• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

የሌላቸው ባለቤቶች (ከበድሉ ዋቅጅራ ሳላስፈቅድ የተዋስሁት)

February 20, 2014 08:36 am by Editor Leave a Comment

በድሉ ዋቅጅራ ‹የሌላቸው ባለቤቶች› የሚል ቅራኔ ውስጥ የገባው ከተጨባጭ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሁኔታ ተነሥቶ ነው፤ አንዳንዴ ሁኔታዎች እያስገደዱን ቅራኔዎችን እንቀበላለን፤ አንድ ጌታ አሽከራቸውን ይጠሩና ባላገር ወደሚኖሩ እናታቸው ዘንድ ይልኩታል፤ ነገር ግን ‹ሞተው ከሆነ እንዳትነግረኝ› ብለው አስጠንቅቀውት ይሄዳል፤ ሴትዮዋ ሞተው ይደርሳል፤ ምን እንደሚያደርግ ግራ ገባው፤ ሲያንሰላስል ብዙ ቀናት ከቆየ በኋላ ጎፈሬውን ለሁለት ከፍሎ ግማሹን ይላጭና ግማሹን ብን አድርጎ ያበጥርና ጌታው ዘንድ ይቀርባል፤ አንዴ ጎፈሬውን እየነካካ፣ አንዴ የተላጨውን እየዳበሰ ጥያቄዎቻቸውን ሲመልስ፣ ጌታው ተቆጡና ‹ምንድን ነው የምታድበሰብሰው አርፈው እንደሁ በወጉ አትነግረኝም!› ብለው ሲጮሁበት ‹አዬ ጌታዬ አርስዎ መቼ በወጉ ላኩኝና!› ብሎ መለሰላቸው።

የበድሉ ‹የሌላቸው› በግማሽ እንደተላጨው ጸጉር ነው፤ ‹ባለቤቶች› ደግሞ እንደግማሽ ጎፈሬው ነው፤ የሌላቸው አላቸው፤ የአላቸው የላቸውም፤ እንደዚህ ያለውን ጉደኛ ሁኔታ እዚያው ጉደኛ ሁኔታ ውስጥ ካለው በቀር ሌላ ሰው አይገባውም፤ መብት ከግዴታ ሲገነጠል መብትም ግዴታም ባሕርያቸውን ለውጠው ሌላ ነገር ይሆናሉ፤ መብትም መሸጦ፣ ግዴታም መሸጦ ሲሆን ከራሱ በቀር ማን ለማን፣ ማን ለምን ኃላፊነት አለበት? መሬቱ ለሙስና ለምለም የሚሆነው እንዲህ እየሆነ ነው፤ ትንሽ መንደር ለትልቅ አገር መመሪያ ሲያወጣና የማንነት ምንጭ ሲሆን ‹‹ኢትዮጵያዊ ዝበሃል መንነት የለን፤›› ብሎ በአደባባይ መናገር ይቻላል፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ሆኖ ኢትዮጵያዊ በሚባል ጋዜጣ ላይ ሀሳቡን እየጻፈ፣ ኢትዮጵያዊ የሚባል ብር እየተቀበለ (በጎን ሊሬም፣ ዶላርም ሊኖር ይችላል፤) ኢትዮጵያዊ የሚባል ምግብ (ማካሮኒም ሊሆን ይችላል) እየበላ፣ ኢትዮጵያ ከምትባል አገር የሚያገኘውን ጥቅም ሁሉ እያግበሰበሰ ‹‹ኢትዮጵያዊ ዝበሃል መንነት የለን፤›› ማለት ይችላል፤ ሀሳቡን የመግለጽ ነጻነት አለው፤ ግን ‹ኢትዮጵያዊ የሚባል ማንነት የለም› ብሎ የሚናገረው ለማን ነው? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው፤ ለኤርትራውያን ነው? ለኢትዮጵያ ወጣቶች ነው? አንዱ የክህደት ትምህርቱ የገባው ወጣት ኢትዮጵያዊነት ዜግነት እንጂ ማንነት አይደለም ብሎ ጻፈልኝ፤ ፊደልን ተምረው ማንበብና መጻፍ ሲጀምሩ ድንቁርናን የሚያነግሡ ሰዎች በተፈጥሮ ያገኙትን ደመ-ነፍሳቸውን እውቀት ያደርጉታል፤ ፊደሉ የእውቀትን በር መክፈቻ መሆኑ ሳይገባቸው ይቀርና ፊደሉን የእውቀት መጨረሻ ያደርጉታል።

‹‹ኢትዮጵያዊ ዝበሃል መንነት የለን፤›› ማለት ኢትዮጵያ ባለቤት የላትም ማለት አይደለም? ይህንን የሚለው ከሌላቸው ‹‹ባለቤቶች›› አንዱ መሆኑ አይደለም? ባለቤቶች ነን የሚሉትንስ ወደባዶነት መለወጥ አይደለም (ሁሉም ዜሮ)? ባለቤት ለመሆን መጀመሪያ ቤቱ ባዶ መሆኑን ማረጋገጥ አስፈላጊ አይደለም? ኢጣልያኑ ቅኝ ገዢ አቶ ሐዲስ ዓለማየሁን ሲያይ ለዓይኑ አልሞላ አሉትና ‹‹ለካ ቤት ባዶ ሲሆን ቁንጫ ያፈራል የሚባለው እውነት ነው!›› አላቸው፤ ሌላው ቢቀር ኢጣልያኑ የተረተው በአማርኛ ነው!

‹‹ኢትዮጵያዊ የሚባል ማንነት የለም፤›› ያለው ሰው ዓላማ አለው፤ ዓላማው ኢትዮጵያን በቁንጫ መሙላት ነው፤ ኢትዮጵያዊ ማንነት ሁሉ ወደቁንጫነት ሲለወጥ እሱ አንድ ቆርቆሮ ፍሊት ይዞ የቁንጫዎች የበላይ ይሆናል፤ ይህንን የሂትለርና የናዚን ፍልስፍና የሚያረጋግጥ ሌላም ነገር አለ፤ ‹‹ትግራዋይነት ዝበሃል ንጹሕ መንነት አለና፤››! ‹‹ትግራዋይነት የሚባል ንጹሕ ማንነት አለን፤›› ማለት ነው፤ ዘረኛነትና ድንቁርና የማይለያዩ መሆናቸውን ማረጋጋጫ ነው፤ እንኳን የትግራይን ሕዝብና ራሱንም አጥርቶ የማያውቅ ሰው ስለ‹‹ንጹሕ›› ማንነት ያወራል፤ እስቲ ‹‹ንጹሕ›› ትግራዋይ የሆኑ ሰዎችን ስም ዘርዝር ቢባል እነማንን አንደሚጠራ አላውቅም፤ የጀርመን ናዚዎች ስለንጹህ የአርያን ዘር የጻፉትን በጥራዝ-ነጠቅነት በዓይኑ ዳብሶት ይሆናል፡፡

ይህንን ዘረኛ ብቻ ሳይሆን ጸረ-ኢትዮጵያ አመለካከት በአደባባይ ያወጣው አንድ የሪፖርተር ጋዜጠኛ ቢሆንም ምንጩ ያው ጋዜጠኛ ብቻ ነው ለማለት ይከብዳል፤ ሰውዬው እንደቧንቧ ከማስተላለፍ ባለፈ ይህንን ሸክም የሚችል አይደለም፤ እንክርዳድን ያበቀለችው መንደር ኢትዮጵያ ውስጥ ናት፤ ሆኖም በዚያች አንድ እንክርዳድን ካበቀለች መንደር ውስጥ ለኢትዮጵያ ህልውና፣ ለኢትዮጵያ ክብር የመጨረሻውን መስዋእትነት የከፈሉ ኢትዮጵያውያን የምንላቸው የሉም? እንደምናውቀው ትግራይ የኢትዮጵያ ማኅጸን ነው፤ ‹‹ኢትዮጵያዊ ዝበሃል መንነት የለን፤›› የሚለው ጉድ ከዚህ ማኅጸን እንዴት በቀለ? የእናት ሆድ ዥጉርጉር ነው ብለን እንዳንተወው የሚቀጥለው ትውልድ ይጎዳል።

አሁን አንድ ጥያቄ ይቀራል፤ ኢትዮጵያዊነት ዜግነት አንጂ ማንነት አይደለም ተብሏል፤ በእውነት ዜግነት ማንነት አይደለም? ጋዜጠኛነት ማንነት አይደለም? እናትነት ማንነት አይደለም? ሚስትነት ማንነት አይደለም? … ማንነትን በጨርቅ ቋጥሮ ከጎሣ ጋር ያቆራኘው ማን ነው? ጎሣም ያለጥርጥር ማንነት ነው፤ ነገር ግን አንዚህን የጠቀስኋቸውንና ሌሎችንም ማንነቶች የሚያጠቃልል ማንነት የለም? ዜግነት አጠቃላይ ማንነት አይባልም? እንዲያውም ከዜግነት በላይ የሆነ ማንነት የለም? ሰውነት ከዜግነት በላይ የሆነ ማንነት አይደለም? ህንድ ከሁለት መቶ በላይ ቋንቋዎች አሉት፤ ከነዚህም ከሀያ እስከሠላሳ የሚሆኑት የራሳቸው ፊደል ያላቸው ናቸው፤ ይህም ሆኖ ማንነታቸው ህንድ መሆኑን ጥያቄ ውስጥ አላስገባባቸውም፤ እንዲሁም ስዊትዘርላንድ አራት የራሳቸው ፊደሎች ያሏቸው ቋንቋዎች ቢኖራቸውም ማንነታቸውን ከስዊስነት አልቀየረውም።

የጎደለ መብት ካለ ያንን ለማሟላት መታገል አንድ ነገር ነው፤ የሁሉም የዜግነት ግዴታ ይሆናል፤ ነገር ግን የኢትዮጵያዊነትን ስሜት ማፍረስ ወይም መሸርሸር ሌላ ነገር ነው፤ በኢትዮጵያዊነት ውስጥ ብዙ የጎደሉና ያልተስተካከሉ ነገሮች ይኖራሉ፤ ኃይላችንን እነዚህን ጉድለቶች ለመንቀስና ለማስተካከል መሞከሩ ከማፈራረሱ የተሻለ አማራጭ ነው።

ባለቤቶች የሌላቸው ከመሆን ወጥተው ያላቸው እንዲሆኑ በማድረግ የተሻለች ኢትዮጵያን መገንባት ይቻላል።

ምንጭ: Mesfin Wolde-Mariam Blog

Filed Under: Opinions Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

Recent Posts

  • ለሱዳንና ኤርትራ ሲከራከሩ የነበሩት አበባው ባለመመረጣቸው “በጣም ተድጃለሁ” አሉ June 26, 2026 12:29 am
  • “ትህነግ ወደ ዓለምአቀፍ ወንጀለኛነትና አሸባሪነት እየተምዘገዘገ ነው” June 25, 2026 01:00 am
  • አሜሪካ በሕገወጡ ትህነግ አመራሮች ላይ ጠንካራ የቪዛ እገዳ ጣለ June 18, 2026 10:29 am
  • እንደ ሌሊት ወፏ የሚንቀሳቀሰው ኢህአፓ/ትብብር   June 18, 2026 09:36 am
  • የታርጋ ጫጫታ June 15, 2026 05:16 pm
  • ፋንታኹን ዋቄ ከአሜሪካ የሃይማኖት እልቂት አወጁ June 15, 2026 02:12 am
  • ሕገወጡ ትህነግ ወጣቶችን ለዳግም ዕልቂት እያሰናዳ ለፈረንጆች “ኢትዮጵያን አውግዙልኝ” እያለ ነው June 11, 2026 12:57 am
  • በሐዘንና ግልፅ ደብዳቤ ስም የተሸፈነ የድህረ ምርጫ ሀገር የማተራመስ ስትራቴጂ June 10, 2026 12:19 am
  • የጽምዶ ልክፍት June 9, 2026 12:49 am
  • ገዳዩ ማነው? አስገዳዩስ ማነው? June 5, 2026 02:37 pm
  • ጽንፈኝነት ግን በኢትዮጵያ ምድር ፈጽሞ ቦታ የለውም! June 5, 2026 01:47 pm
  • የትብብሩ “ብናሸንፍም ፓርላማ አንገባም” መግለጫ “ወንበር ስታጡ ነው” የሚል ከፍተኛ ተቃውሞ አስነሳ June 4, 2026 12:04 am
  • አዲሱ የትራምፕ የምርጫ መመሪያ፡ የአሜሪካ ዲፕሎማቶችን አፍ ያስዘጋ፤ ተቃዋሚዎች ተስፋ ያስቆረጠ June 3, 2026 08:50 pm
  • “ኢህአፓ ከምርጫው በኋላ ይሰነጠቃል” May 29, 2026 07:07 pm
  • ሪፖርተር፡ “ስውር ተልዕኮ” – በከባድ ወንጀል ሊከሰስ May 6, 2026 11:55 pm
  • የፋኖ ኃይል በደረሰበት ጉዳት ሃምሳ ሺህ የሚጠጋ ትጥቅ ጥሎ ጠፋ April 29, 2026 02:27 pm
  • አዲሱ የቴድሮስ ካሳሁን 888 ኮድ፤ እንደ 666?! April 15, 2026 05:53 am
  • ምኑ ነው ያሳቃችሁ፤ ያስደሰታችሁ? April 2, 2026 10:52 am
  • የጀዋር መሃመድ የፖለቲካ ማንነት እና የባዕዳን ተልዕኮ April 2, 2026 10:16 am
  • ከግብፅ በዳያስፖራ ትርምስ ጠማቂዎች በኩል ፋኖ ወደ አዲስ አበባ የላከው “ስጦታ” March 27, 2026 09:14 am
  • “ሰላማዊ ታጋዮቹ” እነ ልደቱ ከአራጁ ሸኔ ጋር ተጣምረዋል March 25, 2026 01:04 pm
  • ጸረ-ኢትዮጵያዊ የሆነው የሪፖርተር አዘጋገብ March 19, 2026 11:54 am
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ የኦሮሚያ የልማት ድርጅቶች March 18, 2026 10:48 am
  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
Copyright © 2026 · Goolgule