
ሕወሓት በትግራይ በሚገኘው የመከላከያ ካምፕ ላይ ጥቃት ማድረሱ እና በዳልሻሕ በኩልም ጦርነት መክፈቱ ተገለጸ። የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ዐቢይ አህመድ እንዳስታወቁት ህወሓት የሰሜን ዕዝንም ለመዝረፍ ሙከራ አድርጓል።
ከቀናት በፊት ህወሐት የተባለው የበረኻ ወንበዴዎች ጥርቅም አባል የሆነው ስዩም መስፍን ከውጭ ኃይሎች ጋር ሆነን በኢትዮጵያ ላይ ጥቃት እንሠነዝራለን ብሎ ሲናገር መደመጡ ይታወሳል።
የወንበዴዎቹ መሪ የሆነው ደብረጽዮን ደግሞ ጦርነት እንጀምራለን፤ እንዋጋለን፤ እናሸንፋለን በማለት የትግራይ ሕዝብ ለዳግመኛ ዕልቂት እንዲዳረግ ጥሪ ሲያደርግ ተሰምቶ ነበር።
እንደ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገለጻ፤ ይህ ሠራዊት ከሃያ ዓመታት በላይ የትግራይን ሕዝብ ሲጠብቅ የቆየ ሠራዊት ነው። በቦታው የሚገኘውም የትግራይን ሕዝብ ከጥቃት ለመከላከል ነው። ሕወሐት ግን እንደ ባዕድና እንደ ወራሪ ሀገር ሠራዊት ቆጥሮ፤ የመከላከያ ሠራዊቱን ለመምታትና ለመዝረፍ ተነሥቷል።
ህወሓት በዳልሻሕ በኩልም ጦርነት ከፍቷል።
መንግሥት የትግራይ ሕዝብ እንዳይጎዳ በማሰብ፣ ጦርነት እንዳይፈጠር የትእግሥቱ ጫፍ ድረስ ታግሷል ያሉት ዶ/ር አብይ፤ ጦርነት የሚቀረው ግን በአንድ ወገን ፍላጎት ብቻ አይደለም ነው ያለት።
“የመከላከያ ሠራዊታችን በኮማንድ ፖስት እየተመራ ሀገሩን የማዳን ተልዕኮውን እንዲወጣ ትእዛዝ ተሰጥቶታል። ቀዩ መሥመር የመጨረሻው ነጥብ ታልፏል። ሀገርና ሕዝብ ለማዳን ሲባል ኃይል የመጨረሻው አማራጭ ሆኗል” ብለዋል።
የኢትዮጵያ ሕዝብ ነገሮችን በሰከነ መንፈስ እንዲከታተል፣ በየአካባቢው ሊከሠቱ የሚችሉ ትንኮሳዎች በንቃት እንዲቃኝና ከመከላከያ ሠራዊታችን ጎን እንዲቆም ጥሪ አቀርባለሁ ብለዋል።
የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ዐቢይ አህመድ በፌስቡክ ገጻቸው ያወጡት መግለጫ ሙሉ ቃል እንዲህ ይነበባል፤
“ሕወሐት በትግራይ በሚገኘው የመከላከ ካምፕ ላይ ጥቃት አድርሷል። ሰሜን ዕዝንም ለመዝረፍ ሙከራ አድርጓል። ይህ ሠራዊት ከሃያ ዓመታት በላይ የትግራይን ሕዝብ ሲጠብቅ የቆየ ሠራዊት ነው። በቦታው የሚገኘውም የትግራይን ሕዝብ ከጥቃት ለመከላከል ነው። ሕወሐት ግን እንደ ባዕድና እንደ ወራሪ ሀገር ሠራዊት ቆጥሮ፣ የመከላከያ ሠራዊቱን ለመምታትና ለመዝረፍ ተነሥቷል። በዳልሻሕ በኩልም ጦርነት ከፍቷል።
“መንግሥት የትግራይ ሕዝብ እንዳይጎዳ በማሰብ፣ ጦርነት እንዳይፈጠር የትእግሥቱ ጫፍ ድረስ ታግሷል። ጦርነት የሚቀረው ግን በአንድ ወገን ፍላጎት ብቻ አይደለም።
“የመከላከያ ሠራዊታችን በኮማንድ ፖስት እየተመራ ሀገሩን የማዳን ተልዕኮውን እንዲወጣ ትእዛዝ ተሰጥቶታል። ቀዩ መሥመር የመጨረሻው ነጥብ ታልፏል። ሀገርና ሕዝብ ለማዳን ሲባል ኃይል የመጨረሻው አማራጭ ሆኗል።
“የኢትዮጵያ ሕዝብ ነገሮችን በሰከነ መንፈስ እንዲከታተል፣ በየአካባቢው ሊከሠቱ የሚችሉ ትንኮሳዎች በንቃት እንዲቃኝና ከመከላከያ ሠራዊታችን ጎን እንዲቆም ጥሪ አቀርባለሁ።”
በቀጣይ ሊነጋ አካባቢ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በቀጥታ ስርጭት ይህን መልዕክት አስተላፈዋል፤
ውድ የሀገሬ ህዝብ ሆይ ዛሬ ከሃዲ ኢትዮጵያውያን ኢትዮጵያን ወግተዋል።
ኢትዮጵያ በጎረሰ እጇ ባጠባ እጇ ተነክሳለች።
ላለፉት 20 ዓመታት የቀበሮ ምሽግ ውስጥ በመሆን ሀገሬን ወገኔን ህዝቤን ብሎ በብዙ ሺዎች መስዋዕትነት ከፍሎ ቆስሎ ደምቶ ሀገሩንና ህዝቡን የታደገው የመከላከያ ሰረዊት ላይ ዛሬ ምሽት ከመቀሌ ጀምሮ በበርካታ ስፍራዎች በካሃዲው ኃይሎች እና ባደረጁት ኃይል ጥቃት ተፈፅሞበታል።
ይህ ጥቃት በሀገራችን እስካሁን ከደረሱት ጥቃቶች እጅግ አሰፋሪ የሚያደርገው የሀገረ መከላከያ ሰራዊት ሰላም ለማስከበር በተለያዩ ሀገራት በተሰማራበት ሀገር በውጭ ኃይል እንኳ አጋጥሞት በማያውቀው ሁኔታ በገዛ ወገኑ ከጀርባው ጥቃት ተፈፀሞበታል።
በዳንሻ በኩል በአማራ ክልል ላይ የፈፀሙት ጥቃት በአማራ ክልል በነበረው ኃይል ተመክቷል።
የትግራይ ሕዝብ ወገናችን ነው ለጥቂት እኩዮች ሲባል ምንም እንኳ የእኩዮች መሸሸጊያ ዋሻ ቢሆንም ሕዝባችን ላይ ጥቃት አንሰነዝርም ብሎ በትዕግስት በቆየው ሰራዊት ላይ ጥቃት ተፈፅሞበታል።
በመላ ሀገራችን ቀድመው ባሰለጠኑት ባሰማሩት ባዘጋጁት ኃይል በተለያየ ቦታ በተለያየ ከተማ በንፁሃን ዜጎች ላይ ጥቃት ሊፈፅሙ ስለሚችል መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ከሚሊሻው ከፖሊስ ሰራዊት እንዲሁም በአካባቢያቸው ከሚገኝ የመከለከያ ሰራዊት ጋር በመተባበር ቀያችሁን ሰፈራችሁን እንድትጠብቁ አሳስባለሁ።
የመከላከያ ሰራዊት ከጠቅላይ ሰፍር በሚሰጥ ትዕዛዝ መለዮውን ሀገሩንና ህዝቡን እንዲከላከል ለሚከፍለው መስዋዕትነት ዛሬም እንደተለመደው በታሪኩ ውስጥ የሚታሰብ መሆኑን እገልፃለሁ።
ይህ እኩይ ኃይል መጥፊያው በመድረሱ በሰላም በንግግር በውይይት ሊፈቱ የሚችሉ ነገሮችን ባለፉት ጥቂት ቀናት ካለምንም ሀፍረት በሚዲያ በመውጣት ከየትኛውም የውጭ ኃይል ጋር በመተባበር ኢትዮጵያን እወጋለሁ ብሎ ሲያውጅ የነበረው ኃይል ይህን ለማመን የሚያስቸግር ንግግር በተግባር ማዋሉን በዚህ ምሽት አረጋግጧል።
የትግራይ ህዝብ ወገኔ ዘመዴ ሕዝቤ ብሎ ላለፉት 20 ዓመታት በቀበሮ ምሽግ ውስጥ በመሆኑ በብዙሺዎች የሚቆጠር መስዋዕትነት የከፈለውን አንተን ለመጠበቅ አስፈላጊውን ሁሉ ያደረገው የመከላከያ ሰራዊት የደረሰበት ጥቃት ጥቃትህ መሆኑን በመገንዘብ ከሀገር መከላከያ ሰራዊት ጎን በመቆም ሀገርህን ከነዚህ ከሃዲ ኃይሎች እንድትከላከልና በንቃት እንድትጠብቅ አሳስባለሁ።
ይህ ጉዳይ ለኢትዮጵያ አሳዘኝ አሳፈሪም ተግባር ቢሆንም ዛሬም እንደተለመደው በተደመረ በተባበረ ክንድ ይህንን ከሃዲ ጡት ነካሽ ኃይል ለማሳፈርና ለመደምሰስ እስፈላጊውን ሁሉ የምናደርግ መሆኑን እገልፃለሁ።
ይህ አሳፈሪ ተግባር በማይደገምበት ሁኔታ የሚቀለበስበትን ተግባር መላው የኢትዮጵያ ህዝብና የሀገር መከላከያ ሰራዊት በመተባበር የሚፈፅሙት ይሆናል።
ለመላው የሀገራችን ህዝቦች አስፈላጊውን መረጃ በየጊዜው በሚመለከታቸው የመንግስት አከላት የሚሰጥ መሆኑን እገልፃለሁ።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply