ክብር መስጠት ያስፈልጋል” ያሉት አቶ በቀለ ለፌዴራል ፖሊስ አባላት፣ ለዓቃቢያነ ሕግና ለፍርድ ቤቱ ክብር እንዳላቸው ገልጸዋል።

የዋስትና መብትን በሚመለከት የሚገርማቸው ነገር ቢኖር ሲከሰሱበት የቆዩበት የወንጀል ሕግ አንቀጽ 241 ወይም ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግታዊ ሥርዓቱ በሚፃረር መንገድ፣ በቀጥታም ይሁን በእጅ አዙር የአገሪቱ አንድነት እንዲፈርስ. . . የሚል ድንጋጌ በመጥቀስ ዋስትና እንዳይፈቀድላቸው መደረጉ መሆኑን ጠቅሰዋል።

ይህ የሕግ ድንጋጌ ከአሥር እስከ 25 ዓመታት ወይም ነገሩ ሲከብድ እስከ ዕድሜ ልክና ሞት ድረስ ያስቀጣል ስለሚል፣ ተጠርጣሪን የዋስ መብት ለመከልከል ይጠቀሙበት እንደነበር አክለዋል። አቶ በቀለ አክለው እንደገለጹት አሁን ደግሞ የወንጀል ሕግ አንቀጽ 238 ድንጋጌን በመጥቀስ ወይም በሕገ መንግሥትና ሕገ መንግሥት ሥርዓት ላይ የሚደረግ የወንጀል ድርጊት ማለትም በኃይል፣ በዛቻ፣ በአድማ ወይም ሕገወጥ በሆነ በማናቸውም መንገድ በማሰብ የፌዴራል ወይም የክልልን ሕገ መንግሥት የተቋቋመን ሥርዓት የማፍረስ የወንጀል ድርጊትን የሚያቋቁመው ድንጋጌ በመጥቀስ፣ የዋስትና መብታቸው መገደቡ የሕጉን ዓላማ ያልተከተለ አካሄድ መሆኑን ተናግረዋል።

የሕጉ ዓላማ መሆን ያለበት ተጠርጣሪውን ወይም ተከሳሹን በሚጠቅም ሁኔታ መተርጎም ሲገባ እየተደረገ ያለው የተገላቢጦሽ መሆኑንም አክለዋል። በመሆኑም ነፃነታቸውን፣ አገራቸውን፣ ሀብታቸውንና ቤተሰባቸውን እንዳያጡ የፍትሕ አካላት ትክክለኛውንና ሕጉና ሕጉን ብቻ መተግበር እንዳለባቸውም ጠይቀዋል። ተቋማትን እያፈረሱ መሄድ አደጋ ስለሆነ አገርን ለማልማት ከተፈለገ፣ “ሁላችንም የድርሻችንን እንድንወጣ መደረግ አለበት” ብለዋል። በአገር ጉዳይ ቁጭ ብሎ መነጋገርና መመካከር እንጂ እስራት ምንም እንደማይፈይድ ተናግረዋል። በቆዩባቸው የእስር ቀናት የፍትሕ አካላት ላደረጉላቸው ሁሉ “እናመሠግናለን፣ እግዚአብሔር ይስጥልን” ብለዋል።

ፍርድ ቤቱ በዕለቱ ቀጠሮ ይዞ የነበረው ዓቃቤ ሕግ በቅድመ ምርመራ መዝገብ የሚያሰማቸውን ምስክሮች (ከ15ቱ አሥሩን አስመስክሮ) አሰምቶ ማጠናቀቁን በመግለጽ፣ የክስ መመሥረቻ ጊዜ በወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ሥነ ሥርዓት አንቀጽ 109 ድንጋጌ መሠረት 15 ቀናት እንዲሰጠው ባቀረበው ጥያቄ ላይ የተነሳውን ተቃውሞና በተጠየቀው የዋስትና መብት ላይ ብይን ለመስጠት ነበር።

ፍርድ ቤቱ ነሐሴ 29 ቀን 2012 ዓ.ም. ባስቻለው ችሎት አቶ በቀለና አቶ ጃዋር ምንም እንኳን ለየብቻቸው የታሰሩ ቢሆንም፣ እንዲገናኙ ወይም እንዲቀላቀሉ የሰጠው ትዕዛዝ ስለመፈጸሙ ሲጠይቅ ተጠርጣሪዎች እንዳልተፈጸመ ተናግረዋል። ለምን እንዳልተፈጸመ የተጠየቁት በፌዴራል ፖሊስ የእስረኛ አስተዳደር ክፍል ተወካይ በሰጡት ምላሽ፣ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ ለአለቃቸው ማስተላለፋቸውን ተናግረው ለምን እንዳልተፈጸመ ግን መረጃ እንደሌላቸው አስረድተዋል።

የተጠርጣሪ ጠበቆች ከደንበኞቻቸው ጋር እንዲገናኙ የተፈቀደላቸው ጊዜ አጭር መሆኑን ጠቁመው ያንንም ቢሆን በአግባቡ መጠቀም እንዳልቻሉ ላቀረቡት አቤቱታ፣ የፌዴራል ፖሊስ ተወካዩዋ በሳምንት ሦስት ጊዜ እንዲገናኙ በተባለው መሠረት እየሠሩ መሆኑንና በመካከር በቀጣይ ጠዋትና ከሰዓት ሙሉ ቀን የሚያገኙበትን አሠራር መፍጠር እንደሚቻል ተናግረዋል። ጠበቆቹም በተወካይዋ ምላሽ ተስማምተዋል።

አቶ ጃዋርና አቶ በቀለ እንዲገናኙ እንዲደረግ የተሰጠው ትዕዛዝ ለምን እንዳልተፈጸመ የፌዴራል ፖሊስ ተወካይዋ በግልጽ እንዲያብራሩ ፍርድ ቤቱ በድጋሚ ሲጠይቅ፣ አቶ ጃዋር በመሀል በሰጠው አስተያየት አባላቱ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ ለመፈጸም እንዳይችሉ የሚያደርግ ጣልቃ ገብነት መኖሩንና ከእነሱ በላይ መሆኑን ተናግሯል። የዚህ አገር የፍርድ ቤት ትዕዛዝን መፈጸም ይቻላል ወይስ አይቻልም የሚለውን ለማረጋገጥ እንጂ፣ ከፖሊስ አባላቱ በላይ መሆኑንም አክሏል። የፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ ይከበራል ወይስ አይከበርም የሚለውን ለማወቅና ፍርድ ቤቱ እንዲረዳው ለማድረግ ያህል ጥያቄውን ማንሳቱንም ጠቁሟል።

ፍርድ ቤቱ ዓቃቤ ሕግ የክስ መመሥረቻ ጊዜ በማለት የጠየቀው 15 ቀናት “ሊፈቀድ ይገባል ወይስ አይገባም” የሚለውን ጭብጥ በመያዝ ከተገቢው የሕግ ድንጋጌ አንፃር በመመርመር ብይን መስጠቱን ተናግረዋል። እንደገለጸውም በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 19(4)  ድንጋጌ መሠረት በቁጥጥር ሥር የዋለ ተጠርጣሪ የተፋጠነ ፍትሕ ማግኝት እንደሚገባው መደንገጉ፣ ይኸው ድንጋጌ ኢትዮጵያ ተቀብላ የሕገ መንግሥቱ አካል ያደረገችው ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎችም የሚያረጋግጡት መሆኑን ዓለም አቀፍ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ድንጋጌ (አይሲሲፒአር) አንቀጽ 9(3) የአፍሪካ ሰብዓዊ መብት ቻርተር አንቀጽ 7(መ) ድንጋጌና ሌሎችም አገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ድንጋጌዎችን በመጥቀስ የተጠርጣሪዎች ሰብዓዊ መብቶች መከበርና የተፋጠነ ፍትሕ የማግኝት መብት እንዳላቸው መደንገጉን ችሎቱ ጠቁሞ፣ የተጠርጣሪ ጠበቆች ያነሱትን የተፋጠነ ፍትሕ የማግኘት ጥያቄ እውነትነት አረጋግጧል።

በሌላ በኩል ዓቃቤ ሕግ የወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ሥርዓት ሕግ አንቀጽ 81(1) ጠቅሶ ያቀረበው የቀዳሚ ምርመራ ሒደት ሕግን የተከተለ መሆኑን አረጋግጦ በአንቀጽ 38(ለ) ድንጋጌ መሠረትም፣ ዓቃቤ ሕግ ቀዳሚ ምርመራን ለሚመለከተው ፍርድ ቤት የማቅረብ ሥልጣን እንዳለውም አስረድቷል። እሱንም በአንቀጽ 94 ድንጋጌ መሠረት ለሚመለከተው ፍርድ ቤት ማቅረብ እንደሚችል የሕግ ድንጋጌ እንዳለው ጠቁሞ፣ ነገር ግን ክስ የመመሥረቻ ጊዜ 15 ቀናት በአንቀጽ 109 ድንጋጌ መሠረት ሲጠይቅ በአንቀጽ 37 ድንጋጌ መሠረት ምርመራና የቅድመ ምርመራ ምስክርነት በእያንዳንዱ ተጠርጣሪ ላይ መደረጉን ማረጋገጥ አስፈላጊ መሆኑን ገልጿል።

በመሆኑም በእነ አቶ ጃዋር መዝገብ የተካተቱትን 14 ተጠርጣዎች በሚመለከት ፍርድ ቤቱ ሲመረምር በአቶ ሐምዛ አዳነ፣ አቶ ሸምሰዲን ጠሀ፣ አቶ ቦና ትብሌና ጋዜጠኛ መለስ ድሪብሳ ላይ የቀዳሚ ምርመራ ምስክርነት እንዳልተሰጠባቸው ማረጋገጡን ገልጿል። በመሆኑም የቀዳሚ ምርምራ ሲሰማ ከአንድ ወር በላይ ጊዜ ስለወሰደ በእነዚህ ተጠርጣሪዎች ላይ ዓቃቤ ሕግ ከጳጉሜን 2 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ ባሉት አምስት ቀናት ውስጥ ክስ መሥርቶ እንዲቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቷል።

አቶ ጃዋር መሐመድና አቶ በቀለ ገርባን ጨምሮ አሥሩን ተጠርጣሪዎች በሚመለከትም፣ ዓቃቤ ሕግ ምንም እንኳን የቀዳሚ ምርመራ ምስክሮች ሲያሰማባቸው የቆና የወንጀለኛ መቅጫ ሥነ ሥርዓት ሕግ አንቀጽ 109 ድንጋጌን ጠቅሶ 15 ቀናት የክስ መመሥረቻ ጊዜ የጠየቀ ቢሆንም፣ የተጠየቀው ሁሉ ይፈቀዳል ማለት እንዳልሆነ አስረድቷል።

በመሆኑም ዓቃቤ ሕግ በተጠርጣሪዎቹ ላይ ያሰማቸው ምስክሮችን ቃል በሥነ ሥርዓት ሕጉ አንቀጽ 91 ድጋጌ መሠረት የፌዴራል የመጀመርያ ደረጃ ፍርድ ቤት ሬጅስትራር ለሚመለከተው ፍርድ ቤት እንዲልክና ዓቃቤ ሕግም ተጠርጣሪዎቹ ከሰኔ 23 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ላይ መሆናቸውን ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ እስከ መስከረም 8 ቀን 2013 ዓ.ም. ድረስ ክስ መሥርቶ መቅረብ እንዳለበት ትዕዛዝ ሰጥቷል።

ዓቃቤ ሕግ በተሰጠው ጊዜ ውስጥ ክስ የሚመሠርት ከሆነ ተጠርጣሪዎች በሚከሰሱበት የወንጀል ድርጊት የሚጠቀሱት የወንጀል ሕግ ድንጋጌዎች ከ15 ዓመታት በላይ የሚያስቀጡ መሆናቸውን ስለጠቆሙና ፍርድ ቤቱም ስለተቀበለው፣ ተጠርጣሪዎች ያቀረቡትን የዋስትና ጥያቄ ውድቅ ማድረጉንም ፍርድ ቤቱ አስታውቋል።

በመጨረሻም አቶ ጃዋርና አቶ በቀለ እንዲገናኙ የተሰጠው ትዕዛዝ ለምን እንዳልተፈጸመ የፌዴራል ፖሊስ እስረኞች አስተዳደር ኃላፊ ምክንያቱን ገልጸው ከመዝገቡ ጋር እንዲያያይዙ ትዕዛዝ በመስጠት፣ የቀዳሚ ምርመራና የጊዜ ቀጠሮ መዝገቡ መዘጋቱን በማሳወቅ ከሁለት ወራት በላይ የቆየው መዝገብ ተዘግቶ ወደ መዝገብ ቤት መመለሱን አስታውቋል።

(ታምሩ ጽጌ፤ ሪፖርተር)

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Law, Right Column Tagged With: chilot, jawar massacre, ችሎት

Reader Interactions

Comments

  1. GI Haile says

    September 15, 2020 02:51 pm at 2:51 pm

    የሕግ ተቋሙ ትከከለኛውን ስራ ያለ አድልዎ ይሰራል የሚለውን ምስክርነት መስማታችን እራሱ ለአገራችን ተስፋ ነው። የሕግ ተቋም ሪፎርሙ ተግባራዊ መሆኑ ትልቅ ተስፋ ነው። እናመሰግናለን። ኣቶ በቀለና ጀዋር መሃመድ የሰሩት ወንጀል በመረጃ ከቀረበ ከአስራ ኣዐምስት አመት በላይ የሚያሳስር መሆኑ እጅግ ኣስደንጋጭ ደግሞ ከደረሰው አደጋ አንፃር ደግሞ የሞት ፍርድ ፐሚያስከትልም ነው። ከ300 በላይ የሰው ነፍስ የቀጠፈ ንብረት ያወደመ ግርግር በመሆኑ ለነዚህ መሪዎች መልከም ወሬ የለም።

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ከፍተኛ የፋኖ አመራሮች መገደላቸው ተነገረ May 6, 2025 10:40 pm
  • ሃይማኖትን ለተራ የፖለቲካ ሸቀጥ ማዋል ውርደት ነው April 24, 2025 12:43 am
  •  የኬሪያ ኢብራሒም ኑዛዜ “ብትንትናችን ወጥቷል” April 22, 2025 12:08 am
  • ለወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን አመራሮች ወታደራዊ ሥልጠና ተሰጠ April 16, 2025 11:44 pm
  • ዓቅም እንደሌለው የገመገመው ሻዕቢያ ፊቱን ከጦርነት ወደ ዲፕሎማሲ እያዞረ ነው   April 15, 2025 12:32 am
  • “አንድ የፋኖ ተቋም (የእስክንድር) ተመሥርቷል፤ ሌሎቹ ደግሞ እንዲሁ አንድ ተቋም መሥርተው ወደዚህ ይመጡ” አበበ ጢሞ April 11, 2025 12:07 am
  • መለስ (ለገሰ) ዜናዊ – ተዋርዶ ያዋረደን! April 9, 2025 10:28 pm
  • የተከዜ ዘብ: የሉዓላዊነት መጠበቂያ April 8, 2025 11:49 pm
  • አዲስ አበባ አስተዳደር የሪፖርተርን የተዛባ መረጃ ኮነነ፤ ሕጋዊ እርምጃ እወስዳለሁ አለ April 8, 2025 10:06 pm
  • ሀሰተኛውን የሪፖርተር ዘገባ ንግድ ባንክ በጽኑ ተቃወመ፤ እርማትም ጠየቀ April 8, 2025 09:48 pm
  • “ኦሮሚያ ላይ ወይም ሌላ ቦታ ላይ ስታደርገው ከነበረ ትግራይ ወስጥም የማታደርግበት ምንም ምክንያት አይኖርህም” ነው ጌታቸው ረዳ April 7, 2025 10:22 pm
  • “TPLF’s belief in a strong federal government was always tied to its own dominance in Addis Ababa” April 7, 2025 10:15 pm
  • Counter-Video by EBC Challenges EBS Broadcast, Sparks Public Outcry Over Alleged Misinformation March 31, 2025 02:36 am
  • የኤሊያስ መሠረትን ፌክ መረጃ ማን ያጋልጥ? February 19, 2025 06:00 pm
  • አዘርባጃን፡ የሻዕቢያን ሸምቀቆ ማጥበቂያ?! February 19, 2025 12:29 am
  • የአሜሪካ ድምፅ/ቪኦኤ ይዘጋ ተባለ  February 12, 2025 03:37 am
  • የብልፅግና ፓርቲ ሹመኛ ካድሬዎች February 3, 2025 11:07 am
  • ትግሉን የጎዳው የእስክንድር ነጋ አካሄድ February 3, 2025 10:29 am
  • ኤሊያስ መሠረት “ጭምብሉ ዛሬ ወለቀ”፤ ተከፋይ ነው! February 2, 2025 05:32 pm
  • የፋሲል ግንብ እድሳት እንዴት ተካሄደ? የመንጣቱ ምክንያት? January 23, 2025 03:41 pm
  • ታሪካዊዉ የፋሲል ቤተመንግሥት ለምን ነጣ? January 23, 2025 03:04 pm
  • የኢትዮጵያ አየር መንገድ በተወልደ አስተዳደር ዘመን ለተሠራ ስህተት 425ሺ ዶላር ተቀጣ December 14, 2024 01:44 am
  • በትግራይ ከሞትና ከአካላዊ ጉዳት የተረፉት ለስደት ተዳርገዋል November 27, 2024 12:09 pm
  • የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት አሠራሩን እንዲያርም ጥብቅ መመሪያ ተሰጠው November 27, 2024 11:31 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule