
በኢትዮ-ሶማሌ ክልል ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ የመጣው የሰብዓዊ መብት ጥሰትና መፈናቀል በክልሉ አስተዳደር በኩል መፍትሔ ተሰጥቶት እንዲስተካከል በፌዴራል መንግሥት በኩል የተለያዩ ጫናዎችና የሽምግልና መድረኮች ላይ የእርቅ ስምምነቶች ሲደረጉ ቆይተዋል። ሆኖም ግን የሰብዓዊ መብት ጥሰቱ ሲብስበት እንጂ ሲቀንስ አልታየም፤ በዚህ ጊዜ ደግሞ የፌዴራል መንግሥት ነገሮችን በቸልታ እንዳያይ የሚያደርገውና ጫን ያለ እርምጃ እንዲወስድ የሚያስችለው የህግ ማዕቀፍ አለው። ይኸውም የፌዴራል መንግሥት በክልሎች ጉዳይ ጣልቃ የሚገባበትን ሁኔታ የሚደነግገው አዋጅ ቁጥር 359/2003 (95) ሲሆን በዚህ አዋጅ መሠረት የፌዴራል መንግሥት በክልሎች ጉዳይ ጣልቃ የመግባት ወሰኑ እስከምን ድረስ እንደሆነ በግልፅ ተደንግጓል።
የፌደራል መንግሥት በክልሎች የሚፈፀሙ ህገመንግሥታዊም ሆነ ሰብዓዊ መብት ጥሰተቶች ሲያጋጥሙ ከሚወስዳቸው እርምጃዎች ውስጥ አንዱ ቅዳሜ ያየነው የመከላከያ ሠራዊት ጣልቃ ገብነት አንዱ ሲሆን ከዚህ ቀጥሎ ሊወሰዱ የሚችሉ ተግባራትስ በምን አግባብ ወደ ህጋዊነት ሊመጡ ይችላሉ የሚለው ነጥብ ዋናውና አንኳሩ ነው። የመከላከያ ሰራዊት ጣልቃ ገብቶ ያረጋጋውን ሰላምና ደህንነት ለማን አስረክቦ ይወጣል? ለክልሉ ፖሊስ ያስረክብ የሚባል ከሆነ ከከዚህ ቀደሙ የከፋ ቀውስ ሊያጋጥመን ይችላል፤ ክልሉንስ ማን ይምራው የሚለው ጥያቄም ሌላኛውና መሰረታዊ ነጥብ ነው።
በአዋጁ አንቀፅ 14(2)(ለ) ስር እንደተደነገገው የፌዴራሉ መንግሥት የክልሉን ምክር ቤትና የክልሉን ከፍተኛ የህግ አስፈፃሚ አካል በማገድ ለፌዴራል መንግስቱ ተጠሪ የሆነ ጊዜያዊ አስተዳደር እንዲቋቋም የመወሰን ስልጣን አለው። ጊዜያዊ አስተዳደሩም ክልሉን በበላይነት ከመምራት ጀምሮ በስልጣን ላይ የነበሩ የአስተዳደር አካላትንና የፀጥታ ክፍል ኃላፊዎችን ለፍርድ እስከማቅረብ የሚደርስ ሥልጣን የሚኖረው ይሆናል።
ስለሆነም የቅዳሜው የመከላከያ ሠራዊት ተልዕኮ ግቡን መምታቱ ሲረጋገጥ በቀጣይ የሚደረገው ተግባር ክልሉን ለጊዜያዊ አስተዳደር የማስረከብ ጉዳይ ይሆናል ማለት ነው።
እነዚህ የሽግግር ሂደቶች ህጋዊነታቸውን ጠብቀው በመሄድ ለክልሉ ሰላም መደፍረስ ዋነኛ ተዋናይ የሆኑ ግለሰቦችን በቁጥጥር ስር በማዋል የክልሉን ሰላምና መረጋጋት የማስቀጠል ኃላፊነት ለፌዴራል መንግስቱ የተሰጠ ስለሆነ በአንዳንድ ወገኖች እየተነሳ ያለው ትችት ህጋዊ መሰረት የሌለው ሲሆን የፌዴራል መንግሥት የዛሬውን እርምጃ ለመውሰድ በመዘግየቱ ቢወቀስ እንጂ አብዲ ኢሌን ጠምዝዞ ከስልጣን በማውረዱ ተጠያቂ መሆን አይችልም። የክልሉ ምክር ቤትም ቢሆን ክልሉን የማስተዳደር አቅሙ ከተሽመደመደ ከህዝብ የተሰጠውን ውክልና እስከመነጠቅ የሚደርስ ተግባር ሊፈፀምበት እንደሚችል ከህጉ መረዳት ይቻላል።
በጋምቤላ ክልል ከአስራ ሶስት አመታት በፊት ተከስቶ የነበረውን የእርስበርስ ግጭት ለማስቆም በማሰብ የወጣው አዋጅ ዛሬ ለሌላ ተግባር ተመዞ የወጣበትን ሁኔታ እያየን ነው።
ይህ በእንዲህ እያለ በፌዴራል መንግሥቱ የሶህዴፓን ወክለው የመንግሥት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ክቡር አቶ አህመድ ሺዴ ክልሉን በጊዜያዊነት ሊመሩ የሚችሉበት ዕድል ሰፊ መሆኑን አንዳንድ ሹክሹክታዎች እየተሰሙ ነው።
በታደሰ ተክሌ የቀረበ ምልከታ፤ ከፌስቡክ ገጹ የተወሰደ።
“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ። ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ™ አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው።
Leave a Reply