• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ይድረስ በኢትዮጵያና በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ጉልበት ላላችሁ ሁሉ

March 11, 2016 06:09 am by Editor 1 Comment

ልጆች ሆነን ታላላቆቻችን ጉልበት አለን ብለው በደል ሲፈጽሙ “እግዚአብሔር በቀዳዳ ይየው!” እንል ነበር፤ ለመርገምም እየፈራን አንዲያው ድርጊቱ እንዲመዘገብልን ማሳሰባችን ይመስለኛል፤ አሁንም እንደዚያ ለማለት ይቃጣኛል፤ ግን አግዚአብሔር በሰማይ ላይ መኖሩን፣ በእያንዳንዳችን ውስጥ መኖሩን የቤተ ሃይማኖት ሰዎች እንኳን ማመናቸው በሚያጠራጥርበት ዘመን ለዓለማዊ ባለሥልጣኖች የእግዚአብሔርን ስም ማንሣት ፋይዳ ይኖረዋል ብዬ አልገምትም፤ ሆኖም እኔ ስለማምንበት የራሴን አሳውቃለሁ፤ ኢትዮጵያ የእግዚአብሔር አገር ነች፤ ኢትዮጵያን ጎድቶ የተጎዳ እንጂ የተጠቀመ የለም፤ ኢትዮጵያን አዳክሞ የደከመ እንጂ የበረታ የለም፤ ኢትዮጵያን አደህይቶ የደኸየ እንጂ የበለጸገ የለም፤ ኢትዮጵያን አዋርዶ የተዋረደ እንጂ የተከበረ የለም፤ ይህ የታሪክ ሐቅ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ባለሥልጣኖች ዓላማችሁ ምንድን ነው? እስከዛሬ ድረስ በየትም አገር በሰማይ ጠቀስ መቃብር ውስጥ የተጋደመ ባለሥልጣን የለም፤ ደግሞስ ሰማይ ጠቀስ መቃብር ካስፈለገ ለአንድ ባለሥልጣን ከነቤተሰቡ ስንት ሰማይ ጠቀስ ፎቆች፣ ስንት ሺህ ካሬ ሜትር መሬት ያስፈልጉታል? ከዚህ በፊት ምጽዓት በሚል ግጥም የሚከተለውን አመልክቼ ነበር፡

ከራስ በላይ ነፋስ ትልቁ ሃይማኖት፤

ዘረፋን ሲያውጀው ቂም ሲያስረግዝ ጥቃት፤

ዓይን አያይም አሉ፤ ጆሮም አያዳምጥ፤

ተለጉሞ አንደበት ሁሉም ይዞታል ምጥ!

በቁንጣን፣ በስካር ጥቂቶች ሲንሩ፣

ብዙዎቹ ደግሞ በረሀብ መንምነው በቁንጫ ሲያርሩ፣

የደሀ እንባ ሲጎርፍ መሬቱ ሲሸበር፣

ዝብርቅርቁ ወጣ፤

ሕይወት ትርጉም አጣ፤

ኧረ የት ነው ጉዞው ዓላማው ምንድን ነው?

ቀድመው የሄዱትን ምነው አናያቸው?

የት ገቡ? የት ጠፉ? ፋና እንኳን አይታይ፤

ብልጭ የሚል የለ ከመሬት ከሰማይ!

መንገዱ ጠበበ፤ ትርምስምሱ በዛ፤

እሪታው ኡኡታው ቀለጠ እንደዋዛ!

መሬቱም ዓየሩም በክፋት ጠነዛ!

ጥላቻና ቂሙ በሰፊው ተነዛ፡፡

እምቢልታው ሲጣራ ነጋሪት ሲያገሳ፣

የአለው ሁሉ ሞቶ የሞተው ሲነሣ፣

ምጽዓት መድረሱ ነው ሊስተካከል ነው ፍርድ፤

በግና ፍየሉ ሊለዩ በገሃድ!

እንደሚመስለኝ በአሁኑ ጊዜ ይህንን አቅጣጫ ማየት የሚያዳግተው ሰው በራሱ ላይ ብቻ ሳይሆን፣ በቤተሰቡና በአገሩ ሕዝብ ላይ መቅሠፍትን የሚጠራ ነው፤ እየተማረርን ነው፤ የርኅራኄ ወዛችን እየደረቀብን ነው፤ መጨካከን እንደጀግንነት እየተቆጠረ ነው፡፡

በሌላ ሞት ማለት በሚል ግጥም፡–

ሞት ማለት፡-

አለመናገር ነው፤ ጭው ያለ ዝምታ፣

የመቃብር ሰላም የሬሳ ጸጥታ፤

ደሀ በሰሌኑ ሣጥን ገብቶ ጌታ፤

የውሸት ልዩነት ተጋድሞ በተርታ!

እኔ እንደምገምተው ጉልበተኞች የሆናችሁ ሁሉ ዓላማችሁ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ዓላማ የተለየና በቅራኔ ላይ ያለ አይመስለኝም፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ ብልጽግና፣ እድገትና ክብር የናንተም ነው፤ በየትም አገር ስትሄዱ የሚነጠፍላችሁና የሚጨበጨብላችሁ የኢትዮጵያን ሕዝብ በመወከላችሁ ነው፤ ዛሬ በአውሮፓና በአሜሪካ የኢትዮጵያ ሕዝብ ያለው ክብርና በአጼ ኃይለ ሥላሴ ዘመን የኢትዮጵያ ሕዝብ የነበረው ክብር በጣም የተለየ ነው፤ አጼ ኃይለ ሥላሴ ያገኙትን ክብር ከሳቸው በኋላ የመጡት አላገኙትም፤ ኢትዮጵያንና የኢትዮጵያን ሕዝብ አዋርዶ ከየትም ክብርን ማግኘት አይቻልም፤ የራስን ሕዝብ ንቆ መከበር አይቻልም፤ የራስን ሕዝብ አንገቱን አስደፍቶ ቀና ብሎ መሄድ አይቻልም፡፡

እስር ቤቶችን ሁሉ ዝጉ፤ የዘጋችሁትን አንደበት ሁሉ ልቀቁ፤ ያፈናችሁትን አእምሮ ሁሉ ለነጻነት አብቁት፤ ጭካኔን በርኅራኄ፣ ጉልበትን በእውቀት፣ ዱላን በክርክር፣ ቁጣን በፍትሐዊነት እየለወጣችሁና እያበረዳችሁ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር ታረቁ፤ በተለይ ከኢትዮጵያ ወጣት ጋር ልብ ለልብ ተገናኙ፤ ነገ የወጣቱ ነው፡፡

አይተናል፤ አንበሶች ነን የሚሉ ቀሚስ ለብሰው ሲሸሹ! አይተናል፤ አለኛ ማን? እያሉ ሲወጠሩ የነበሩ እንዳይጥ በጓሮ ተደብቀው የሙጢኝ ሲሉ! አይተናል፤ ጀግኖች ነን ብለው ሲያቅራሩ የነበሩ በየፈረንጅ አገሩ አንገታቸውን አቀርቅረው ትሕትና ሲማሩ! አይተናል፤ የዘረፉትን ሁሉ ሳይበሉ፣ ሳያጌጡበት ሲቸገሩ! አይተናል! ሰምተናል አይደለም አይተናል!

ሌላ ዙር ግፍ ቂምን እየወለደ፣ ቂም በቀልን እየወለደ፣ በቀል አዲስ ግፍን የሚወልድበት ሁኔታ ሲፈጠር ለማየት አንፈልግም፤ በቃን ግፍ! በቃን ቂምና በቀል! በቃን እየተዋረደ የሚያዋርደንን ማየት! በቃን መንፈሳዊ ወኔ በሌላቸው ጉልበተኞች መነዳት! በቃን ጠመንጃቸውን ሲነጠቁ አይጥ የሚሆኑ አሻንጉሊቶች! በቃን በደሀ ጉልበት ጉልበተኞች፣ በደሀ ሀብት ሀብታሞች መስለው የሚታዩ ኅሊና-ቢሶችን መሸከም! እስቲ እኛ ደካማዎቹ ሰዎች እንሁን! አስቲ እናንተም ጉልበተኞች ሰዎች ሁኑልን! እንደሰዎች በሰላም እንድንነጋገር ድፍረቱን፣ መንፈሳዊ ወኔውን ከቅን መንፈስ ጋር እንዲሰጠን እግዚአብሔርን እንለምነው! ክፋትን እንሻረው! ነቢዩ ኢሳይያስ እንዳለው “ለክፉዎች ሰላም የላቸውም፤ ይላል እግዚአብሔር፤” እንዳይሆንብን!

የካቲት 2008

(ምንጭ: Mesfin Wolde-Mariam Blog)

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Comments

  1. eunetu says

    March 24, 2016 06:29 pm at 6:29 pm

    የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ!መካሪና ያለንበትን ሁኔታና ወዴት እየተጓዝን እንደሆነ የሚነግሩን ታማኝና እውነተኛ አዋቂ ሰዎችን ምንጊዜም እግዚ/ር አሳጥቶን አያውቅም። ችግሩ ቆም ብሎ በመስማት ይህን የመሰለውን የአባቶች ምክር ተግባራዊ የሚያደርግ መጥፋቱ እንጂ!እረ እባካች እናንተ የጊዜው ባለጉልበቶች ነገ በራሱ ማንነት ደረሶባችሁ እንዳለፉት ጠቅላይ ሚ/ር አፈር ከመሆናችሁ በፊት ዛሬ በእጃችሁ ውስጥ ያለችውን የዚችን አገር የወደፊት እጣ ፋንታ በመልካም መንገድ በመምራት የማያልፍ ሥራ ባይሆን ለቤተሰባችሁ ሠርታችሁ ለማለፍ ሞክሩ! ማለፋችሁ ላይቀር፤ ያለፈውን የተጠያቂነት በደላችሁን ላንቆጥርባችሁ በኢትዮጵያውያን ስም ቃል እንገባለን!!! እባካችሁ አገር ገላችሁ አብራችሁ የሞት ሙት ከመሞት፤ አገሪቱን አድናችሁ ዳኑ! በታሪ ከመጠየቅም ዳኑ??? የፕሮፌሰሩን አባታዊ ምክርም ሳይመሽ ብትጠቀሙበት ትርፉ በበለጠ ለእናንተና ለልጆቻችሁ መሆኑን ተገንዘቡ??? እግዚ/ር ለናንተና ለሃይማኖት ፈሪ መሪዎቻችን ጭምር ላገር/ለህዝብ ጥቅም እንድታስቡና እንድትሠሩ ማስተዋል ይስጣችሁ። አሜን።

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm
  • የተመሠረተው የፋኖ አደረጃጀት ዋነኛ ዓላማው ድርድር መሆኑ ተነገረ May 14, 2025 11:07 pm
  • ከፍተኛ የፋኖ አመራሮች መገደላቸው ተነገረ May 6, 2025 10:40 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule