
በሀገረ ሐበሻ ፤ ክቡር ነበር ሥራ
የሥራ ባሕሉ ፤ ነበረ ጠንካራ
በዓለም መድረክ ላይ ፤ ያደረገው አውራ
ኃያል ጉልበተኛ ፤ እጅግ የሚፈራ
የግዛት ሀገሩን ፤ በምዕራብ ምሥራቁ
አስፋፍቶ ያስያዘው ፤ እያስገበረ ዕንቁ
ዛሬ ግን ስናየው ፤ ያ አውራ ሐበሻ
የቀን ጎደሎ ገጥሞት ፤ ነክሶት ክፉ ውሻ
እዚህ ሀገሩ ላይ ፤ ከእሱው መዳረሻ
ከቶ የማይነካውን ፤ ብዙ የሥራ ድርሻ
ይህ ጨዋ የጨዋ ዘር ፤ የጌታ ልጅ ጌታ
የሎሌ የባሪያ ነው ፤ ያለውን ገበታ
ርቆ ይሄድና ፤ ከሩቃኑ ጓዳ
ተደብቆ ከወገን ፤ ታይቶ እንዳይከዳ
ያለዕረፍት ይሠራል ፤ ተግቶ አስንቆ ባዳ
መጥቶ የማይነግረንን ፤ ሳያፍር ሳይጎዳ
ባሪያው ከነበሩት ፤ ካሳያቸው ፍዳ ፡፡
ሥራን ወዶ ማክበር ፤ ሠርቶም ሀብታም መሆን
ከጥንት ጀምሮ ፤ ነበር ባሕላችን
ወደ ኋላ ግና ፤ የአውሮፓ ሚሲዮኖች
አዩትና አቅሙን ፤ የሕዝቡን እሴቶች
የጎጆ ኢንዱስትሪው (ምግንባቡ) ፤ የያዘውን ቦታ
ነገ እንደሚሆነን ፤ ለሀገር ሆኖ አለኝታ
ሊመጥቅ እንደሚችል ፤ በኪነ ብጀታ (በቴክኖሎጂ)
ስለታወቃቸው ፤ ክፋትን ሸረቡ
ያን የሚሠሩትን ፤ ትጉዎችን ከሕዝቡ
ነጥሎ ለማጥፋት ፤ ከኅብረተሰቡ
እንደዚህ እያሉ ፤ ሰበኩ ከተቡ
እኛ በሀገራችን ፤ ይሄን የሚሠሩ
ብረት የሚያቀልጡ ፤ ሸክላንም ከአፈሩ
በቡዳ ዓይን በልተው ፤ እያስለፈለፉ
ብዙ ሕዝብ እየፈጁ ፤ ሆነው የሚያጠፉ
እነሱን ሰብስበን ፤ ካጠፋን በኋላ
ነው ሰላም ያገኘን ፤ የኖርነው በተድላ
እናንተም እንደኛ ፤ ካላደረጋቹህ
ጤና አይሰጧቹህም ፤ ካልመነጠራቹህ
ብለው ሰበኩና ፤ ወደ ሕዝብ በመግባት
የጥፋቱን ሴራ ፤ መርዘኛውን ስብከት
ቀጥቃጭ ሸክላ ሠሪን ፤ ቡዳ በማሰኘት
ከሰው እንዳይደርሱ ፤ እንዲያልፉ በግዞት
አድርገው በማጥቃት ፤ በእርኩስ ምቀኝነት
ከእድገት ገቱንና ፤ አበቁን ለውድቀት
እነዚህ እርጉሞች ፤ በዚህ ሳይበቃቸው
የቀረውን ሥራ ፤ ተግቶ ለሚሠራው
እኛ በሀገራችን ፤ ይሄን ዓይነት ሥራ
የሚሠራ ሁሉ ፤ ነው ከባሪያ ጎራ
ጨዋ የጨዋ ልጅ ግን ፤ እንደዚህ ዓይነቱን
ቢሞት አይነካውም ፤ በዘሩ የሌለውን
ያዛል እንጅ ያሠራል ፤ባሪያ አገልጋዩን
እያሉ ስሜቱን ፤ ሲያጠቁት ክፉኛ
ኃያል ያረገንን ፤ ብርቱ ባለሻኛ
ባለ ሠይፍ አለቃ ፤ የዕቡያን ዳኛ
እውነት መሰለውና ፤ ስለተታለለ
ያ ክብር ዐቢይ ሀብቱ ፤ እጅግ ተጃጃለ
ሥራን ንቆት ቀረ ፤ ላለመባል ባሪያ
ሴራቸውም ሠምሮ ፤ ደኸየች ኢትዮጵያ
ያኔ ለተሠራበት ፤ ሸር በእነዚያ ውሻ
አቶለት መፍትሔ ፤ ቸግሮት ማርከሻ
ዛሬም ይቸገራል ፤ እንጃ መጨረሻ ፡፡
የዚህ ክፉ ሴራ ፤ አደጋው ታይቷቸው
የዐፄ ፋሲል ልጅ ፤ ዮሐንስ አንደኛው
ሳይጸና ለማረም ፤ ስር ሰዶ ሳይወረው
ልምሹ ሽባ አድርጎ ፤ ሐበሻን ሳይነቅለው
ንጉሥ ሆነው ሳለ ፤ ሳይኖር የቸገራቸው
የሥራን ክቡርነት ፤ ለማሳየት ብለው
ከቤተመንግሥቱ ፤ ኢምንትን ሳይነኩ
በላብ እያደሩ ፤ በሥራ ሊማርኩ
ሰሌን እየሠሩ ፤ ሥራ እየሰበኩ
ከቶም ላለመንካት ፤ የደሀን ግብር እንኩ
ከዚያ በሚያገኙት ፤ እየተዳደሩ
መሥራት እንደሆነ ፤ የጨዋ ዘር ግብሩ
እሳቸው ንጉሡ ፤ ሠርተውም ቢያስተምሩ
በካህንነታቸውም ፤ ሊሠራ የማይወድ
አይብላ የሚለውን ፤ የአምላክን ቃለ ፍርድ
ለአዳምም ያለውን ፤ ጥረህ ግረህ ብላ
ሰብከው እያሰበኩ ፤ ቢተጉም በመላ
ሊነቀል አልቻለም ፤ ያክፉ አሜኬላ
ዐፄ ቴዎድሮስም ፤ ጀግናው ስመ ጥሩ
ንጉሥ ሆኖ እያለ ፤ ባለዝና ኩሩ
ጫማ እንኳን ሳይመኝ ፤ እየሄደ በእግሩ
ዶማውን ጨብጦ ፤ በእጁ እየቆፈረ
የሥራን ክቡርነት ፤ ቢያሳይ እየታተረ
ብዠታ ሴራውን ፤ ሊያጠፋ እየጣረ
መሪ ቃል አውጥቶ ፤ ነዶ እየፎከረ
ታላቅ እንደነበርን ፤ በዓለም ትናንትና
ታላቅ እንሆናለን ፤ ዛሬም እንደገና
እያለ ተቃጥሎ ፤ ባለው ፍቅር ለሀገሩ
አባብሎ በመላ ፤ እሽ ያለለት ለታ
እንቢ ሲለው ደሞ ፤ ሳይወድ በግዴታ
በቆራጥ አመራር ፤ ቢለውም ከምሩ
ሳይነቀል ቀረ ፤ የሰይጣን ምክር ስሩ
ሌሎችም ትጉሐን ፤ ብዙ ቢሞክሩ
አሁንም አልጠፋም ፤ ያ የእንክርዳድ ዘሩ
ከዐፄ ዮሐንስ በላይ ፤ ሰባኪ አንደበቱ
ከዐፄ ቴዎድሮስ በላይ ፤ ቆራጥ ክንደ ብርቱ
ከቶ ማን መቶለት ፤ ይማራል በእውነቱ ?
ምከረው ምከረው ፤ እንቢ ካለ ግና
መከራ ይምከረው ፤ እንዳለው ሳተና
ምናልባት ይማራል ፤ ሲታሽ በመከራ
ግን ከዚህ የከፋ ፤ ምን መጥቶ ሊገራ ?
ነው ወይስ ተምሯል ? አውቋል ያንን ሴራ ?
ተሰብሮ መውደቁን ፤ ማውደሙን አደራ ?
የኛ የሥራ ባሕል ፤ የነበረው ድሮ
ርእሰ ኃያላን ፤ እያለን ጀምሮ
ገና በኦሪቱ ፤ በአምላክ አስተምህሮ
የበዓል ቀናት ተብለው ፤ የማይሠራባቸው
ከወር እስከ ዓመቱ ፤ ነበሩ ተለይተው
በሐዲስ ኪዳንም ፤ እንደ ጥንቱ ሁሉ
የበዓላት መከበር ፤ በሐዲስም ቀጠሉ
ነገር ግን ሥርዓቱ ፤ እንደ ጥንቱ ሳይሆን
የተለየ ሆኗል ፤ ስናይ አከባበሩን
የሐዲስ ኪዳኑ ፤ በበዓል ቀናቱ
ሥራ እንዳይሠራ ፤ ቢልም እንደጥንቱ
ለይቶ ባወጣቸው ፤ ከወሩ በአምስቱ
ቀኖናዊ በሆነው ፤ አስተምህሮቱ
በአከባበሩም ላይ ፤ ታይቷል ልዩነቱ ፡፡
ሕይዎት የምትቀናው ፤ ሥራ ባሉት ብቻ
ከቶ አይደለምና ፤ የችግር ቁልፍ መፍቻ
በእነዚህ በዓላት ፤ የታዘዘው ተግባር
ሕይዎት የሚያቀና ፤ ብዙ አለው ቁምነገር
በማኅበራዊው ፤ ሕይዎት መስተጋብር
የታመመ ያዘነን ፤ ገጥሞት እክል ችግር
የታሰረን ወገን ፤ ታርዞ የተራበን
ደካማ ወገን አልባን ፤ ድጋፍ የሚያሻውን
መጎብኘት መጠየቅ ፤ እርገው የታዘዘውን
ለመገንባት ፍቅርን ፤ ሰ ብ አ ዊ ነ ትን
በጋብቻ ሕይዎት ፤ ለሦስቱ ጉልቻ
ለሚተሳሰሩ ፤ መሥርተው ጋብቻ
ሽምግልናው ምክሩ ፤ እንዲሠምር በእሽታ
በሌላውም ጉዳይ ፤ በተለያየ ቦታ
በጥል በክርክር ፤ ላጣም ሰላም ፋታ
ማስታረቅ ማስማማት ፤ ወጥቶና ወርዶ
ጥላቻን አጥፍቶ ፤ አፋቅሮ አዋዶ
ወደ አምላክ ቤት ሔዶም ፤ ቃለ እግዜርን መስማት
ሰብእናን ማነጽ ፤ ምግባርን ማቃናት
ክብር ምስጋናን ማቅረብ ፤ ማወደስ በጸሎት
ለቀለሱት ትዳር ፤ ለተወለዱ ልጆች
በቂ ጊዜ መስጠት ፤ እንዳይጎዱ በአንዳች
ዕቅድንም መንደፍ ፤ ነገ ለሚሠራው
መምከር ማደራጀት ፤ ገብቶ በጎደለው
ይሄን ይሄንና ፤ እንዲህ የመሳሰለው
ጉዳይ ይከወናል ፤ በዓል ቀን በሆነው
ኑሯችን በሥርዓት ፤ እንዲሆን ዐቅድ ያለው ::
እንዲህ አርጎ አበጃጅቶ ፤ ኑሮውን ሲገፋ
ሥራውን ሲሠራ ፤ አጥቶ ሳይከፋ
ያው ወደኋላ ግን ፤ ገጠመው ደንቃራ
በቅኝ ግዛት ሰላይ ፤ ተተብትቦ ሴራ
ከወደ አውሮፓ ፤ ክፋትን ሸርበው
ሰተት ብለው ገቡ ፤ ቅን አሳቢ መስለው
እንዲያው ግን በሞቴ ፤ ምንድን ነው ያረግናቸው ?
ጥርስ የነከሱብን ፤ የዚህን ያህል ከፍተው ?
እነዚያ እኩያን ፤ ካመጡብን ዕዳ
ከዋናዎቹ አንዱ ፤ ሀገርን የጎዳ
መቀመቅ ያገባን ፤ ያስቆጠረን ፍዳ
የነጻነት ጥቅሟን ፤ ዋጋ እያደባዩ
ከሥራ አጣልተው ፤ ከሀብት እያደኸዩ
መቋቋም እንዳንችል ፤ ሲወረን እኩዩ
ለባርነት ግዛት ፤ ሲያመቻቹን ቆዩ
ከሚሲዮን ልሳን ፤ ጤና አለ ብላቹህ
ጆሮ ልባቹህን ፤ ከፍታቹህ ሰጥታቹህ
እመቀ እመቃት ፤ ዘቅጣቹህ ገባቹህ
ይሄም ሁሉ አልፎ ፤ ዛሬም እንደገና
ሚሲዮን ለሀበሻ ፤ ብለህ ያስባል ቀና
ጆሮና ልብህን ፤ ከፍተህ ሰተሀልና
ደሞ ልትቆጥር ነው ፤ ሌላ የአሳር ዙር ገና
ሥነ ልቡናውን ፤ እያወሳሰቡ
በሳይካትሪ ቁማር ፤ ግራ እያጋቡ
ስንቱን የተማረ ፤ ንክ ፉዞ አደረጉ
ስንቱን ቀለዱበት ፤ እንዲያ እንደፈለጉ
ለሀገር ለወገን ፤ አርገው እንዳይሠሩ
ሰብአዊ ልማቷን ፤ በገፍ አከሰሩ
ፖለቲካም ገብተው ፤ በሀገር ልጆች መሀል
በፈለጉት መንገድ ፤ ጠምዝዘዋቸዋል
ሰላምና አንድነት ፤ ለመቸም እንዳይኖር
ቁልፍልፍ አድርገው ፤ ታንፈታው በማሰር ፡፡
እንኳን ሊቀበሉት ፤ ሊሰማ የሚያስነውር
በቅድስት ኢትዮጵያ ፤ በእግዚአብሔር ምድር
ባሕልን የሚቃረን ፤ ሃይማኖትን ጭምር
እንኳን በሃይማኖት ፤ በዓለማዊ ላሉ
ከቶ የማይታሰብ ፤ ይሁን ለመባሉ
ሰዶማዊነትን ፤ ተቀበሉ እያሉ
ከሰይጣን እንደሆኑ ፤ በይፋ ያሳያሉ
አእምሮ ያለው ሰው ፤ ይሄን ጊዜ እንኳን
ነቄ ብሎ አይወጣም ? ጣጥሎ አጋንንትን ?
ዓላማ ግባቸው ፤ ዐውቆ ምን እንደሆን
ሃይማኖት የሚሉት ፤ እነደሆነ ሽፋን
ዛሬ በዚህ ጊዜ ፤ ያልነቃ ጭንቅላት
መቸም አይባንንም ፤ ምንም ቢያደርጉት ፡፡
ይህ የዋህነት ነው ? ወይንስ ጅልነት ?
በሚሲዮን ሴራ ፤ ደርሶ እያለ ሞት
አእምሮ ያለው ሰው ፤ የሚያስብ ጭንቅላት
የሚከነክነው ፤ የሀገሩ ውድመት
የሚቆረቁረው ፤ የሥልጣኔው መጥፋት
ይመስዮንናል ? ለማገልገል ጠላት ?
ራሱን ለመንቀል ፤ በሰይጣን እጆች ጣት ?
በየትኛው መጽሐፍ ፤ በምን ምስክርነት ?
እሱ ካንተ ይልቅ ፤ ለአምላክ ኖሮት ቅርበት ?
ደሞ እምንህ ደርሶ ፤ የትና መቸ ዐውቆት ?
ከነ መኖሩ እንኳን ፤ መጽሐፉ ያልጠቀሱት
ማን ይናገር ሲባል ፤ ያየ የነበረ
ማንስ ደሞ ያርዳ ፤ እንዳልክ የቀበረ
አንተ ለሱ ተርፈህ ፤ ትሰጣለህ እንጅ
ምን ጎሎህ ምን አተህ ? ትቀበል ከእሱ እጅ ?
ምን ዓይነት አዚም ነው ? ምንስ ዓይነት አስማት ?
እንደዚህ የሚያፈዝ ፤ የሚያደነዝዝ ሞት
ማስተዋል የሚነፍግ ፤ የሚያቅት ለመንቃት ?
አደንቁሮ የሚገል ፤ የደመነፍስ ሕይዎት
ቀድሞስ እውነት መስሎህ ፤ ሳታውቅ ተታለህ
ዛሬ ምን ሆነህ ነው ? እንዲህ መጃጃልህ ?
ማንነትህን ሳይቀር ፤ ሲነቅለው ከልብህ
ሸሩ ሳይታይህ ፤ ፈዘህ ምርዝ መጋትህ ?
አንድ ጊዜ እንቅፋት ፤ ደጅ መንገዱ ላይ
ያደናቀፈው ሰው ፤ ደግሞ እሱው ድንጋይ
ቢያነቅፈው እንደገና ፤ ድንጋዩ እራሱ ነው
ተብሎ እንደተባለው ፤ ንቃት የጎደለው
ሆነህ ቀረህለት ? ሁሌ የሚያጃጅለው ?
መቸ ነው የምትነቃው ? ምንስ ቢያደርግብህ ?
ባዶ እጅህን ቀርተህ ፤ ሁሉን ነገር አተህ
የዛኔ ብትነቃ ፤ ምን ትፈይዳለህ ?
ምንም ምን ለማድረግ ፤ ዕድሉ እኮ አይኖርህ
ንቃ ንቃ ንቃ ፤ እባክህን ንቃ
እንደ የእርግማን ልጅ ፤ አትልመድ ሰቆቃ
ደንበር ብለህ ተነሥ ፤ ሁሉንም በል በቃ
ሀገርህን ማየት ፤ አትሻም ወይ ልቃ ?
በቀድሞው ቦታዋ ፤ እንደገና ታውቃ ?
እስከመቸ ታስራ ፤ እስከመቸ ወድቃ ?
ኢትዮጵያና አፍሪካ ፤ የሆኑት መጻጉ
በአውሮፓ ሚሲዮን ፤ ነው ስለተወጉ
ታሪክ ይንገራቹህ ፤ ሀቁን ብትፈልጉ
ይሄ የሰይጣን አዚም ፤ የማይለቅ ከሆነ
በአፍሪካ ኢትዮጵያ ፤ እየተኮነነ
የመርዝ መርፌውን ፤ መውጋት ከቀጠለ
ዛሬም እንደቀድሞው ፤ ጠልቆ እየሰለለ
ፀሐይ ላትወጣ ነው ፤ ጨለማም ገነነ
ደኅንነትም አይኖር ፤ ሞት ከሠለጠነ
ሰይጣን ከነገሠ ፤ ሴራው ከሰፈነ
ጥር 2003 ዓ.ም.
amsalugkidan@gmail.com
Leave a Reply