• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

«AmOr!» «አሞር!»

August 30, 2016 12:38 am by Editor Leave a Comment

ወደ ዋናው ርዕሴ ከመግባቴ በፊት በቅድሚያ በወያኔ ጥይት በቅርቡ በግፍ ለረገፉት የአገራችን ጀግና ወጣቶች ጥልቅ የሆነ ሀዘኔን እየገለጽኩ፤ ለቤተሰቦቻቸውና ለመላው ፍትህ፤ ዲሞክራሲና ነፃነት ናፋቂው የኢትዮጵያ ህዝብ እግዚአብሔር መጽናናቱን እንዲሰጠው ከልብ እመኛለሁ፡፡

በጉልበት በሚገዙ አምባገነኖች ስር ያለች አገር የከፋፍለህ ግዛ ፖሊሲ ከጦር ኃይላቸው ባላነሰ ሁኔታ የሚተማመኑበት ስርአታቸውን ይዞ ካቆመው አንዱ ምሰሶ ነው ማለት ይቻላል፡፡ የወያኔንም ስርአት እና ስልጣን ከተሸከሙት ከአምስት ያልበለጡ ምሰሶዎች (the supporting/bearing wall)ውስጥ ይሄ የከፋፍለህ ግዛ ምሰሶ አንዱ ነው፡፡

ሌሎቹ ምሰሶዎች በአጭሩ፦

1)የጦር ኃይሉ፤ ደህንነቱና ካድሬዎቹ

2)ኤኮኖሚው-ያከማቸው የተዘረፈ ገንዘብ፤ ሀብት ንብረት የኢትዮጵያ መሬት በሙሉ

3)ድርጅቱን ከመነሻው የደገፉትና፤ አሁንም በመደገፍ ላይ ያሉ፡፡ ህልውናውን በማወቅ ወይም በመሳሳት ወይም በጥቅም ከራሳቸው ህልውና ጋር ያያያዙ ግለሰቦች፤ ህዝቦች እና የህብረተሰብ ክፍሎች፤ እንዲሁም ሆድ አደሩ

4)የአፍሪካ ቀንድ ሰላም መጥፋት እና እንደ አልሻባብ አይነት አሸባሪ መፈጠሩ በውጭ በተለይም በምዕራባውያን ዓይን የወያኔ እንደ «ዋስትና» መቆጠርም ስርአቱ በከፊልም ቢሆን የሚተማመንበት ሌላው ምሰሶ ይመስለኛል፡፡

አንድን ቤት ወይም ህንጻን ለማፍረስ የተሸከመውን ምሰሶ በግድ ማፍረስ እንደሚያስፈልገው ሁሉ፤ ስርአትንም ለማፍረስ የግድ ስርአቱን የተሸከሙትን ምሰሶዎች ማፍረስ ያስፈልጋል፡፡ የወያኔንም ምሰሶዎች ማፍረስ ካልተቻለ፤ የወያኔን ዕድሜ፤ ህዝብና ተቃዋሚዎች እንደሚመኙት ለማሳጠር አስቸጋሪ ይሆናል፡፡

አንድን ነገር ለማፍረስ በቅድሚያ በቀላሉ መፍረስ ያለበትን ነገር ጠንቅቆ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ከላይ የተገለጹትን ምሰሶዎች በአንዴ ማፍረስ ያስቸግራል፡፡ ግን አንዱን ምሰሶ ብቻ በማፍረስ ስርአቱን ማናጋት ይቻላል፡፡ የአንድ ምሰሶ መፍረስ ስርአቱን በግድ ወደ አንድ አቅጣጫ እንዲያዘነብል (ባላንሱን እንዲያጣ)ያስደርገዋል፡፡ የአንዱ ምሰሶ መፍረስ አጠገቡ ያለውን፤ በተለያየ መዋቅር የተሳሰረውን ምሰሶ ጫና ያሳድርበትና እሱም መናድ ይጀምራል፡፡ ከዚያ በኃላ የተቀሩት ምሰሶዎች መፍረስ ለተፈጥሮ ህግ ብቻ መተው ነው፡፡

ታድያ ዛሬ ህዝባችን በከፍተኛ የወያኔ ወከባና ግድያ ላይ እያለ በቀላሉ ሊያፈርሰው የሚችለው የትኛውን ምሰሶ ነው ብለን ስንጠይቅ የምናገኘው መልስ ይሄ «የከፋፍለህ ግዛ» ምሰሶ ነው፡፡ ይሄ «የከፋፍለ ግዛ» ምሰሶ ልብ ብሎ ላጠናው ሰው፤ ከሌሎቹ ምሰሶዎች በተቃራኒ፤ የወያኔ ስርአት ደካማ ጎን የሚጋለጥበት ነው፡፡ (the weakest link in the system) ይሄን ምሰሶ ከሌሎቹ ምሰሶዎች ጋር ስናወዳድረው፡

1)ምሰሶውን ያቆመው የውሸት ፕሮፖጋንዳና፤ ህዝቡ ዓይኑን ያለመክፈቱ መሆኑ፡

2)በቁሳዊ ንጥረ ነገር ያልታሰረ መሆኑ-ገዢዎች ከፋፍለው ለሚገዙት ህዝብ ሁሉ በገንዘብ     መደለል አለመቻሉ፡፡ ለድለላውም የሚበቃ በቂ ገንዘብ አለመኖሩ፡፡

3)ምሰሶው ሙሉ በሙሉ በገዢዎቹ በወያኔ ቁጥጥር (ግቢ) ውስጥ ባለመሆኑ፡-

ህዝባችን ይህን «የከፋፍለህ ግዛ» ምሰሶ አንድነትን በመመስረት በቀላሉ ሊያፈርሰው ይችላል፡፡

ዋናው ትግል በሰላም እና ለሰላም መሆን እንዳለበት እንደ መሰረታዊ ሀሳብ መወሰድ ያለበት ይመስለኛል፡፡ ግቡም የገዢውን ክፍል፤ ወያኔን ካለምንም ቅድመ ሁኔታ በክብ ጠረጴዛ ዙርያ ስልጣኑን ለህዝብ እንዲያስረክብ ማስደረግ መሆን አለበት፡፡ ህዝብ ጠላቱን ካላወቀ ወዳጁንም አያውቅም፡፡ የኢትዮጵያ ጠላቶች ገዢዎቹ ወያኔዎች እና ወያኔዎች ብቻ ናቸው አራት ነጥብ፡፡

እነሱ የመጡበት ብሔር እነሱ ላመጡት ጣጣ ሰለባ መሆኑ እጅግ በጣም ስለሚያሳዝን፤ የኢትዮጵያ ህዝብ ምን ጊዜም ወያኔንና የመጡበትን ብሔር ለይቶ ማየት አለበት፡፡ በሁለት በኩል አጣብቂኝ ውስጥ የገባውን ብሔር የሞራልና የትብብር ድጋፍ ከምንጊዜውም በበለጠ ሁኔታ በመለገስ የኢትዮጵያን ትልቅ ጨዋነት፤ ባህል፤ ታሪክ እና እምነት ምን ያህል ስር የሰደደና ከዘር ዘር ተላልፎ የመጣ መሆኑን ለዓለም ህዝብ ሁሉ ማስመስከር ያስፈልጋል፡፡

ሁላችንም እንደምናውቀው አንድን ህዝባዊ እንቅስቃሴ ግቡን እንዲመታ ወይም ቢያንስ እንዲያፋጥነው ከሚያስፈልጉት ዋና ዋና ነገሮች አንዱ በአንድ ድምጽ የሚጮህ «slogan» ወይም «የህዝብ ድምጽ» ነው፡፡

ድምጹ ጠንካራ መልዕክት ያዘለና ገዢው ክፍል በጭራሽ መስማት የማይፈልገው፤ ቃሉን ለመያዝ ቀለል ያለ፤ በወረቀትም ለመበተንም ሆነ በግድግዳ ለመጻፍ የቀለለ፤ በሶሻል ሜዲያ በቀላሉ የሚሰራጭ፤ የውስጥም ሆነ የውጭ (ጉዳዩ የማያገባው እንኳን ቢሆን -ለምሳሌ የውጭ ጋዜጠኛ በቀላሉ ሊረዳው እና ለአዳማጮቹ በቀላሉ ማስረዳት የሚችለው)፤ መልዕክቱ ሰምና ወርቅ የያዘ እና በብዙ መንገድ የሚተረጎም፤ ሰላማዊ እና የስምምነትን መልዕክት ያዘለና ብዙሀኑን ህዝብ ያካተተ ቢሆን ይመረጣል፡፡

በታሪክ እንዲህ አይነት ኃይለኛ መልዕክት ያለው ቃል ብዙ ቦታ ተስተውሏል፡፡ እንደ ምሳሌ በ80 ዎቹ ላይ በፖላንድ የተነሳው «ሶሊዳርኖሽች» የሚል የህዝብ ድምጽ ነበር፡፡ በአሜሪካ የፕሬዚዳንት ኦባማም «Yes we can» ን እንደ ምሳሌ መጥቀስ ይቻላል፡፡

ለእኛ ኢትዮጵያውያኖችስ፤ አሁን ተቀጣጥሎ ያለውን ህዝባዊ እንቅስቃሴ እና የአንድነት ፍቅር ለመርዳት ምን አይነት «ሶሊዳርኖሽች» ወይም «Yes we can» ያስፈልግናል?

«AmOr» የሚለው የፍቅርና የኃይል ቃል «የህዝብ ድምጽ» መሆን ያለበት ይመስለኛል፡፡

«AmOr» -አሞር ምን ማለት ነው? AmOr በጣም የቆየ የጥንት ቃል ሲሆን፤ ትርጉሙም «ፍቅር» ማለት ነው፡፡ (ቃሉ የመጣው ከግሪክ እንዲሁም ከላቲን የፍቅር አማልክት ከሚለው ሲሆን)፤ሀይማኖታዊ ትርጉሙ ደግሞ «መተላለፊያ» «ኮሪዶር» «Passage» እንደ ማለትም ይሆናል፡፡

ወደ እኛው አገር ደግሞ ስንመጣ የእንግሊዘኛ ቃላቱን ልብ ካላችሁት፤ «Amhara» አማራ ከሚለው የመጀመሪያውን ሁለት ፊደላት «Am» የሚለውን ወስዶ «Oromo» ከሚለውም እንዲሁ ሁለት ፊደላትን «Or» የሚለውን በመውሰድ የተገነባ ቃል ነው፡፡ «AmOr»! – አሞር በዚህ አተረጓጎም፤የአማራውና የኦሮሞው ፍቅር ማለት ሲሆን፤ የኢትዮጵያ ህዝብ ከወያኔው «ከፋፍለህ ግዛ» በሽታ የሚድንበት መድሀኒት እና ለወያኔ ደግሞ የመሞቻው «መርዝ» ነው፡፡ «AmOr» – አሞር በሀይማኖት መጽሀፍ ደግሞ «መተላለፊያ» ነው ብዬአለሁ፤ ያም ማለት ለአገራችን ከጭቆና እና ከአምባገነን የጉልበተኛ አገዛዝ ወደ ዲሞክራሲ እና የግለስብ ነጻነት ወደሚረጋገጥበት የህዝብ አስተዳደር የምንሸጋገርበት የመተላለፊያ ኮሪዶር ማለት ነው፡፡

ቃሉ ኦሮሞና አማራን ብቻ ነው የሚወክለው ልትሉ ትችላላችህ፡፡ ግን ዋናው ትርጉሙ «ፍቅር» ማለት መሆኑን አትዘንጉ – ፍቅር በሁሉም ብሔሮችና ህዝቦች መካክል፡፡ ሌላው ደግሞ ሁለቱን ትልልቅ የኢትዮጵያ ብሔሮች መወከሉ፤ በእነሱ መካክል ያለው ፍቅር በአገሪቷ ውስጥ ለዘላቂው ለምንመኘውም ባላንሱን የጠበቀ ሰላም ይረዳል፡፡ (በአሜሪካና በረሽያ መካከል ፍቅር ከሰፈነ በመላው ዓለም ሰላም ይሰፍናል እንደማለት እንደሆነው)የኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም የሚረጋገጠው በእነዚህ ሁለት ትልልቅ ብሔሮች መካከል ፍቅር፤ መተማመን፤ መረዳዳት እና የኃላፊነት ስሜት ሲሰፍን ነው፡፡

የኢትዮጵያ ጠላቶችና ጨቋኝ ገዢዎች ይህንን ጉዳይ ከህዝቡ የበለጠ ስለሚያውቁት በተለይ በእነዚህ ብሔሮች መካከል አለመስማማት እንዲሰፍን ያላሰለሰ ጥረት ያደርጋሉ፤ እያደረጉም ነው ያሉት፤ ይሄ ደግሞ ያደባባይ ሚስጥር ነው(በኦሮሞና በአማራ ህዝቦች መካከል በቅርቡ የተፈጠረው የትግል ህብረትን አስመልክቶ «ይሄ የኛን ድክመትና የቤት ሥራችንን አለመስራታችንን ነው የሚያሳየው» በማለት የኢትዮጵያ መንግስት ቃል አቀባይ በንዴትና በቁጭት ሲዘባርቅ ተደምጧል)፡፡ (ሌላም ምሳሌ ካስፈለገ፤ «ጎልጉል» በቅርቡ ባስነበበን ዜና ላይ እነ አባይ ጸሃዬ “አማራና ኦሮሞ ተባበሩብን፤ ሰግተናል” የሚል መረጃ ማስታወስ ይቻላል)፡፡

እንግዲህ ሁሉም አገር ወዳድ AmOr! AmOr! AmOr! የሚለውን ቃል በየአደባባዩ ማሰማት ሲጀምር፤ የወያኔ ጠንካራ ምሰሶ የሚመስለው ቀስ በቀስ መፍረስ ይጀምራል! ያኔውኑ ሌላኛው ምሰሶ (ከአሜሪካንና ከአውሮፓ የሚመጣው የገንዘብም ሆነ የዲፕሎማሲያዊው እርዳታ)መንገዳገድና መፍረስ ይጀምራል፡፡

በመጨረሻም ለመግለጽ የምፈልገው፤ ይህ AmOr «አሞር» የሚለው ቃል የማንንም የፖለቲካ ድርጅት እንደማይወክልና፤ እኔም እንደ አንድ አገር ወዳድ፤ የወንድሞቼና የእህቶቼ ያላግባብ ደም መፍሰስ ካንገበገቡኝ አንዱ በመሆኔ፤ ቃሉን በቅርቡ በግፍ፤ ለመብትና ለነፃነታቸው ሲሉ በወያኔ ጥይት ለረገፉት ጀግና የኦሮሞና የአማራ ወጣቶች መታሰቢያ ይሁናቸው፡፡

ልዑልሰገድ ወልደየስ ሂርጳ

(ከላይ የሚታየው ፎቶግራፍ ከፌስ ቡክ ላይ ተወስዶ አሞር የሚል ጽሁፍ ተጨምሮበታል፤ በፍቶው ላይ ያሉት ሰዎች ከጽሁፉ ጋር ምን ግንኙነት የላቸውም)

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የማርያምን ማዕረግ ዝቅ አደረገች December 12, 2025 09:27 pm
  • ኢህአፓ: ከነጭ ሽብር ወደ “አዲስ አበባ ትናገር” የጎዳና ሽብር? December 12, 2025 09:11 pm
  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule