
የፌዴሬሽን ምክር ቤት ማክሰኞ ባካሄደው መደበኛ ጉባዔ የፌደራል መንግሥት ከትግራይ ክልል መስተዳድር ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት እንዳያደርግ ውሳኔ አሳለፈ።
ይህ ውሳኔ ሊተላለፍ የቻለው ባለፈው ነሃሴ 30 2012 ዓ.ም የፌዴሬሽን ምክር ቤት አድርጎት በነበረው አስቸኳይ ጉባዔ በትግራይ ክልል የሚካሄደው ምርጫ እንዳልተደረገ፣ እንዳልተፈጸመ እና እንደማይጸና ውሳኔ ማስተላለፉን ተከትሎ ነው።
ውሳኔውን የሚከታተል የህገ መንግስት ጉዳዮች እና የማንነት ጉዳዮች አጣሪ ቋሚ ኮሚቴ ጉዳዩን ሲከታተል ቆይቶ ውሳኔው ባለመፈጸሙ ባዛሬው ዕለት ባደረገው መደበኛ ስብሰባ ነው ይህንን ወሳኔ ሊያሳልፍ ያቻለው።
ምክር ቤቱ በትግራይ ክልል መንግስት ላይ ሶስት ውሳኔዎችን ማሳለፉን ገልጿል።
የመጀመሪያው የትግራይ ክልል ያካሄደውን ኢ-ህገ መንስታዊ ምርጫ ተከትሎ ከተመሰረቱ የትግራይ ክልል ምክር ቤትና ከፍተኛ የህግ አስፈጻሚ አካል ጋር የፌዴራል መንግስት ምንም አይነት ግንኙነት እንደማያደርግ ወስኗል።
ሁለተኛው የፌደራል መንግስት የትግራይ ህዝብን የልማትና መሰረታዊ አገልግሎቶች ፍላጎት ማዕከል በማድረግ የከተማ እና የቀበሌ አስተዳደርን ጨምሮ በክልሉ ከሚገኙ ህጋዊ ተቋማት ብቻ የስራ ግንኙነት ያደርጋል።
ሶስተኛ የውሳኔውን አፈጻጸም በፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ እና ጉዳዩ በሚመለከታቸው ቋሚ ኮሚቴ ክትትል መደረግ እንዳለበት ውሳኔ ተላልፏል። (ሰለሞን ጸጋዬ፤ ኢቢሲ)
ከዚሁ ጋር በተያያዘ “ወደ ትግራይ ተመለሱ” ተብለው በህወሓት የተጠሩት አባላት “አንሄድም” ማለታቸው ተሰምቷል።

ህወሃት የፌዴራል መንግስቱ ሕገ መንግስቱን እንደጣሰ ገልጾ በፌደራል ደረጃ ምርጫን በማሸነፍ በሚያዙ ኃላፊነቶችና ውክልና የነበራቸው የህወሃት አመራሮችና የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ኃላፊነታቸውን በመተው ወደ ድርጅታችሁ ህወሓት ጽ/ቤት ሪፖርት እንዲያደርጉ ነው ውሳኔ ያስተላለፈው።
በዚህም መሰረት የጠቅላይ ሚኒስትሩን ልዩ አማካሪ አርከበ ዕቁባይ (ዶ/ር)፣ የሕዳሴው ግድብ ሕዝባዊ ተሳትፊ ማስተባበሪያ ምክር ቤት ጽ/ቤት ዋና ዳይሬክተር ሮማን ገ/ሥላሴ ፣ የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ አልማዝ መኮንን ፣ የትራንስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉ ገ/እግዚአብሔር ፣ ዓባይ ወልዱን እና አዲስ ዓለም ባሌማን ጨምሮ 13 አመራሮች ለህወሃት ጽ/ቤት ሪፖርት እንዲያደርጉ ተጠይቀዋል። ከዚህ በተጨማሪም የህወሃት አባል የሆኑ 27 የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላትም ጥሪ ተላልፎላቸዋል።
በዚህ ጉዳይ ላይ አል ዐይን አስተያየት የጠየቃቸው የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ሕዝባዊ ተሳትፎ ማስተባበሪያ ምክር ቤት ጽ/ቤት ዋና ዳይሬክተር ሮማን ገ/ሥላሴ ጉዳዩን እንዳልሰሙት ተናግረዋል። ህወሃት ይህንኑ ውሳኔ በይፋዊ የፌስቡክ ገጹ ላይ ሪፖርት እንዲያደርጉ ከጠቀሳቸው አመራሮች መካከል ወ/ሮ ሮማን ገ/ስላሴ አምስተኛ ተራ ቁጥር ላይ የጠቀሳቸው እርሳቸው ግን ጥሪውን እንዳላዩትና እንዳላነበቡት ተናግረዋል።
በመጨረሻም “እኔ የምሰራው ሕዳሴው ግድብ ላይ ነው፣ግድቡ ደግሞ የሁሉም ብሔር ፣ የሁሉም ሕዝብ ሀብት ነው” ሲሉ ለአል ዐይን ምላሽ ሰጥተዋል። ጥሪውን በተመለከተ አስተያየት እንዲሰጡን የጠየቅናቸው ወ/ሮ ሮማን ምላሽ ከመስጠት ተቆጥበዋል።
ትናንትና በሁለቱ ምክር ቤቶች መክፈቻ ላይ የተገኙት ብቸኛዋ የትግራይ ሕዝብ ተወካይ ወ/ሮ ያየሽ ተስፋሁነኝም ህወሃት ከአባልነታቸው ተነስተው ሪፖርት እንዲያደርጉ ከጻፈላቸው የፓርቲው አባላት መካከል ቢሆኑም የህዝብ ድምፅ በማክበር ወደ ስብሰባው መምጣታቸውን ለኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ተናግረዋል።

“የተለያየ ፓርቲ ወክለን ወደ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ብንገባም ምክር ቤት ስንገባ ግን የኢትዮጵያ ሕዝብ ወኪል ነን” ያሉት ወ/ሮ ያየሽ አንድ የምክር ቤት አባል ከአባልነቱ የሚነሳው የወከለው ህዝብ አይወክሉኝም ሲል አሊያም የስራ ዘመን ሲያበቃ መሆኑን ገልጸዋል። ዓለም አቀፍ በሆነው የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ምርጫ እንዲራዘም መደረጉ የሕግ ልዕልና የታየበት መሆኑን ተናግረው በመክፈቻው ስብሰባ መገኘታቸው ትክክለኛ እና የሚጠበቅ ስለመሆኑ ገልጸዋል።
የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ አልማዝ መኮንንም ሪፖርት እንዲያደርጉ ከተጠቀሱት መካከል ሲሆኑ ስለጉዳዩ እንዳልሰሙ ገልጸዋል።
ጥሪ የተደረገው ለምክር ቤት አባላት መሆኑን ነው የማውቀው ያሉት ወ/ሮ አልማዝ ትናንትና እስከምሽት ሥራ ላይ እንደነበሩና ስለእርሳቸውም ሆነ ስለሌሎች አመራሮች የሰሙት እንደሌለ ለአል ዐይን ተናግረዋል። (አል ዐይን አማርኛ)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply