
ባሳለፍነው ሳምንት አሸባሪው የሕወሓት ቡድን ሰብዓዊ ርዳታዎችን ለሚያመላልሱ ተሽከርካሪዎች አገልግሎት የሚውልና በዓለም ምግብ ፕሮግራም መቀሌ መጋዘን የተከማቸ ነዳጅ መዝረፉ ይፋ መሆኑ አይዘነጋም። በወጣው መረጃም ቡድኑ 12 የነዳጅ ቦቴዎችን በአጠቃላይ 570 ሺህ ሊትር ነዳጅ መዝረፉ ነው የተመላከተው።
የፖለቲካና ፌዴራሊዝም ምሁሩ ሀይለየሱስ (ዶ/ር) አዲስ ልሳን ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ አሸባሪው ሕወሓት ከጅምሩ አንስቶ የተለያዩ የስርቆት ወንጀሎችን ሲፈፅም የኖረ መሆኑን አውስተው፤ በተለይ በከፍተኛ የዕለት ደራሽ ድጋፍ ላይ ሲፈፅም የነበረው ዝርፊያ ህዝቡ በረሀብ እንዲያልቅ ከመፍረድ ለይተው እንደማያዩት ነው የገለፁት።
አንድ ፓርቲ፤ አንድ ህዝብ የሚል አስተሳሰብ የቆየና ኮሚኒስታዊ አመለካከት እንደሆነ የሚያስረዱት ምሁሩ አክለው እንዳስገነዘቡት፤ አሸባሪ ቡድኑ አሁን ላይ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ በየትኛውም አግባብ ህዝባዊ ውግንና የሌለውና ስልጣንና ስልጣንን ብቻ ያስቀደመ ነው። ይህንንም “እኛ ስልጣን ካልያዝን ሁሉም ይውደም” የሚል ዓይነት እኩይ ተግባራቸው ማሳያ ነው ይላሉ ምሁሩ።
የሽብር ቡድኑ ከሰሞኑ የፈፀመው የነዳጅ ስርቆት ተግባር አስቀድሞም ሲፈፅመው የነበረ የእኩይ ባህይሪው መገለጫና የነውረኛነቱ ማስታወሻ መሆኑን ያነሱት ሀይለየሱስ (ዶ/ር) የውጭ መንግስታት ተግባሩን ለማውገዝ የሄዱበት ርቀት ግን ለትችት የሚዳርግ ነው ይላሉ። በእርግጥ ዘግይተውም ቢሆን በራሳቸው ላይ ሲደርስ የተወሰኑ እንቅስቃሴዎችን እያደረጉ ቢሆንም ከጉዳዩ ክብደት አንፃር በቂ አይደለም ነው የሚሉት።
በመቀሌ ለሰብዓዊ ድጋፍ ተከማችቶ የነበረ ነዳጅ በሽብር ቡድኑ መዘረፉን አስመልክቶ የዓለም ምግብ ፕሮግራም መረጃውን ይፋ ከማድረጉ ጋር ተያይዞ የተለያዩ አስተያየቶች እየተሰጡ ቢሆንም በትክክል የዚህ ጥፋት ተጠያቂው አሸባሪዉ ሕወሓት ነውና ከድርጊቱ ሊቆጠብ ይገባል የሚል መልዕክት በሁሉም የውጭ አካላት አልተላለፈበትም፤ ይህ መሆኑ ደግሞ ምን ያህል የውጭ ጣልቃ ገብነት እንዳለበት የሚያስገነዝብ ነው ይላሉ።
ያም ሆነ ይህ ግን በአሁኑ ሰዓት ሕወሓት ላይ እየደረሰበት ያለው ውግዘት የመጣውም በቀጥታ በተራድኦ ድርጅቶች አማካኝነት በመሆኑ ተሰሚነቱ ከፍ ይላልና የኢትዮጵያ መንግስት አጋጣሚውን ቸል ሊለው እንደማይገባም መክረዋል። በእንግሊዝኛ ቋንቋ በስፋት እየተሰራጨ ያለውን የቡድኑን የዘረፋ መረጃ በተለያዩ ቋንቋዎች በማስተጋባት የዓለም ማህበረሰብ እንዲረዳ ማድረግ ይገባል ሲሉም መክረዋል።
ህዝቡም ቢሆን ለሀገር መዳን ቅድሚያ ሰጥቶ አሸባሪውን ቡድን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ አደብ ለማስገዛት የሚደረገውን ርብርብ ሊደግፍ ይገባልም ሲሉ ነው ምክራቸውን የለገሱት።
ይህ አሸባሪ ቡድን የትግራይ ህዝብን መበደል ከጀመረ ረጅም አመታትን አስቆጥሯል። ገና ወደስልጣን ለመምጣት ሲያልም ጀምሮ ጦሩን ሊደግፍልኝ ይችላል ያለውን ወንጀል ሁሉ ሲፈፅም እንደነበር ነው ዶ/ር ሀይለየሱስ ያስታወሱት።
ህይወትን ያለምግብና ውሃ ለማቆየት ትግል በሚደረግበት በ1977 ዓ.ም በሕወሓት ታጣቂ ቡድንና በወቅቱ የኢትዮጵያ መንግስት መካከል ከፍተኛ ውጊያ መካሄዱ የሚታወስ ነው። ይህ ወቅት ለበርካቶች የስቃይ ወቅትም ነበር። ሀገሪቷም ምድር ላይ ያለች ሲዖል የሚል ስያሜ ተሰጥቷት እንደነበር ታሪክ ያወሳል። ይህንን የተረዱት አለም አቀፍ ተራድኦ ድርጅቶችም የህይወት አድን ስራን አንድ ብለው ቢጀምሩም መልካም ምግባራቸው ለፅንፈኞች ሲሳይ ነበር የሆነው። የሕወሓት የሽብር ቡድን ተላላኪ የሆኑ ሰዎች ረሀብተኛ አርሶ አደር መስለው በመቅረብ ለትግራይ ህዝብ የዕለት ደራሽ መግዣ እንዲውል የታቀደውን አንድ መቶ ሚሊዮን ዶላር ወደ ህወሓት ካዝና እንዲገባ አድርገዋል።
የፖለቲካ ተንታኝ አንድሪው ቆሪብኮ እኤአ ሰኔ 9 ቀን 2022 ለኢዜአ በሰጡት ማብራሪያ ላይ እንዳመለከቱት፤ አሸባሪው ህወሓት ወደ ቀድሞ የተንኮል ተግባሩ የተመለሰበትን ለሰብአዊ እርዳታ የቀረበን ንብረት ለጦርነት ማዋል ነው። በ1985 በኢትዮጵያ በተከሰተው ረሃብ ወቅት በሰሜን ኢትዮጵያ የተከሰተውን ረሃብ ለመዋጋት ከተሰበሰበው 100 ሚሊዮን ዶላር 95 በመቶውን የጦር መሳሪያ መግዛቱን አስታውሰዋል።
በድርቅ ለተጎዱና ለረሀብ ለተጋለጡ ኢትዮጵያውያን የተሰጠው ይህ ገንዘብ ለዚያን ጊዜ አማፂው ህወሓት የጦር መሳሪያ መግዣ መዋሉን የተለያዩ የፅሁፍና የድምፅ ማስረጃዎች ያመላክታሉ። በመረጃዎቹ መሰረትም አሸባሪው ሕወሓት በረሀብ ለተጎዱና በሞት አፋፍ ላይ ላለዉ የትግራይ ህዝብ ከመጣው የነፍስ አድን እህል መግዣ ውስጥ 95 በመቶ ያህሉን ለጦር መሳሪያ መግዣነት አውሎታል። በዚህ ሳቢያም በርካታ ህፃናትና አዋቂዎች እንደቅጠል እንዲረግፉ ሆነዋል። ይኸን ድርጊት ከፈፀመው 37 ዓመት ቢያልፉትም የተጣባው የዘረፋና ለዜጎች ቅንጣት ታህል አለማሰብ አባዜውን ዛሬም ደግሞታል።
የሽብር ቡድኑ የትግራይ ህዝቦች ይህንና ሌሎች በርካታ የሰቆቃ ጊዜያትን እንዲያሳልፉ ፈርዶባቸዋል። እየፈፀማቸው የመጡ የግፍ ተግባራትም በታሪክ ተከትበዋል።
የዛሬ ዓመት ገደማ የተፈፀመ ሌላ የእለት ደራሽ እህል ምዝበራ የቅርብ የአሸባሪው ህወሓት ነውራዊ ተግባር ማሳያ ነው። አሸባሪው ቡድን ከተሞችን አውድሞና የነዋሪዎችን ሀብት ከዘረፈ በኋላ የዩኤስ ኤይድ የእርዳታ እህል ማከማቻን በመስበር የእለት ደራሽ እርዳታን ዘርፎ ወስዷል።
ባሳለፍነው ሳምንት ረቡዕ ደግሞ ሰብዓዊ ርዳታዎችን ለሚያመላልሱ ተሸከርካሪዎች አገልግሎት የሚውልና በዓለም ምግብ ፕሮግራም መቀሌ መጋዘን የተከማቸ ነዳጅ መዝረፉም ይፋ መሆኑ አይዘነጋም። ዳግም ከተቀሰቀሰው ውጊያ ጋር በተያያዘ ነሀሴ 18 ቀን 2014 ዓ.ም ማለዳ ላይ መቀሌ የሚገኘው የዓለም ምግብ ፕሮግራም መጋዘን በትግራይ ኃይሎች ዘረፋ መፈፀሙንም ያመላከተው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ነው።
የተመድ የሰብአዊ ጉዳዮች ምክትል ዋና ጸሃፊና የአስቸኳይ ድጋፍ አስተባባሪው ማርቲን ግሪፊዝም፤ በመቀሌ በሚገኘው የዓለም የምግብ ፕሮግራም መጋዘን ላይ የተፈፀመውን የነዳጅ ዝርፊያ አውግዘዋል።
ዋና ፀሀፊው በይፋዊ የማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ባሰፈሩት ሃሳብ፤ በትግራይ ክልል መቀሌ በሚገኘው የዓለም ምግብ ፕሮግራም መጋዘን ውስጥ የነበረው ነዳጅ በችግር ውስጥ ላሉ ዜጎች የሰብዓዊ ድጋፍ አገልግሎት ለማድረስ የሚያስችል ነበር ብለዋል። የነዳጁ መዘረፍ የምግብ ዋስትና እጦት እየጨመረ ባለበት በዚህ ወቅት መዘዙ አስከፊ ሊሆን እንደሚችል አመላክተዋል።
በወቅቱ በወጣው መረጃም ቡድኑ 12 የነዳጅ ቦቴዎችን በአጠቃላይ 570 ሺህ ሊትር ነዳጅ መዝረፉ ነው የተመላከተው። ቡድኑ ድርጊቱን የፈፀመው በኃይል በመሆኑ በስፍራው ያሉ አካላት ለመከላከል እንዳልቻሉ ነው መረጃዎች የሚያመላክቱት።
ይህ ሁሉ ሲሆን ዓለም አቀፍ ተቋማት እና የሚመለከታቸው ሃላፊዎቻቸው ድርጊቱ አሳስቦናል ከሚል መግለጫ በስተቀር አንዳች ርምጃ ሲወስዱ አልታዩም። አሸባሪው ሕወሓት አሁን ከፈፀመው ኢሰብአዊ ድርጊት አንጻር አለም አቀፋዊ ጫናዎች እንደሚደረጉ የሚጠበቅ ቢሆንም እስከአሁን በዚያ ደረጃ የተወሰዱ ርምጃዎች የሉም። በዘረፋ ሱስ የተጠመደዉ አሸባሪዉ ሕወሓትም ከኢትዮጵያ መንግስት የቀረበለትን የሰላም አማራጭ በመተዉ በመንግስት ላይ ጦርነት ከፍቷል። (አዲስ ሚዲያ-በየሺ ወልዴ)
Leave a Reply