• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

በአልቃይዳ ሰበብ ቻይናን መቆጣጠር

February 13, 2013 10:11 am by Editor 6 Comments

የአገራቸውን አጠቃላይ ሁኔታ እና መጪው ጊዜ ምን እንደሚመስል፤ የአገራቸውን የወደፊት የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ፣ የማኅበራዊ፣ … ሁኔታ እንዲሁም አሜሪካ በቀጣይ ዓመታት የምትከተለውን የአጭርና የረጅም ጊዜ የውጪ ፖሊሲ ዕቅድ በተመለከተ ለሁለተኛ ጊዜ ከተመረጡ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ማክሰኞ ምሽት ለምክርቤቱ ንግግር ያደረጉት ፕሬዚዳንት ኦባማ በርካታ ጉዳዮችን ዳስሰዋል፡፡ አፍሪካና ቻይናም የንግግራቸውን ሙሉ ቀልብ የሳቡ ነበሩ ባይባልም ሳይጠቀሱ አልታለፉም፡፡ በተለይ ስለአፍሪካ እንዲህ ብለዋል፤-

‹‹… የተለያዩ አፍቃሪ የአልቃይዳ ወኪሎችና አክራሪዎች ከአረብ ምድር እስከ አፍሪካ ብቅ እያሉ መጥተዋል፤ እነዚህ ቡድኖች ሊያመጡ የሚችሉት አደጋ እንደዚያው እያደገ መጥቷል፡፡ ይህንን አደጋ ለመቋቋምም በአስር ሺዎች የሚጠጉ ልጆቻችንን በመላክም ሆነ አገራትን መቆጣጠር አያስፈልገንም፡፡ ይልቁንም እንደ የመን፤ ሊቢያ እና ሶማሊያ ያሉት አገሮች የራሳቸውን ደኅንነት እንዲያጠናክሩ እንረዳቸዋለን፤ በማሊ እያደረግን እንዳለነው አሸባሪዎችን እየተዋጉ ያሉትን ወዳጆቻችንንም እንደግፋለን፡፡ እንደአስፈላጊነቱም ባለን አቅም ሁሉ በአሜሪካውያን ላይ አደጋ ሊጥሉ በሚችሉ አሸባሪዎች ላይ ቀጥተኛ እርምጃ እንወስዳለን፡፡››

የማሊ ጉዳይ

የፈረንሣይ ወታደሮች ባማኮ ማሊ አየርማረፊያ (ፎቶ: ሬውተርስ)

በአፍሪካዊቷ ማሊ እየተከሰተ ያለው ሁኔታ እጅግ አሳሳቢ ሆኗል፡፡ አሸባሪነትን ማክሸፍ አለብን ብለው የተነሱት ምዕራባውያን ማሊን ከተለያየ አቅጣጫ እያዋከቧት ይገኛሉ፡፡ የቀድሞ ቅኝ ገዢዋ ፈረንሳይ ጦር በመላክ ውጊያውን እየመራች ነው፡፡ ሁሉም እየተጫወቱት ያለው ሙዚቃ ‹‹በአሸባሪነት ላይ ጦርነት ከፍተናል›› የሚል ነው፡፡

እንግሊዝ ጦርነቱ ረጅም ጊዜ ቢፈጅም በዚሁ መቀጠል እንዳለበትና አስፈላጊውም ሁሉ መስዋዕትነት መከፈል አንዳለበት በየሚዲያው እያስተጋባች ትገኛለች፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሯ ዴቪድ ካሜሮን የማሊው ቀውስ ‹‹ወራትን የሚጠይቅ ምላሽ ሳይሆን ዓመታትን እንዲያውም አስርተ ዓመታትን የሚጠይቅ›› እንደሚሆን ተናግረዋል፡፡ ይህንኑ የአገራቸውን ሃሳብ በመደገፍ የብሪታኒያ ልዩ ኮማንዶ ወደ ማሊ በመሄድ የፈረንሣይን ጦር የሚያግዝ ሲሆን ከዚህ በተጨማሪም ሰው ዓልባ የቦምብ ጥቃትና የአየር ላይ ስለላም ታካሂዳለች፡፡

በተመሳሳይ መልኩ አሜሪካም ለጦርነቱ ሙሉ ድጋፍ እየሰጠች ትገኛለች፡፡ ዋሽንግተን ፖስት በቅርቡ እንደዘገበው የአሜሪካው መከላከያ ሚኒስትር ከፈረንሣዩ አቻቸው ጋር ሰሞኑን ባደረጉት ውይይት በአፍሪካ የሚገኘው የአሜሪካ የጦር ዕዝ ማዕከል (አፍሪኮም) ለፈረንሣይ የጦር አውሮፕላኖች አየር ላይ ነዳጅ የመሙላት ድጋፍ እንዲሠጥ ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡ እንዲሁም አሜሪካ ከቻድና ቶጎ ወታደሮችን በማጓጓዝ ተግባር ላይ እንደምትሰማራ ታውቋል፡፡

ይህ እየሆነ ባለበት ወቅት ፕሬዚዳንት ኦባማ በማሊ የሚገኙ አክራሪዎችን ለመዋጋት እንዲያስችል በሚል የአሜሪካንን ምክርቤት (ኮንግሬስ) 32ሚሊዮን ዶላር ዕርዳታ ጠይቀዋል፡፡ ይህ ጥያቄ አሜሪካ በአሁኑ ወቅት በማሊ ለሚገኘው የፈረንሣይ ጦር ከምትረዳውና ከምትሰጠው ድጋፍ ውጪ መሆኑ ነው፡፡

የፈረንሣይ የጦር ሄሊኮፕተሮች በማሊ ክልል ከአየር ላይ የሚያደርጉትን ጥቃት ቀጥለዋል፡፡ መጠለያና መሸሸጊያ የሌላቸው ንጹሃን በአብዛኛው የእስልምና እምነት ተከታይ ማሊያውያን በየጊዜው እያለቁ ይገኛል፡፡ በጥር ወር መገባደጃ አካባቢ የተፈጸመውን አሰቃቂ ጥቃት የዘገበው የአሶሺየትድ ፕሬስ ጋዜጠኛ እንዳለው ከአየር በተካሄደ ጥቃት 11 ሰዎች በአንድ ጊዜ ሲገደሉ አራቱ የአንድ ቤተሰብ አባላት ናቸው፡፡ የዓይን ምስክር ጠቅሶ የዘገበው ጋዜጠኛ ከሟቾቹ ውስጥ ህጻናት እንደሚገኙበትም ተናግሯል፡፡

አሸባሪን በመዋጋት በቻይና ላይ መዝመት

ምንም እንኳን ምዕራባውያን በማሊም ሆነ በሌሎች የአፍሪካ አገራት የሚያካሂዱት የቀጥታ ወረራ ከአሸባሪነት ጋር ለማያያዝ ቢሞክሩም ሁኔታው ግን ሌላ ትርጉም እየተሰጠው መጥቷል፡፡

(Photo: thenakedconvos.com)

በቅርቡ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት ሥልጣን የለቀቁት ሒላሪ ክሊንተን በአንድ ወቅት ሲናገሩ ‹‹የእስያን ዕድገትና ታታሪነት መግታት የአሜሪካ ቀዳሚ የኢኮኖሚና የስትራቴጂ ፍላጎት ነው›› ብለው ነበር፡፡ በዚህ ንግግራቸው ‹‹እስያ›› ብለው በደፈናው ይጥቀሱት እንጂ ዋንኛ የንግግራቸው ዓላማ ቻይና ላይ ያተኮረ እንደሆነ በርካታ የአሜሪካንና የቻይናን የበላይነት እሽቅድምድም የሚያጠኑ የሚናገሩት ነው፡፡

በአሁኑ ወቅት ቻይና ከአፍሪካ ጋር እየመሠረተች ያለው ግንኙነት እየጨመረ ብቻ ሳይሆን እየረቀቀም መጥቷል፡፡ ቀድሞ የምዕራብ አሸርጋጅ የነበሩ የአፍሪካ አምባገነኖች በአሁኑ ወቅት ከኮሙኒስት ቻይና ጋር በንግድና በኢኮኖሚ ብቻ ሳይሆን በአፈና፣ በስለላ እንዲሁም በሙስና እጅና ጓንት እየሆኑ መጥተዋል፡፡ በርካታዎቹ መሪዎች አፍቃሪ ምዕራብ ለመሆን ቢሞክሩም የኮሙኒዝም አራማጅ እንደመሆናቸው የቻይና ወዳጅነት በውጭ ከሚታየው በላይ ውስጣቸው የዘለቀ እንደሆነ በብዙ ፈርጁ እየተመሰከረ ያለ ሁኔታ ነው፡፡

በተለይ ከስድስት ዓመት በፊት ‹‹የቻይና እና የአፍሪካ የትብብር መድረክ›› በማለት ቻይና ወደ ሃምሳ የሚጠጉ መሪዎችንና ሚኒስትሮችን በቤጂንግ በመጥራት ታላቅ ስብሰባ ካካሄደች ወዲህ ምዕራባውያን በተለይም አሜሪካ በጉዳዩ ላይ ከፍተኛ ትኩረት መስጠት ጀመረች፡፡ ወዲያውም የአፍሪኮም ኅልውና ይፋ ሆነ፡፡ ዓላማውም በውጭ ከሚታየው ሌላ በዋንኛነት ቻይና በአፍሪካ የምታደርገውን የኢኮኖሚና የፖለቲካ ተጽዕኖ መከታተል እንደሆነ እምብዛም የተሰወረ አልነበረም፡፡

ቻይና ግን በበኩሏ በአፍሪካ ያላትን እንቅስቃሴ በከፍተኛ ሁኔታ በመቀጠል አቶ መለስን ጨምሮ በርካታ ቀን ምዕራባዊ ማታ ኮሙኒስታዊ የሆኑ መሪዎችን ማሽሞንሞን ቀጠለች፡፡ የሙሉ ቀን የቻይና ወዳጅ ለማድረግም በሁሉም ዘርፍ እንቅስቃሴዋን ገፋች፡፡ የዛሬ አምስት ዓመት ገደማ ቻይና በአፍሪካ ለምታደርገው እንቅስቃሴ ማስፈጸሚያ የሦስት ዓመት ዕቅድ በማውጣት ሦስት ቢሊዮን ዶላር መደበች፡፡ ይህም ቻይና አስቀድማ ከመደበችው ሦስት ቢሊዮን ብድርና ሁለት ቢሊዮን የውጭ ንግድ ዱቤ ሌላ መሆኑን ፕሬዚዳንት ሁ ጁንታዖ በወቅቱ ስምንት የአፍሪካ አገራትን በጎበኙ ጊዜ ያስታወቁት ጉዳይ ነበር፡፡

ቻይና በዚህ አልተገታችም፤ በ2003 መገባደጃ ላይ በተገኘው መረጃ መሠረት ቻይና ከአፍሪካ ጋር ያላት የንግድ ግንኙነት ወደ 170ቢሊዮን ዶላር የደረሰ ሲሆን ባለፉት አስር ዓመታት ብቻ አፍሪካ ለቻይና ኢንዱስትሪዎችን የምትልከው ግብዓት ከ5.6 ቢሊዮን ዶላር ወደ 93ቢሊዮን ዶላር አሻቅቧል፡፡ በሐምሌ 2004ዓም ደግሞ ለሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት ቻይና ለአፍሪካ አገራት ልትሰጥ ያሰበችውን ብድር በእጥፍ በማሳደግ 20ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ መወሰኗን አሳውቃለች፡፡

ይህ እጅግ አሳሳቢ የሆነው ቻይና በአፍሪካ ላይ እያደረገች ያለው ተጽዕኖ ምዕራባውያን በዝምታ የሚያልፉት አይደለም፡፡ በቅርቡ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት የተሾሙት ጆን ኬሪ በአሜሪካው የሕግ መወሰኛ ምክርቤት ለጥያቄ በቀረቡ ጊዜ በተለይ የቻይና እና የአፍሪካን ሁኔታ አስመልክቶ ሲናገሩ ‹‹ቻይና በመላው አፍሪካ ተሰራጭታለች – እውነቴን ነው የምለው በአፍሪካ በሙሉ! በመዓድንና በሌሎች … ጠርታችሁ በማትዘልቁት መስኮች በሙሉ የረጅም ጊዜ ስምምነቶች እየፈረመች ትገኛለች፡፡ እኛ ደግሞ ከጨዋታው ውጪ የሆንባቸው የተወሰኑ ቦታዎች አሉ፤ እንደዚህ ማለቱን ባልወደውም፤ ወገኖቼ በጨዋታው መሳተፍ አለብን›› ብለው ነበር፡፡ አሜሪካና ምዕራባውያን ባጠቃላይ ወደ ጨዋታው ለመግባት ቆርጠው ተነስተዋል፡፡

ይህ ደግሞ ተግባራዊ ሊሆን የሚችለው ‹‹በአሸባሪነት ላይ ጦርነት›› የሚል የሽፋን ስዕል ሲሰጠው ብቻ ነው፡፡ በአፍሪካ ይህንን የሽፋን ስዕል የመጽሐፋቸው መለያ ያደረጉ አገራት ጥቂት አይደሉም፡፡ መንገዱ ሲጨልምበት ቆም ብሎ ከማሰብ ይልቅ ጊዜያዊ ጥቅሙን ብቻ በማየት የሚጓዘው ህወሃት/ኢህአዴግ አገራችንን በዚህ ሽፋን ውስጥ ካስገባትና የቅርብና የሩቅ ጠላቶች በግድ ከፈጠረልን ቆይቷል፡፡ ዞር ብሎ ደግሞ ከቻይና ጋር ተጋብቷል፡፡

‹‹ባለራዕዩ›› መለስ ለሁለቱም ታዛዥና ታማኝ ሆነው የትኛውን አብልጠው እንደሚታዘዙና ለየትኛው እንደሚገዙ ውሉን ሳይዙ አገራችንን ውል አልባ አድርገው አልፈዋል፡፡ የኅልፈታቸውም መነሻ ይህ ነው ባይባልም ከጅምሩ ኮሙኒስታዊ መሆናቸውና ዞረው ወደ ማዖ አገር ፊታቸውን ማቅናታቸው የምዕራባውያን ወዳጅ ሆነው እንደማይቀጥሉ ጉልህ ማስረጃ ነበር፡፡ ምርጫቸውን ሳያስተካክሉ ተሰናበቱ እንጂ፡፡

የምዕራባውያን በተለይም የአሜሪካና የቻይና ፍጥጫ በአፍሪካ ዙሪያ በዚህ መልኩ የጎሪጥ በመተያየት የሚቀጥል አይሆንም የሚሉት የፖለቲካ ተንታኞች በተለይ በፕሬዚዳንት ኦባማ ሁለተኛ የአስተዳደር ዓመታት ወደ ተጨባጭ ደረጃ እንደሚያድግ አስረግጠው ይናገራሉ፡፡ አፍሪካ የአሜሪካና የቻይና ሁሉንዓቀፍ ጦርነት የምታስተናግድ ሆና ስትቀጥል የአገራችንስ መጻዒ ዕድል ምን ይሆን?

(ይህንን ዘገባ ለማጠናቀር በርካታ የሚዲያ ውጤቶችን በዋቢነት ተጠቅመናል፤ ለሚጠይቀንም እናሳውቃለን:: ፎቶ: ጂ. አር)


ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው፡፡ ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (https://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን፡፡

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: News Tagged With: Full Width Top, Middle Column

Reader Interactions

Comments

  1. inkopa says

    February 13, 2013 03:48 pm at 3:48 pm

    ጎልጉሎች እግዜር ይስጣችሁ! በውብ አማርኛ ስለተደገፈው የእውቀት ትጥቅ!!

    Reply
  2. ብስራት says

    February 13, 2013 05:24 pm at 5:24 pm

    ይሄ እኮ የጥቅም ጉዳይ ነው፡፡ የጥሬ እቃ ጉዳይ!! ቻይናም ሆኑ ምእራባውያን የሚፈልጉት ነገር አንድ እና አንድ ነው፡፡ የማይነጥፍ ጥሬ እቃ እና የምጣኔ ሀብት የበላይነት፡፡ ለአፍሪቃ ምርጫው ከዳቢሎስ እና ከሴጣን ምረጥ ነው፡፡ ሁለቱም ጥሬ ሀብት ይፈልጋሉ ውዳቂያቸውን ደሞ ወደ ገበያው ይለቃሉ፡፡ አለቀ፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ነቃ ያሉ ሀገራት ደግሞ ሁለቱንም እያጫወቱ መያዝ ብልህነት ነው፡፡ መለስ እዚህ ላይ የነበረው አቋም ጥሩም ነው ጥሩም አልነበረም፡፡ አንዳቸውን ለአንዳቸው እንደ ማስፈራሪያ እየያዙ ማጫወት ብልህነት ይመስለኛል፡፡ ሌላ ምርጫ ከተገኘ ጥሩ ነው፡፡

    Reply
  3. Daniel Hein says

    February 13, 2013 09:45 pm at 9:45 pm

    which means how it works modern colonialism.
    I deeply regret Mr.Obama

    Reply
  4. Elias says

    February 18, 2013 01:20 pm at 1:20 pm

    በሌላ ኣገላለጽ አፍሪካውያን በተለይ ሙስሊም አፍሪካውያን በዚህ ፍትጊያ ፊዳ ይደረጋሉ ማለት ነው!
    ዎያኔ አህባሽን ኢምፖርት አስደርጎ ሃገር የሚያምሰው ነገር ከዚህ ጋር እንዴት ይሁን የሚያያዘው? ሙስሊም ኢትዮጵያውያን አሸባሪ እየተባሉ በወያኔ ጥይት የሚቆሉበት ሁኔታ ካልኩሌት የተደረገ እንደሆነም ያሳያል ይህ ትንታኔ።

    Reply
  5. zehara elias says

    February 25, 2013 07:04 pm at 7:04 pm

    yes indeed@elias.as elias said when u traceback all incedences(actions) taken by african governments; mali,algeria, ethiopia etc all are parts of these movement. Specialy when we look at current ethiopian muslim movement one can relate it to the above interst of wasternes! Pleas all ethiopians understan these condition and try to support onthe getting ride of this evel wasterners and weyanes acts.God BLESS AND SAVE ETHIOpians.

    Reply
  6. kedir yimer says

    March 6, 2014 02:24 am at 2:24 am

    ጉልጉል በጣም ደስ የሚል እየታየ ያለውን እውት ነው ጥርት አርገህ ያሳየኸን ቀጥልበት

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የተንጋደደው የገዱ መልስ February 6, 2026 03:05 pm
  • ሻዕቢያ “አክሱም ገብቶ ወጣቶች በጅምላ ሲረሽን ጸብ ተፋፍሟል …” February 4, 2026 01:15 pm
  • አደራ ጠባቂው የኢሉአባቦር ሕዝብ February 4, 2026 12:14 pm
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን January 28, 2026 09:56 am
  • በአሜሪካ ጥምር ዜግነት እንዲቀር ጥያቄ ቀረበ January 27, 2026 03:05 pm
  • “ከህወሓት፣ ከሻዕቢያ፣ ከግብፅ ሰዎች ጋር ሆኖ እንዴት የአማራን ጥያቄ ማስመለስ ይቻላል?” ኮሎኔል ፈንታው January 25, 2026 04:23 am
  • የኢትዮጵያ አየር ኃይል: ለአፍሪካ ሀገራት የመጀመሪያዎቹን የአየር ኃይል አብራሪዎች ያሰለጠነ ተቋም January 25, 2026 03:50 am
  • የአማረ ሪፖርተር እያደረሰ ያለው የብሔራዊ ደኅንነት አደጋ January 22, 2026 01:56 am
  • የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የማርያምን ማዕረግ ዝቅ አደረገች December 12, 2025 09:27 pm
  • ኢህአፓ: ከነጭ ሽብር ወደ “አዲስ አበባ ትናገር” የጎዳና ሽብር? December 12, 2025 09:11 pm
  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule