• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ሰማቹህ ወይ መርዶ

January 9, 2014 06:50 pm by Editor 4 Comments

ሰማቹህ ወይ መርዶ ? ሀገር ተገምድሎ

ሰማቹህ ? ወይ ነዶ!! ፤ ካገርህ ተከፍሎ

ሀገርህ ተቆርጦ ፤ ለሱዳን ተሰጠ

መንግሥት ነኝ ባለው ፤ ራሱን ባስቀመጠ

ብለው ሲያወሩልኝ ፤ መንፈሴ ተናጠ

አንጎሌ ተናጋ ፤ አቅሌ ተናወጠ

ብርድ ብርድ አለኝና ፤ እያቅለሸለሸ

ወይ ወደላይ አይል ፤ እንዲሁ እያሸ

ባዕድ የሆነ ስሜት ፤ ሲያውከኝ አመሸ

አሳድሮ አዋለኝ ፤ ሰንብቶም አልሸሸ

ይሄን የሀገር ክህደት ፤ ይሄን የሞት ዜና

ሙሾ ልጻፍለት ፤ ብየ ተነሣሁና

ወረቀት ብዕሩን ፤ ካለበት አንሥቸ

ለታሪክ ለትውልድ ፤ ከትቤ ላልፍ ትቸ

ከዚህች ቀን በፊት ፤ በሀገሩ ታሪክ

እንደዚህ ያለ ጉድ ፤ እንዲህ ያለ መታወክ

በገዛ መንግሥቱ ፤ ለባዕድ ሲበረከት

ሽንጥ ገትሮ በሐሰት ፤ ለባዕድ ሲሟገት

ገጥሞት አያውቅምና  ፤ ብዕሩ ተቸገረ

ተጨነቀ ራደ ፤ እንባ አቀረረ

ጉሮሮው ላይ ድንገት ፤ ሳግ ተሰነቀረ

ቀለም ማውጣት ማፍለቅ ፤ አቅቶት አቋረጠ

ወረቀቱም ጮኸ ፤ ኡኡ አለ አመጠ

ከቶ እንዴት አድርጌ ፤ ይሄን እችለዋለሁ ?

ሙሉ የእድሜ ዘመኔን ፤ ተሸክሜ አድራለሁ ?

ብዕሩ ወረቀቱ ፤ እንዲህ ቢቸገሩም

ጨክኜ አስጨንቄ ፤ ግድ ባስጽፋቸውም

በቁጣ ነድጀ ፤ በእልህ ተነሥቸ

ብጽፈው ብጽፈው ፤ ብለው ተደፍቸ

የደረሰብንን ፤ የክህደት ናዳ

የእብደቱን ፍጻሜ ፤ የጉድ ውርደት ዕዳ

የሰብእናውን ዝቅጠት ፤ ጭሉም ድንቁርና

የዜግነቱን ክሽፈት ፤ ከንቱ መሆን መና

የነውሩን ልክ ማጣት ፤ የቁሸቱን ብስና

የሐበሻነት ፍን ደም ፤ እንደሌለው ዳና

ልቡ ውስጥ እንደሌለች ፤ የሀገር ሥዕል ልቀት

ለሕዝብ ለወገን ፤ ነገ የሚባል ምኞት

አጥፍቶ ለመጥፋት ፤ ብቻ ያለውን ቅዠት

የአሸባሪነቱን  ፤ ተወልዶ ያረጀበት

የእፉኝት ልጅነት ፤ የጠላትነቱን

አቻ ተስተካካይ ፤ ምሳሌ አልባነቱን

አልገልጽልኝ አሉ ፤ ያሉ ሁሉ ቃላቱ

ዐቅም አነሳቸው ፤ ብዕሩ ወረቀቱ ፡፡

ተው ስማኝ ሀገሬ ፤ ተው ስማኝ ሀገሬ

ባንተ ነበር እኮ ፤ እስካሁን መኖሬ

የታሪክ አተላው ፤ በሀገር የጨከነ

ለምንም ምን ቢሆን ፤ ነውና ያልታመነ

ከእስካሁን ግብሩ ፤ ሲሆን እንዳየነ

ወገቡን አጥብቆ ፤ ተግቶ እየማሰነ

ሥራ የሚሠራው ፤ ለባዕድ ስለሆነ

ሉዓላዊነትክን ፤ እየደፋፈነ

ብሔራዊ ጥቅምን ፤ ቅርጫ እየተመነ

አንተንም ከመሸጥ ፤ እያፈናቀለ

እንደማይመለስ ፤ ዐውቀህ እንዳበለ

ሀገር የሚያስበጣጥሰው ፤ የያዘው አባዜ

የቀረውን ሰጥቶ ፤ ሳይጨርስ ይሄን ጊዜ

ይሄ ሁሉ ድርጊት ፤ አስረጅ ስለሆነ

እንደበግ ነድቶ ፤ ሳይሸጥህ እየጫነ

ተነሥ በቃ በለው ፤ መቸም ድኖ አልዳነ ፡፡

የቅኝ ግዛት ውል ፤ እኛን እንዲገዛ

ነው የሱ ፍላጎት ፤ ሁከት እንዲበዛ

ታዲያ ፍላጎቱ ፤ ከሆነ እንደዛ

ዓባይ መገደቡ ፤ ውሸት ነዋ ዋዛ ?

ሊያታልልህ ነዋ ፤ ሊያደክም በብዝበዛ ፡፡

ያ የምንኮራበት ፤ የነጻነት ጸጋ

ጥቅም አልባ ነዋ ፤ የከፈልነው ዋጋ ?

አይ ዞር በል ለማለት ፤ መስሎ ለማይታየን

የሐበሻነትን ደም ፤ ፈጥኖ ለሚያፈላብን

ሉዓላዊነትን ፤ ብሔራዊን ምንዳ

ለማስከበር እንጅ ፤ የነጻነት ፋይዳ

ለዚህ ለዚህ እማ ፤ ቅኝ ግዛት ምን ጎዳ ?

የእናት አባቶቻችን ፤ ደምና አጥንታቸው

ለምን ነበር ታዲያ ፤ የተከሰከሰው ?

በከንቱ ነበራ ? ድንበር ላይ የፈሰሰው ?

በቅኝ ገዥ ውል ፤ ከተስማማህማ

ገና ትሰጣለሀ ? የኢትዮጵያን ማማ ?

ሰሜን ደቡብ ምዕራብ ፤ ገጠር ከከተማ ?

ለእንግሊዝ ፈረንሳይ ፤ ለጣሊያን በፊርማ ፡፡

እንደ እነሱ መሻት ፤ ቢሆን ተጣጥሮ

ያሉትን እሽ እያልን ፤ ብንቀበል ኖሮ

ኢትዮጵያ እኮ የለችም ፤ ጠፍታለች ከድሮ

እንቢ ስላልን ነው ፤ አሻፈረኝ ለአውሬ

ነፍሴን እሰጣለሁ ፤ ለኢትዮጵያ ሀገሬ ፡፡

ሀገር ማለት ለኔ ፤ አይደለም መሬቱ

ሀገር ለኔ ሰው ነው ፤ ይሄ ነው እውነቱ

እያልክ የሰበከን ፤ ለዚህ እንደነበረ

ነግሬህ እኮ ነበር ፤ ይህችን እንዳሴረ

ገና ይቀጥላል ፤ ደሞ ለመከረ ፡፡

እሺ አንተ እንዳልከው ፤ ሀገር ማለት ላንተ

ሰው ማለት ከሆነ ፤ ወገን የታተተ

ስለ ሰዉ ስትል ፤ ሳትቸር ሳትፈራ

ከሚገዳደረው ፤ ሊያሰጥም በመከራ

ለምን ሳትቆምለት ? አለኝ ካልክ አደራ ?

ሳትፈነቃቅለው ፤ ከኖረበት ስፍራ ?

ምን ነውሳ ታዲያ ፤ ከገዛ እርሥቱ

ከኖረበት መንደር ፤ ካለበት እትብቱ

ከቀየው አፈናቅለህ ፤ አስቀረኸው ከንቱ ?

ለችጋር ሰጠኸው ፤ የሚያርሰውን አጥቶ ?

አሳልፈህ ልትሰጥ ፤ ላለው ተጎራብቶ ፡፡

ከገዛ ሕዝቡ ይልቅ ፤ ባዕድ የበለጠበት

·ረ ይሄ ምን ጉድ ነው ? አቅል ያሳጣው እብደት ?

ለዋለልህ ውለታ ፤ ለዚህ እንድትበቃ

መክፈልህ ከሆነ ፤ መጥቀምህ ላለቃ

ተው እንዲህ አይደለም ፤ ሀገር አይደል እቃ ?

ተው ለማንም አይበጅ ፤ ላንተም ነው ሰቆቃ

መዘዙ ብዙ ነው ፤ እንዲህ ያል እቃቃ

ባይሆን ገንዘብ ስጠው ፤ ካዝናችን አራቁተህ

ለምን ተብሎ አንልም ፤ ሁሉም ቃል ይግባልህ

መሬት ግን መሬት ነው ፤ ከቶ የማይተካ

ምድር ሀገራችንን ፤ አንዲት ጋት አትንካ ፡፡

አንተም ጎረቤቴ ፤ በቅኝ ገዥህ ሴራ

ተጠልፈህ ወድቀሀል ፤ መዘዝ ጣጣን ፍራ

ያኔ እንዲያ አጠላልፎ ፤ ሲሞክር ሊያስርልህ

ይመስልሀል እንዴ ? ላንተ አስቦልህ ?

ልብ ካለህ አስተውል ፤ እንዳይመስልህ ሊጠቅም

ስትደማ እንድትኖር ነው ፤ በግጭት ዝንተ ዓለም

ይህ ነውና ዓላማው ፤ ፈልግለት መላ

ቅኝ ገዥን ከጠላህ ፤ ሴራውንም ጥላ

የሰላም እጅ ዘርጋ ፤ ይፈር ቡሆው ገላ

ፊቱ እሳት ይምሰል ፤ ዐይኑ እንደ ደም ይቅላ ፡፡

የቆዳ ስፋትህ ፤ ከአፍሪካ አንደኛ

ያንተን ሲሦ ታክል ፤ ሀገር ይዘን እኛ

ያንተን ሦስት ጊዜ እጥፍ ፤ ሕዝብ ታጭቋል ክፉኛ

ምን ጨካኝ ብትሆን ነው ? ምን ያህል ስስታም ?

ባለህ አልረካ ብለህ ፤ ከኛ የሚያምርህ ደም ?

ሀበሻን ተፋቅረህ ፤ በደግ ጉርብትና

ብትኖር ነው የሚሻልህ ፤ እንድትዘልቅ በደኅና ፡፡

ከሞኝ ደጃፍ ሞፈር ፤ ይቆረጣል ላርሶ

ውኃየን በነጻ ፤ መጠጣቱ አንሶ

የተፈጥሮ እኮነው ፤ ብለው እያጃጃሉ

ከውኃ የከበረ ፤ ሌላ እንዳለ ሁሉ

ቀድተን እንውሰድ ቢሉት ፤ ከያዘው ግድቡ

እንደሚሰጥ ሁሉ ፤ ለሁሉ እንደልቡ ፡፡

ለተፈጥሮነቱ ፤ ለሱ ለሱ እማ

እንዲያ በመሆኑም ፤ ነጻ ከተሻማ

ያንተስ ያው አልነበር ፤ በቧንቧ ፈሳሹ

የነዳጅ ዘይትህ ፤ ዶላር አሳፋሹ ?

ማን ይሙትና አሁን ፤ ዓባይ የሚፈሰው

ከእናነንተ ወደኛ ፤ ቢሆን ኖሮ አቅጣጫው

ጠብታ ውኃ መንካት ፤ አልችልም ልቀዳ

ብለህ ትለቃለህ ? ሕዝብህ እየተጎዳ ?

እየተቸገረ ፤ በራብ በጥም ፍዳ ?

ነው ወይስ ትላለህ ፤ ቃልህን በማስገምገም

ሐበሽ እናዝናለን ፤ ለእኛም አልበቃንም

እያልክ ታፌዛለህ ፤ ከዚያው ከደጃቹህ

እንዲያዘንብላቹህ ፤ ዱአ አርጉ ወደ አላህ ?

ይሄን እንደምትል ፤ አልጠራጠርም

በገዛ ገንዘቤ ፤ ደርቀህ ያሲያዘህ ቂም

እንዲህ ያንጨረጨረህ ፤ ያረገህ ስስታም

ጭራሽ ያንተ ቢሆን ነው ? ዘራፍ ማለት ትተህ

ምን ደፋሮች ናቸው ? ሳትለን ተገርመህ

ጠብታ ሳትነካ ፤ መርጠህ መሆን ድሀ

ለእኛ ብለህ አዝነህ ፤ ሰጥተኸን በአምሀ

እኔ ልቸገር ብለህ ፤ የምትሰጠን ውኃ ? ፡፡

ታዲያ ውኃየን ወስደህ ፤ በገዛም መሬቴ

አርሰህ ስትበላ ፤ የእኔ አጥቶ አንጀቴ

ችጋር እየፈጀኝ ፤ ባዶ ሆኖ ቤቴ

ዝም ብየ የማይህ ፤ እንዴት ነው በሞቴ ?

ለዚህ ብልጠታቹህ ፤ ልክና ቅጥ ላጣው

በራስ ወዳድነት ፤ እጅግ ለታወረው

ለከት አብጁለት ፤ መጥፊያህ እንዳያደርገው ፡፡

ጭራሽማ እርሥቴን ፤ ሀገርማ ወስደህ

እሺ እሺ የሚልህ ፤ ዝቃጭ ባንዳ አግኝተህ

እንደምን በሰላም ፤ እንቅልፍ ተኝተህ

እናድራለን ብለህ ፤ ቅዠት አሳሰበህ ?

ወስደህ ላትወስደው ፤ ከነብር አፍ ሥጋ

በከንቱ ባትደክም ፤ ምናለ ባትፈጋ ?

ካላልክ በቀር ይባላኝ ፤ ልጥፋ ቀኔ አይንጋ ፡፡

ከሁለት ያጣ ሆነህ ፤ ከምትቀር ባዶ

ተው ተው ይሻልሀል ፤ መኖሩ ተዋዶ ?

መሬት አልቸገረህ ፤ ሞልቶሀል ጠፍ መሬት

ሕዝብህ አልጠበበው ፤ እንደኛ አጥቶ ጋት

ተው ልብ በል ፍራ ፤ አስብ ለወደፊት ?

ኋላ አይጥ ለሞቷ ፤ ይሆንብሀል ጥፋት

ነገ እኮ ወያኔ ፤ የለም ቋሚ ላንተ

ታጥቆ የሚጠብቅህ ፤ ሸር እየዶለተ ፡፡

ከሊቅ እስከ ደቂቅ ፤ ኢትዮጵያዊ ሁሉ

ለዚህ ነፍሱን የማይሰጥ ፤ እኔ እኔ እያሉ

ይኖር ይመስልሀል ? የማይጸና ቃሉ

ለእናት ኢትዮጵያ ፤ ቀልተው የማይቀሉ ?

ካልመለሰም በቀር ፤ ድንበር ካላጠረ

ከቶም አያርፍልህ ፤ እንደተደፈረ ፡፡

ይሄን ነው የምትሻው ? ዘለዓለም መታጨድ ?

ቀጠናው እንዲታወክ ? ሰላም አጥቶ እንዲነድ ?

ይሄንን ከሆነ ፤ ጠብቀን በል በርታ

ታውቀዋለህ ሐበሻን ፤ እንደማይለቅ ቃታ

የልቡን ሳያደርስ ፤ ሱሪ እንደማይፈታ ፡፡

ክፉ መካሪህን ፤ ቅኝ ገዥን አትስማ

ጎረቤት ይሻላል ፤ ከሩቅ ላንተ ልድማ ፡፡

የነበረን ፍቅር ፤ ያ የጠነከረ

በአንድ አሰልፎን ፤ ቱርክ እየሰበረ

እንዳልሆነ ሆኖ ፤ እንዴት እንደፈረሰ

አታስታውሰውም ? በእሷ ነው የረከሰ ፡፡

ዛሬ ይሄን እንዳቄልክ ፤ አባቱን አቂላ

ቅጥረኛ ሆኖላት ፤ አንተን ተበቅላ

እጅህ የገባውን ድል ፤ ከእጅህ አስጥላ ፡፡

ጥቅምና ጉዳትን ፤ በማሰብ አርቆ

ጉርብትናችንን ፤ ከሸር ጠብቆ

ካሳ እንዳደረገው ፤ በጥበብ እረቆ

መጠንቀቅ ሲገባው ፤ እንደመሪ ልቆ

በአሽከርነቱ ፤ ለፈቃዷ ወድቆ

ሁሌም አብረን ኗሪ ፤ ጎረቤት መሆንክን

እንደቀድሞው ደሞ ፤ አንድ አካልነትህን

መገንዘብ ተስኖት ፤ መያዝ ወዳጅነትህን

በካሳ እንዳረገው ፤ ገልጦ ባንዳነቱን

ምንም በማናውቀው ፤ እንተንና እኔን

ቃልኪዳኑ ፈርሶ ፤ ወዳጅነታችን

ደመኞች አድርገው ፤ አጣልፈው አስቀሩን ፡፡

ተበቅለኸውም ፤ መርሳት አቅቶህ ቂም

ታነፈንፋለህ ፤ ይሄው እስከዛሬም ፡፡

ያውም ገዳማችን ፤ እርእሰ እርእስ

ማኅበረ ሥላሴን ፤ ስንት የያዘውን ቅርስ

ያውም የቴዎድሮስን ፤ የዚያን ጀግና ቀየ

ይሄን ጉድ በሰማ ፤ ይሄን አጀብ ባየ

በነጋ በጠባ ፤ ተሻግሮ እያለፈ

የሚሰፍረውን ባዕድ ፤ እያሰፈሰፈ

እዚያው እየሄደ ፤ ሲያባርር ሲቀጣ

የአባቶቹን እርሥት ፤ ሊያስከብር እንዳናጣ

መድፍን በጎራዴ ፤ ገጥሞ አፍታ ሲያሳጣ

ያውም በሽፍትነት ፤ ዐጤ ሳይሆን ገብቶ

ከጥቂት ፋኖች ጋር ፤ ለኋላ ይሄን ፈርቶ

ጉድ ነው የጉድም ጉድ ፤ ዛሬ የሰው ጎደሎ

ከቶ የማይታሰብ ፤ ይደረጋል ተብሎ

ወገን ነኝ በሚል ፤ ግን ሳይሆን ተማስሎ

ቴዎድሮስ ያላሰበው ፤ ዛሬ በከሀዲ

ሲቋምጥ ለኖረው ፤ ለጠላት መሐዲ

ይግረምህ አሉና ፤ ጭራሽ የእትብት ምድሩን

ሊሰጡ አማራቸው ፤ እይ ድፍረታቸውን ፡፡

የለማ ቋረኛ ፤ የለማ ጎንደሬ

የለማ ሐበሻ ፤ የካሳ ዘር ፍሬ

ሀገር ሲነኩበት ፤ የሚሆነው አውሬ

ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው
ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው

አቅሉ የማያርፍለት ፤ ሳያርደው እንደበሬ

ያ መጠሪያ ስሙ ፤ የዳልጋ አንበሳ

ትንፋሹ የእሳት ላንቃ ፤ ደራጎን እንዳገሳ

እውነት ተሰልቧላ  ፤ ሆኗላ እሬሳ ፡፡

amsalugkidan@gmail.com

Filed Under: Literature Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Comments

  1. Joro yalew says

    January 13, 2014 11:16 pm at 11:16 pm

    ሰላምታዬ ይድረሳችሁ የጎልጉል አዘጋጆች

    የ ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው “ሰማቹህ ወይ መርዶ ግጥም”ና የሚያለቅሰ አይን በኢትየጵያ ካርታ

    ያቀረቡትን ወድጀዋለሁ።

    ሥዕሉ የሳቸው መሆኑን ግን በናንተው አዝጋጆች ትብብር እንድታስታውቁኝ በአክብሮት እጠይቃለሁ።

    Reply
    • Editor says

      January 13, 2014 11:51 pm at 11:51 pm

      Joro yalew

      ለመልክቱ እናመሰግናለን:: ሥዕሉን ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው አይደሉም የላኩልን:: እኛው ከድረገጽ ላይ በፍለጋ ያገኘነው ነው::

      ከሰላምታ ጋር

      አርታኢ/Editor
      ጎልጉል: የድረገጽ ጋዜጣ/Golgul: the Internet Newspaper
      http://www.goolgule.com
      editor@goolgule.com

      Reply
      • Joro yalew says

        January 14, 2014 06:49 am at 6:49 am

        የጎልጉል ድረገጽ ጋዜጣ አዘጋጆችr,
        Thank you for your quick response and good job. It seems like his work, cause the picture is between his name and his poem. The woman who designed this heart touching flyer/ picture, know her very well.
        ከሰላምታ ጋር

        Reply
        • Editor says

          January 14, 2014 07:51 am at 7:51 am

          Dear Joro yalew,

          Many thanks for the info. Please provide us the name of the designer and we would be happy to acknowledge here. The problem with this internet age is you will find things that are posted almost everywhere and it is very difficult to know who the real owner is.

          Kindest regards,

          አርታኢ/Editor
          ጎልጉል: የድረገጽ ጋዜጣ/Golgul: the Internet Newspaper
          https://www.goolgule.com
          editor@goolgule.com

          Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

Recent Posts

  • ለሱዳንና ኤርትራ ሲከራከሩ የነበሩት አበባው ባለመመረጣቸው “በጣም ተድጃለሁ” አሉ June 26, 2026 12:29 am
  • “ትህነግ ወደ ዓለምአቀፍ ወንጀለኛነትና አሸባሪነት እየተምዘገዘገ ነው” June 25, 2026 01:00 am
  • አሜሪካ በሕገወጡ ትህነግ አመራሮች ላይ ጠንካራ የቪዛ እገዳ ጣለ June 18, 2026 10:29 am
  • እንደ ሌሊት ወፏ የሚንቀሳቀሰው ኢህአፓ/ትብብር   June 18, 2026 09:36 am
  • የታርጋ ጫጫታ June 15, 2026 05:16 pm
  • ፋንታኹን ዋቄ ከአሜሪካ የሃይማኖት እልቂት አወጁ June 15, 2026 02:12 am
  • ሕገወጡ ትህነግ ወጣቶችን ለዳግም ዕልቂት እያሰናዳ ለፈረንጆች “ኢትዮጵያን አውግዙልኝ” እያለ ነው June 11, 2026 12:57 am
  • በሐዘንና ግልፅ ደብዳቤ ስም የተሸፈነ የድህረ ምርጫ ሀገር የማተራመስ ስትራቴጂ June 10, 2026 12:19 am
  • የጽምዶ ልክፍት June 9, 2026 12:49 am
  • ገዳዩ ማነው? አስገዳዩስ ማነው? June 5, 2026 02:37 pm
  • ጽንፈኝነት ግን በኢትዮጵያ ምድር ፈጽሞ ቦታ የለውም! June 5, 2026 01:47 pm
  • የትብብሩ “ብናሸንፍም ፓርላማ አንገባም” መግለጫ “ወንበር ስታጡ ነው” የሚል ከፍተኛ ተቃውሞ አስነሳ June 4, 2026 12:04 am
  • አዲሱ የትራምፕ የምርጫ መመሪያ፡ የአሜሪካ ዲፕሎማቶችን አፍ ያስዘጋ፤ ተቃዋሚዎች ተስፋ ያስቆረጠ June 3, 2026 08:50 pm
  • “ኢህአፓ ከምርጫው በኋላ ይሰነጠቃል” May 29, 2026 07:07 pm
  • ሪፖርተር፡ “ስውር ተልዕኮ” – በከባድ ወንጀል ሊከሰስ May 6, 2026 11:55 pm
  • የፋኖ ኃይል በደረሰበት ጉዳት ሃምሳ ሺህ የሚጠጋ ትጥቅ ጥሎ ጠፋ April 29, 2026 02:27 pm
  • አዲሱ የቴድሮስ ካሳሁን 888 ኮድ፤ እንደ 666?! April 15, 2026 05:53 am
  • ምኑ ነው ያሳቃችሁ፤ ያስደሰታችሁ? April 2, 2026 10:52 am
  • የጀዋር መሃመድ የፖለቲካ ማንነት እና የባዕዳን ተልዕኮ April 2, 2026 10:16 am
  • ከግብፅ በዳያስፖራ ትርምስ ጠማቂዎች በኩል ፋኖ ወደ አዲስ አበባ የላከው “ስጦታ” March 27, 2026 09:14 am
  • “ሰላማዊ ታጋዮቹ” እነ ልደቱ ከአራጁ ሸኔ ጋር ተጣምረዋል March 25, 2026 01:04 pm
  • ጸረ-ኢትዮጵያዊ የሆነው የሪፖርተር አዘጋገብ March 19, 2026 11:54 am
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ የኦሮሚያ የልማት ድርጅቶች March 18, 2026 10:48 am
  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
Copyright © 2026 · Goolgule