
ስሜት ጎርፍ ነው፤ ያውም ደራሽ ጎርፍ፤ ብሄራዊ ቡድናችንን ስንደግፍም ሆነ ስናወድስ እንዲሁም ስንወቅስ በዚሁ ደራሽ ጎርፍ መወሰዳችን ይታያል። ይሄ ችግር ግን እንደ ሃገርም ችግራችን እየሆነ የመጣ ነገር ነው በስሜት መደገፍ በስሜት መቃወም፤ ዛሬ ያወደሱትን ነገ መርግም ሁሉንም ነገር በዘላቂ ጥቅም፤ በዘላቂ ስራ እና በዕውቀት መመዘን እያቃተን ነው። ከዚያም ዐልፎ ስሜታችን ጫፍ ላይ በሚደርስበት ጊዜ ሰከን ብሎ የሚያስብ ሰው ሲያጋጥመን እንደጭራቅ እንመለከተዋለን። ከእኛ በሓሳብ የተለየ አስተያየት የሰጠ እንደሆነማ በቃ ቤተክርስቲያን ውስጥ የገባ ውሻ እናደርገዋለን።…
የሰሞኑ የብሄራዊ ቡድናችን ውጤትም የዚህ ጎርፍ ሰለባዎች መሆናችን አንዱ ማሳያ ነው። መጀመሪያ ላይ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አዲስ አበባ ከቤኒን ብሄራዊ ቡድን ጋር ሲጫወት አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የአሰላለፍ ስህተት ሰርቶአል መሃል ላይ ምንም ፈጣሪ /creative/ ተጫዋች አልነበረውም በሚል ከውጤቱ በኋላ ህዝቡም ጋዜጠኞችም ሲያወግዙት ከረሙ። ልብ አድርጉ እዚህ ጋር ሁሉም የሚያወራው በስሜት የዕለቱን ጨዋታ በተመለከተ የነበረውን ችግር እንጂ በዕውቀት የሃገራችን እግርኳስ ችግር ምንድን ነው? ብሎ ስለዘለቄታው የሚያወራ እና የሚያስብ የለም። ፌደሬሽኑም ቢሆን ህልውናውን ከጊዜያዊ ውጤት ጋር አጣብቆ የተቀመጠ ስለሆነ ዘለቄታዊ ስራ ሲሰራ አይታይም እናም አቶ ሰውነት ያቺን የተችት ፍላጻ እንደምንም ሽል ብለው አሳለፏት ። …
ቀጥሎም ከጥቂት ጊዜያት በኋላ ሱዳንን አሸንፈን ለአፍሪካ ዋንጫ አላፊ መሆናችንን አረጋገጥን፤ ስሜት አሁንም እንደደራሽ ጎርፍ አጥለቀለቀን ህዝቡ ”ሳላዲን ጥቁር ሰው” ተባለ። ሲሰደብ የነበረው ሰውነት በየኤፍኤም ራዲዮው ጋሼ ጋሼ መባል ተጀመረ። አንዳንዶቹም ኢትዮጵያዊው ሞሪኖ ይሉት ጀመር። አሁንም እዚህ ጋር ረጋ ብሎ በዕውቀት ይሄ ውጤት ጊዜያዊ ነው፤ ዘለቄታዊ ውጤት የምንፈልግ ከሆነ ሰከን ብለን የእግርኳሱን ችግር እንመልከት በስሜት አንነዳ የሚል ሰው ሲገኝ እንደከሃዲ ሃገሩን እንደማይወድ ተቆጥሮ መወገዝ ጀመረ በስሜት! አቶ ሰውነትም ይህቺን ስለሚያውቅ በሴካፋ ውድድር መሳተፋችን አስፈላጊ አይደለም ብሎ ራሳችንን ከሴካፋ ውድድር እንድናገልል አደረገ። ለምን? ምክኒያቱም ስሜታዊ መሆናአችንን ስለሚያውቅ በሴካፋ ላይ የሚመጣው ውጤት የእርሱን ከብሄራዊ ቡድን ጋር ቆይታ ስለምትወስን ቁማሩን መቆመር አልፈለገም። አዎ ስራዎች በዕቅድ እና በዕውቀት ሳይሆን በስሜት በሚሰሩበት ሃገር ለምን ሪስክ ይወስዳል? …
የዛምቢያውን ጨዋታ አቻ ስንወጣማ ሁሉም ራሱን በስሜት አበደ፤ በደራሹ ውሃ እየተገፋ የሃገር ፍቅር ስሜት በሚል ሽፋን ተጫዋቾቹ ወኔ አላቸው ጀግና ናቸው ማለት ተጀመረ። በዚህ ወቅት እጅግ በጣም ጥቂት ሰዎች ናቸው ረጋ ብለው በስሜት ሳይነዱ እግርኳስ ጥበብ እንጂ ወኔ አይደለም ብለው ለመናገር ድፍረት የአገኙት እንደ Genene Mekuria Libro ያሉት ሰዎች፤ ግን ማን ያዳምጣል? ሁሉም በስሜት ባሉን እየተንሳፈፈ ነው ከጋዜጠኛ እስከ ፌደሬሽኑ ድረስ፤ እንደማይደርስ የለም ዐርብ ዕለት የቡርኪናፋሶ ውጤት የስሜት ባሉኑን ክፉኛ አስተንፍሶት ከነበርንበት ከፍታ በድንገት ከመሬት ወርደን ዝርግፍ አልን ፤ አሁን ደግሞ አሰልጣኙን ማውገዝ ተጀመረ በሳምንት ውስጥ ስናወድሰው የነበረውን ሰውዬ ወደተለመደው በስሜት ማውገዝ ተጀመረ ያሳዝናል ። …
በሃገር ፍቅር ስሜት ቢሆን በቁርጠኝነት ቢሆን ኖሮ የአፍሪካ ዋንጫን አይደለም የዓለም ዋንጫንም ቢሆን ከእኛ ልጆች የሚነጥቅ ሃገር አይኖርም ነበር፡፡ በነገራችን ላይ ለተጫዋቾቹ ያለኝ ክብር በጣም ከፍተኛ ነው የሚችሉትን ሁሉ አድርገዋል የቆጠቡትም አንዳች ነገር አልነበረም እናም ክብር ይገባቸዋል። መጪው ውጤት ምንም ቢሆን ቢያልፉም ባያልፉም ለእነሱ ያለኝ ክብር አይቀንስም … አሁንም ቢሆን ግን ከጊዜያዊ ውጤት ባሻገር ነገሮችን በዕውቀት የሚመለከት ጋዜጠኛ፤ በዕውቀት የሚሰራ ፌዴሬሽን እና ጊዜያዊ ውጤት ተመልክቶ ሳይሆን ዘላቂ ስራዎች እየተመለከተ የሚደግፍ ተመልካች ያስፈልገናል። እግርኳስ የስሜት ስፖርት መሆኑ ሳይረሳ ስሜቱም በሜዳ ላይ እንጂ ከሜዳ ጀርባ የሚሰራው ነገር በሙሉ በዕውቀት እና በጥበብ የሚሰራ መሆኑም ሳይዘነጋ …
አዎ እግርኳሳችን የእራሷን ሙሴ ትፈልጋለች!
ዝግጅት ክፍሉ፤ ጽሁፉን ያገኘነው ከፌስቡክ ሲሆን ጸሐፊው Enena Hasabe ናቸው፡፡ ከዚህ ርዕስ ጋር ተመሳሳይ በሆነ መልኩ የድረገጽ ጋዜጣችን (እባካችሁ ይህንን “ኢትዮጵያዊነት” አክብሩት!!) በሚል ርዕስ ተመሳሳይ ሃሳብ በርዕስ አንቀጽ ላይ አውጥተን ነበር፡፡
“ለመሆኑ የሀገር ስሜትና የእግር ኳስ ሰሜት አንድ ናቸውን ?” ይህ ቢሆንማ ኖሮ “የፖለቲካ ፓርቲን መደገፍና ሀገርን መደገፍ አንድ ሊሆኑ ነው” እንግዳው አግር ኳስ የማይጫወት ወይንም የማይወድ ሁሉ የሀገር ፍቅር የለውም…የፓርቲ አባል ያልሆን የሀገሩ ፍቅር የለውም ማለታችን ይሆን? እየተስተዋለ!!!
***”ከጊዜያዊ ውጤት ባሻገር ነገሮችን በዕውቀት የሚመለከት ጋዜጠኛ፤ በዕውቀት የሚሰራ ፌዴሬሽን እና ጊዜያዊ ውጤት ተመልክቶ ሳይሆን ዘላቂ ስራዎች እየተመለከተ የሚደግፍ ተመልካች ያስፈልገናል። እግርኳስ የስሜት ስፖርት መሆኑ ሳይረሳ ስሜቱም በሜዳ ላይ እንጂ ከሜዳ ጀርባ የሚሰራው ነገር በሙሉ በዕውቀት እና በጥበብ የሚሰራ መሆኑም ሳይዘነጋ … (ይህ በሳል ምክር ነው በለው!)
————————————–*************—————————
“በስሜት መደገፍ በስሜት መቃወም፤ ዛሬ ያወደሱትን ነገ መርግም ሁሉንም ነገር በዘላቂ ጥቅም፤ በዘላቂ ስራ እና በዕውቀት መመዘን እያቃተን ነው። ከዚያም ዐልፎ ስሜታችን ጫፍ ላይ በሚደርስበት ጊዜ ሰከን ብሎ የሚያስብ ሰው ሲያጋጥመን እንደጭራቅ እንመለከተዋለን። ከእኛ በሓሳብ የተለየ አስተያየት የሰጠ እንደሆነማ በቃ ቤተክርስቲያን ውስጥ የገባ ውሻ እናደርገዋለን።… ++
” (አቤ ቶክቻው አልቅሶ ካስለቀሰኝ ላካፍላችሁ)… እኔና ሀሳቤ ይህንን ይመስሉ ነበር በለው!
፩) ለመሆኑ በቀጥታ ጨዋታውን በሀገር ውስጥ ለማስተላለፍ ተቸግሮ ያለቀሰ መንግስትና የኢቲቪ ጣቢያ ለመሆኑ ይህን ሁሉ በቦታው የተገኘ ደጋፊ ለማጓጓዝ ገንዘብ ማግኝቱ ዕድገታችን ደብል ድጅት ሳይሆን ‘ፈረሱላ’ ሆኗል ማለት ነውን ?
፪) መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገሮች አልሰለፍም ብሎ የሀገሪቱን ዕድገት ንቆ በሰው ሀገር ኢንቨስተር ለመሆን የመጣ ከሆነ ወጣቱ ሀገሩን ይህን ያህል የጠላበት ነገር ያስገርማል!?
፫) ይህ ሁሉ ወጣት በሀገሩ የኢኮኖሚም ይሁን የፖለቲካ ችግር ኖሮበት የተሠደደ ከሆነ ሀገሩ የማነው? ሞቶም, ተሰዶ, ታስሮ, ባህር ገብቶ, ከፎቅ ተወርውሮ,በሀገር ውስጥ ማን ቀረ ? ?
፬) በእርግጥ ይህ ሁሉ ወጣት ሀገሩን ነው ? ወይንስ ሥርዓቱን ነው የጠላው?
ሀገሩን ቢሆን ለምን እቤቱ አልተቀመጠም ?
የጠላው ሥርዓቱን ለመሆኑ የሚያሳብቀው የባንዲራ መዘበራረቅና ሁለት ብሔራዊ መዝሙር መዘመሩ ነው “ልዩነታችን ውበታችን” ይሉሃል ይሄ አደለምን?
ይህ ሁሉ የኢህአዴግ ደጋፊ ከሆነ እሰው ሀገር ምን ያደርጋሉ? ቱሪስቶች ናቸው? ይማራሉን?መቼም ይህ ሁሉ ትኬት ከፍሎ የመጣ ሀብታም ‘የኮብል እስቶን ምሩቅ’ ‘የዲያስፖራ ኢንቨስተር’ ‘በአነስተኛና ጥቃቅን የታቀፉ’ ‘ስኳር የላሡ ‘ ‘ጤፍ መብላት የጀመሩ’ ባለሀብት ይሆኑ ይሆን ?
፭) የዚህ የጎል ብዛትና የባንዲራችን ነገር.. (፩) ለባለ አንበሳው (፩) ምልክት ለሌለበት (፩)ለባለ ኮከቡ ለመርዳት ለውጡት (፩) ( ኦነግና ኤርትራ) በመፈቃቀርና በመተሳሰብ ላይ በተመሠረተ እኩል እንዲካፈሉ ነው።(መክፈልና መቁረስ ተጠናውቷቸዋልና)….!!
************************************************
ምንም ባንዲራ ላልያዘ ተመልካች አንድ ጋዜጠናኛ እንዲያስረዳው ቀረበ አሉ..
ጋዜጠኛ -ሀገራችሁ አንድ ናት ይህ ሁሉ ባንዲራ ምንድነው?
ታዛቢው *ታሪኩ ብዙ ነው ግን…ነገሩን ለማሳጠር “ይህ የምታየው ዘሩ ልዩ የሆነ ‘አንበሳ’ በጫካ በዚህ በምታው ‘ትልቅ ዛፍ (ዋርካ)’ሥር ሲደክመውም ለአደንም ሲሰማራ ያርፍ ነበር ።የዱር እንስሳት እዚያ ላይ የምታየውን ‘ቀንበጥ’ ለመቀንጠስ ሲመጡ ይቀልባቸው ነበር።አንበሳው ኖሮ ኖሮ አረጀ ደከመ በሀገራችን እንደሚሉት”አንበሳ ሲያረጅ የዝንብ መጫወቻ ይሆናል” ነው። ዝንቦች ወረሩት ጎበዝ መሆናቸውን ለማሳየት ‘ኮከብ’ ጫኑበት አለው”።
ጋዜጠኛ – “እኔ መች አወኩ ይህ ካኒቴራ ላይ የታተመው ” ንብ ‘መስሎኝ ለካስ ‘ ዝንብ ‘ ነው ለጊዜህና ለሰጠኸኝ ማብራሪያ አመሰግናለሁ። የዝንቦቹን አራቢ ሞባይል ቴሌፎን ይዘው አይቻቸዋለሁ”።
ጋዜጠኛ- አንተ ታዲያ ለምን አንደኛውን እንኳ ለማስታውስ ሰንደቅ አልያዝስክም?
ታዛቢው *”ተሳስቼ ሌላ ባንዲራ ይዤ የሚያስቆጥሩብን የጎል ቁጥር ከፍ እንዳይል ፈርቼ ነው”።
*ዕድገታችን በመጨመረ ቁጥር ውርደታችን መቀነሰ ነበረበት።አራት ነጥብ።አብሮ ለመሥራትና ለመብላት መገፋፋት… ለማዳመቅና ቁጥርን ለማብዛት ደጋፊ መጥራት ትልቅ ቅጥፈት ነው በለው!
ተቀምጦ ከማልቀስ… ለክብር~ ለነፃነት~ በእኩልነት~ በአንድነት~ተነስቶ መቆጣት !!!!
ብሔራዊ ቡድኑ ወደፊት የተሻለውን ውጤት እንዲገጥመው ከልብ እመኛለሁ የሰው ልጅ መልካሙ ጥበብ ከስሕተት መማር እንጂ በምክንያት መፈንጠዝም ሁን ማዘን ብዙም አያስኬድም በለው! ከሀገረ ካናዳ በቸር ይግጠመን