• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

የደብሪቱ ወተት

September 27, 2013 09:28 pm by Editor Leave a Comment

ሰፈራችንን መሀል ለመሀል ሰንጥቆ ከሚያልፈው መንገድ በስተቀኝ ሃያ አንድ መኖሪያ ቤቶች ይገኛሉ። ከነዚህ ቤቶች ነዋሪዎች ውስጥ ከአብዛኛዎቹ ጋር የስጋ ዝምድና አለን። በተለይ በአንድ ግቢ ውስጥ የምንኖረው ስምንት ቤተሰቦች ደግሞ የቅርብ – በጣም የቅርብ ዘመዳሞች ነን።

በነዚህ ቤቶች ውስጥ አያቶች፣ እናቶች፣ አባቶች፣ አክስቶች፣ አጎቶች፣ አማትና አማቾች ሲኖሩ ከሁሉም የተውጣጣን የልጅ ልጆችም እንገኛለን። ከአጎቶቻችንና ከአክስቶታችን መካከል ሁለቱ ከኛ ዕድሜ ብዙ ስለማይርቁ ቀረቤታችን የጎላ ነው።

አሰግድ ገ/እግዚአብሔርና …

አሰግድ ቀልደኛ ነው። በማንኛውም ጊዜ በትንሹም በትልቁም ነገር እራሱን አዝናንቶ ሌላንም ለማስደሰት ይጥራል። የወጣለት ፀሐፊም ነው። እንደዛሬው የትያትር ጥበብ ሳይስፋፋ በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ከሚሉ ጥቂት ተዋናዮች መካከልም አንዱ ነበር። አሰግድ አጎቴ ብቻ ሳይሆን ከጉርምስናዬ ማግስት ጀምሮ ምርጥ ጓደኛዬም ሆኖ ቆይቷል። ስለ አሰግድ ይቺን ካልኩ ይበቃኛል ወደቤታችን ድራማ ላምራ።

በቤታችን ውስጥ ቀንና ሰዓታቸው ያልተወሰነ፤ አጫጭር ድራማዎች በየጊዜው ይቀርባሉ። እነዚህ ድራማዎች አይጠኑም፤ ተዋናይ ተመርጦ አይመደብባቸውም፤ ፀሐፊና አዘጋጅ የላቸውም። አንዱ ባሻው መንገድ ይጀምረዋል፤ ሌላው አውቆም ሆነ ሳያውቅም ያግዘዋል፤ በቅብብሎሽ ወይም በግል ድራማው ተሠርቶ ይፈጸማል። ድራማው አስቂኝ ቢሆንም የማያቄሙ ተበዳዮችም ይኖሩታል። ብዙ ግዜ ድራማው በልጅ ልጆች የሚቀርብ ሲሆን፤ አሰግድ ድምቀት ሰጭ ሆኖ ያገለግላል።

አንድ ቀን እንዲህ ተሠራ። አንዷ አክስታችን ከመንደሩ ጠዋት ጠዋት የሚመጣላት ወተት በኪራይ ይዛለች። አከራይዋ ወ/ሮ ደብሪቱ ይባላሉ። ደብሪቱ ዝቅአድርጌ። ኃይለኛነታቸው በሰፊው ስለሚወራ ሰው ሁሉ በጥንቃቄ ነው የሚይዛቸው። የወተት ሂሳብ በወቅቱ ያልከፈለ የጭቃ ጅራፋቸውን ስለሚያወርዱበት ከቀኗ ውልፍች አይልም።

አክስቴ ዘንግታው ይሁን በሌላ አጋጣሚ የዛን ወር የወተት ሂሳብ ሳትከፍል ሦስት ቀን አልፏታል። በአራተኛው ቀን ጠዋት ወፍ ሳይንጫጫ የወ/ሮ ደብሪቱ ድምፅ በግቢያችን ውስጥ ተሰማ።

“ወ/ሮ አሰገደች እንደምን አደሩ? ምነው ምነው ትልቅ ስው አይደሉም እንዴ!? ከልጆቼ ጉሮሮ ነጥቄ ያከራየኽዎትን የወተት ሂሳብ ሊበሉኝ ነው? ወይስ ምን ሆነው ነው ሦስት ቀን ሙሉ ያላኩልኝ? ከኔ ከደሃይቱ ይሄን በልተው ምን ሊጠቀሙ ነው? ምነው ጡር አይሆንብዎትም ወይ? ነግሬዎታለሁ! ማንንም የምፈራ እንዳይመስልዎት፤ እንቢ ካሉ ሕግ ፊት ነው የምገትርዎት እከነሽና ደብሪቱ! ‘ግዛኝ ግዣኝ ብለው፣ ሊሸጠኝ አሰበኝ’ አለ ያገሬ ሰው! ዛሬ ባይልኩልኝ ወርድ ከራሴ …” የደብሪቱ ንግግር ማለቂያም የለው …

አክስቴ መግቢያ ቀዳዳ ጠፍቷታል፤ በሹክሹክታ ታወራ ጀመር “ይቺ ሴትዮ ጤናም የላት እንዴ?”

“ምን ጤናም የላት ትያለሽ? ለምንድነው! በወቅቱ ያልከፈልሽው?” ባለቤቷ ደነፋ።

“አንተ ደግሞ ዝም በል። ቢረሳ እንኳን ላኩልኝ ይባላል እንጂ፤ በጠዋት መጥቶ ምን ያስለፈልፋል።” አክስቴ ይበልጥ ጮኸች። የግቢው ቤተሰብ በሙሉ የሴትየዋን እሮሮ እየሰማ ነው። ማንም መልስ ሊመልስ አልፈለገም። ሁሉም አድፍጦ ዝም!

ደብሪቱ ብለው ብለው ድምጻቸው ሲጠፋ መሄዳቸው ስለታወቀ ከየቤቱ ብቅ ብቅ ማለት ተጀመረ። አክስቴ ከሁሉም ቀድማ ነበር ውጪውን የረገጠችው። የወንድሟ ልጅ በራፏ ላይ ቆሟል። “ውይ ሽመልስዬ እዚህ ምን ትሠራለህ? ይቺ እብድ በጠዋት ቀሰቀሰችህ አይደል?” አክስቴ ጥፋተኛነት ተሰምቷታል።

“ምን እኔን ብቻ የሰፈሩ ህዝብ በሙሉ እኮ ነው የተረበሸው! አዋጅ የሚናገሩ ነበር የሚመስሉት። ማን ያልሰማ አለ ብለሽ ነው” ሽመልስ ነገሩን ይበልጥ አደመቀው።

“ጉድ! ጉድ! ጉድ! አዋረደችን እኮ! እስቲ በለሊት መጥቶ አፍ መክፈት ምን አመጣው የሷን ብር ይዤ እንዳልጠፋ ነው? ወይስ ገንዘብ ሆነና እንዳልክድ …?”

“ኧረ! ሕግ ፊት እገትርሻለሁም ብለዋል!”

“ሂድ! አንተ ደግሞ ነገር አታንፏቅ፤ ለሃያ ብር ነው ሕግ ፊት የምትገትረኝ!?”

“እኔ ምን አውቃለሁ፤ ሲሉ የሰማሁትን ነው”

“እሷማ ምን ያላለችው አለ! ቆይ! ግድ የለም! እማደርገውን፤ እኔ ነኝ የማውቅ።” አክስቴ ወደ በሩ አመራች።

“እንዴ አሁን ልትሄጂ ነው እንዴ?” ሸመልስ ነገሩ አላማረውም።

“አሁንማ ምን ይሁን ብዬ እሄዳለሁ። እንደሷ አላበድኩ። እንደው እንዴት እንደገባች በሩን ለማየት እንጂ ቡናዬን ጠጥቼ ቀስ ብዬ እደርሳለሁ። የማደርገውን እኔ ነኝ የማውቅ። ሁለተኛ ግን የሷን ወተት … መርዝ ያስጠጣኝ።”

* * * * * * * * * * *

የአክስቴ ቡና ደርሶ ዘመድ ተሰብስቧል፤ ሁለት ሌሎች አክስቶቼና አንድ አጎቴ እስከሚስቱ ቦታቸውን ይዘዋል። አሰግድ አለ፤ ዙሪያውን በልጅ ልጆች ተከቧል። አያታችን በምርኩዛቸው መሬቱን እያንኳኩ ቀኝ እግራቸውን እየጎተቱ ገቡ። ሁሉም ብድግ ብሎ ተቀበላቸው። ማዕከላዊውን ቦታ ይዘው ከተቀመጡ በኋላ፤ “ጠዋት እንደዛ ትለፈልፍ የነበረችው ማናት?” ጥያቄ አቀረቡ።

“ወ/ሮ ደብሪቱ ናታ” አክስቴ ወ/ሮን ጠበቅ አደረገቻት።

“ምን ይሁን ብላ?” አባባ ነገሩ ገርሟቸዋል።

“አልሰሙም እንዴ ወተት አከራይዋ …

“እኮ ምን ይሁን ብላ መጣች?” አላስጨረሷትም።

“የወተት ኪራይ ሳትከፍይ ዘገየሽ ብላ፤ ልትሳደብ ነዋ! ጨፈረችብኝ እኮ! …”

“ለመሆኑ! በሩን ማን ከፈተላት?”

“እንጃላት! እጇን አስገብታ ከፍታ ወይም አንዱ ወጥቶ ይሆናላ”

“ገብቶ ማለትሽ ነው?” አባባ ወደ አሰግድ ተመለከቱ።

አሰግድ ሽሙጡ ቢገባውም መልስ ሊሰጥ አልፈለገም። “ደግሞ እኮ ስትናገር አንገቷን የታነቀች ነው የምትመስል” አለ አሰግድ፤ የሴትዬዋ ነገር እንዲሰፋ ፈልጓል፤ ሁሉም በጅምላ ሳቀ።

“ኧረ! የሚያንቅ ይነቃትና፤ ስትታይም የታነቀች ነው የምትመስል” የእህቷ መሰደብ ያንገበገባት ትንሿ አክስታችን ነበረች። የአሰግድ ሳቅ ጎልቶ ወጣ።

“አዎን ሳቅ አንተ! ጅብም ሲጎትተኝ ብታይ ሳትስቅ አትቀር። አይ! የኛ ወንድም!” አክስቴ ተናደደችበት።

“አንችስ ለምን ሳትከፍይ ቆየሽ?” አያታችን ሌላ ጥያቄ ወረወሩ።

“እርስት አደረኩት አባብዬ”

“እርስት አደረኩት! አንቺ የረሳሽ እንደሆን እሷም መርሳት አለባት?” ሁሉም ሳቁን ለቀቀው። አባባም በራሳቸው ንግግር ይስቁ ጀመር። ወርቅ ጥርሳቸው ከግራና ከቀኝ እንደ አንፖል ያበራል።

“እናስ! የሆነ እንደሆን ሀገር ጥዬ አልኮበልል፤ በጠዋት መጥቶ መለፍለፍን ምን አመጣው? ቆይ! ግድየለም! የማደርገውን እኔ ነኝ የማውቅ …”

“አክስቴ ገንዘባቸውን ወደዚያ ወርውሪላቸው እንጂ ምንም እንዳትናገሪ” ሽመልስ ጣልቃ ገባ።

“ለምንድነው የማልናገር? አንተን ደግሞ የሷ ጠበቃ ያደረገህ ማነው? ፎቃቃ”

“አይ! ወንድማቸው የአብዮት ጥበቃ ሊቀመንበር ናቸው ሲባል ስለሰማሁ …”

“ታድያ! የሆነስ እንደሆን በጠዋት እየተነሳሽ ሰው ስደቢ ብሎ ፈቅዶላታል ማለት ነው? ማነው ከዘሯ የነገሠ?” ትንሿ አክስት ተንጣጣች። አክስቴ እየተናገረች ሥራዋን አላቋረጠችም። ቁርስ አቅርባ ተበላ። አቦል ቡና ተዳረሰ፤ አሁን ሁሉም ጎኑ ካለው ሰው ጋር ጨዋታ ጀምሯል። አሰግድ ከኛ ጋር እየቀለደ ነው፤ አባባ ጣቶቻቸውን አቆላልፈው ሁለት አውራ ጣቶቻቸውን ማገለባበጥ ይዘዋል።

ሽመልስ ገባ ወጣ ይላል። አክስቴ አልወደደችለትም። “መቀመጫህ ላይ መርፌ የተሰካ ይመስል፤ ምን ያንቆራጥጥሃል? ቡና እያፈላሁ የሚክለፈለፍብኝ አልወድም … ትቀመጥ እንደሆን ተቀመጥ!” ሸመልስ ውጭውን መርጦ ወጣ።

ሁለተኛውና ሦስተኛው ቡና ተፈልቶ ተጠጣ። አክስቴ ስኒውን አነሳስታ፣ እቃውን አጣጥባ ልብሷን ለባብሳ ተነሳች። መሃረቧ ላይ ብር ቋጥራ ያዘች። ወ/ሮ ደብሬ ዛሬ ጉዷ ፈልቷል። ሁለቱ ሌሎቹ አክስቶቼ በዛው የምንደርስበት አለ ብለው ከአክስቴ ጋር ለመሄድ እየጠበቋት ነው። አሰግድ ሥራው ሊሄድ ተዘጋጅቷል። እግረ መንገዱን ግን የደብሬን ጉዳይ ለማየት ፈልጓል። አብዛኛው የልጅ ልጅ በር ላይ እንደዘብ ቆሞ ይሳሳቃል።

በዚህ መሀል ያልታሰበ ነገር ተፈጠረ። የደብሬ ልጅ እንደወትሮዋ ወተቱን በነጭ ጨርቅ ሸፍና በራፋችን ላይ ቆማ ታየች። አክስቴ እንደዛ ተናግረው ካሁን ወዲያ ወ/ሮ ደብሬ ወተት ይልካሉ የሚል ግምት አልነበራትም፤ አብዛኛውም የሚያስበው ይሄንኑ ነው።

አክስቴ ልጅቷን እንደጉድ እያየቻት “አንቺ! …” ብላ ልትናገር ስትጀምር ሸመልስ አንዳች የሚያህል ድንጋይ ይዞ እግሯ ላይ ተከመረ።

“ምንድንነው ነገሩ?” አክስቴ አንባረቀች። ሁሉም ገርሞት ሽመልስ ላይ ዓይኑን ተክሏል።

“አክስቴ ይቅር በይኝ፤ ይቅር በይኝ” ድንጋዩን አስቀምጦ እግሯን አንቆ ያዘ።

“ምንድነው ነገሩ? ጤናም አልያዘኽ? ምኑን ነው ይቅር የምልህ? ኧረ! ይሄ ልጅ አንድ በሉልኝ …” አክስቴ ቆጣ ማለት ጀመረች።

ሁሉም በጥያቄ ያጣድፈው ጀመር፤ ምንድነው? ምን አድርገሃል? አባባ ተነስተው ጎኑን በምርኩዛቸው ጎንተል አደረጉት። ተናደዋል። “ምንድንነው ያደረግኸው? አትናገርም?”

ሽመልስ ይሄን ጊዜ ተነስቶ ቆመ። ፊቱ ፀሐይ ወጥቶ የሚዘንብ ቀን መስሏል። ሳቅም ድንጋጤም ይዞታል።

“ምንድነው ምን አድርገኻል?” የአክስቴ የግንባር ቆዳ ተሰበሰበ።

“ጠዋት …”

“እ … ጠዋት”

“እማማ ደብሬ”

“እ … እማማ ደብሬ ትናገር እንደሆን ተናገር” አክስቴ ይበልጥ ተናደደች።

“እማማ ደብሬ አልመጡም።”

“ታድያ! ማነው እንደዛ ይለፈልፍ የነበረው? እኔ ነኝ እንዳትለኝ ብቻ” አክስቴ አፏን ይዛ ዓይኗን አፈጠጠች።

“አዎን! እኔ ነኝ አክስትዬ ይቅርታ አድርጊልኝ” እንደገና እግሯን አንቆ ያዘ። ሁሉም ሳቁን ለቀቀው አክስቴ እንደመሳቅ እያለች ከእግሯ ላይ ካነሳችው በኋላ እጁን ቀጨም አድርጋ ይዛ “እስቲ እንደጠዋቱ ተናገር” አለችው።

ሽመልስ በአንድ እጁ ጉሮሮውን ይዞ ድምፁን አስተካክሎ መናገር ጀመረ፤ “ወ/ሮ እጅጋየሁ እንደምን አደሩ? ወር ሙሉ ወተቴን ጠጥተው ገንዘቤን ያላኩልኝ ምን ሆነው ነው? ምነው ነውር እማይደል …?”

ጠዋት የተሰማው የደብሪቱ ድምፅ በድጋሚ ግቢውን ሞላው።

(Photo: ILRI – ወ/ሮ ደብሪቱ አይደሉም)

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Social Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ከፍተኛ የፋኖ አመራሮች መገደላቸው ተነገረ May 6, 2025 10:40 pm
  • ሃይማኖትን ለተራ የፖለቲካ ሸቀጥ ማዋል ውርደት ነው April 24, 2025 12:43 am
  •  የኬሪያ ኢብራሒም ኑዛዜ “ብትንትናችን ወጥቷል” April 22, 2025 12:08 am
  • ለወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን አመራሮች ወታደራዊ ሥልጠና ተሰጠ April 16, 2025 11:44 pm
  • ዓቅም እንደሌለው የገመገመው ሻዕቢያ ፊቱን ከጦርነት ወደ ዲፕሎማሲ እያዞረ ነው   April 15, 2025 12:32 am
  • “አንድ የፋኖ ተቋም (የእስክንድር) ተመሥርቷል፤ ሌሎቹ ደግሞ እንዲሁ አንድ ተቋም መሥርተው ወደዚህ ይመጡ” አበበ ጢሞ April 11, 2025 12:07 am
  • መለስ (ለገሰ) ዜናዊ – ተዋርዶ ያዋረደን! April 9, 2025 10:28 pm
  • የተከዜ ዘብ: የሉዓላዊነት መጠበቂያ April 8, 2025 11:49 pm
  • አዲስ አበባ አስተዳደር የሪፖርተርን የተዛባ መረጃ ኮነነ፤ ሕጋዊ እርምጃ እወስዳለሁ አለ April 8, 2025 10:06 pm
  • ሀሰተኛውን የሪፖርተር ዘገባ ንግድ ባንክ በጽኑ ተቃወመ፤ እርማትም ጠየቀ April 8, 2025 09:48 pm
  • “ኦሮሚያ ላይ ወይም ሌላ ቦታ ላይ ስታደርገው ከነበረ ትግራይ ወስጥም የማታደርግበት ምንም ምክንያት አይኖርህም” ነው ጌታቸው ረዳ April 7, 2025 10:22 pm
  • “TPLF’s belief in a strong federal government was always tied to its own dominance in Addis Ababa” April 7, 2025 10:15 pm
  • Counter-Video by EBC Challenges EBS Broadcast, Sparks Public Outcry Over Alleged Misinformation March 31, 2025 02:36 am
  • የኤሊያስ መሠረትን ፌክ መረጃ ማን ያጋልጥ? February 19, 2025 06:00 pm
  • አዘርባጃን፡ የሻዕቢያን ሸምቀቆ ማጥበቂያ?! February 19, 2025 12:29 am
  • የአሜሪካ ድምፅ/ቪኦኤ ይዘጋ ተባለ  February 12, 2025 03:37 am
  • የብልፅግና ፓርቲ ሹመኛ ካድሬዎች February 3, 2025 11:07 am
  • ትግሉን የጎዳው የእስክንድር ነጋ አካሄድ February 3, 2025 10:29 am
  • ኤሊያስ መሠረት “ጭምብሉ ዛሬ ወለቀ”፤ ተከፋይ ነው! February 2, 2025 05:32 pm
  • የፋሲል ግንብ እድሳት እንዴት ተካሄደ? የመንጣቱ ምክንያት? January 23, 2025 03:41 pm
  • ታሪካዊዉ የፋሲል ቤተመንግሥት ለምን ነጣ? January 23, 2025 03:04 pm
  • የኢትዮጵያ አየር መንገድ በተወልደ አስተዳደር ዘመን ለተሠራ ስህተት 425ሺ ዶላር ተቀጣ December 14, 2024 01:44 am
  • በትግራይ ከሞትና ከአካላዊ ጉዳት የተረፉት ለስደት ተዳርገዋል November 27, 2024 12:09 pm
  • የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት አሠራሩን እንዲያርም ጥብቅ መመሪያ ተሰጠው November 27, 2024 11:31 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule