
የዎላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳጋቶ ኮምቤን ጨምሮ የዞኑ ከፍተኛ አመራሮች ከትላንት በስቲያ በመከላከያ ሠራዊት መያዛቸው ተሰምቷል።
እሁድ አመሻሹን የደቡብ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን እና የደቡብ ክልል ሰላምና ጸጥታ ቢሮ ሃላፊዎች ለደቡብ ቴሌቪዥን በሰጡት መግለጫ የዎላይታ ዞን አመራሮች በዞኑ ኮማንድ ፖስት ዛሬ ከሰዓት መያዛቸውን ተናግረዋል።
በክልሉ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ሃላፊ አለማየሁ ባውዲ እንዳሉት የዞኑ ከፍተኛ አመራሮች የተለያዩ ህገወጥ አደረጃጀቶችን ፈጥረው ግጭት የመቀስቀስ ፍላጎታቸውን እንዲያስፈጽሙ እያደረጉ ነበር ብለዋል።
አመራሮቹ በፓርቲ ደረጃ እንዲሁም በግለሰብ ደረጃ ሀገር ለማፍረስ ከሚንቀሳቀሱ አካላት ጋር ተቀናጅተው በመስራት ላይ ይገኛሉም ሲሉ ገልጸዋል።
አቶ አለማየሁ ሀገር ለማፍረስ የሚሰሩ በማለት ከገለጿቸው ህወኃትና ኦነግ ሸኔ አካላት ጋር በድብቅ ሰው እየላኩ ስብሰባ እንደሚያደርጉ እና ተልዕኮ እንደሚቀበሉ ተናግረዋል። ለዚህም ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት መረጃዎች ተገኝተዋል ብለዋል።
የኮማንድ ፖስቱ ትዕዛዝ በመተላለፍ ህገወጥ ስብሰባዎች እንዲሁም ሰልፎችን እንዳደረጉ ተገልጿል። ህብረተሰቡ የሰጡትን አመራር ቢቀበላቸው አካባቢው ግጭቶች ይፈጠሩ እንደነበር አቶ አለማየሁ ተናግረዋል።
አቶ አለማየሁ ከሕገ መንግሥት ውጭ በመንቀሳቀስ ክልሉን የግጭት ቀጠና ለማድረግ ሲንቀሳቀሱ መቆየታቸውን ገልፀው ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ በተደጋጋሚ ቢነገራቸውም በእኩይ ድርጊታቸው መቀጠሉን ምረጣቸውን አብራርተዋል።
የዞኑ ህዝብ የአመራሩን የጥፋት ተልዕኮ ሳይቀበል መቆየቱን በመጥቀስ ሃላፊው ለህዝቡ ምስጋና አቅርበዋል። በአሁኑ ወቅት ዞኑ በተረጋጋ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ገልፀው ህዝቡ የሰላም እሴቱን እንዲያስቀጥልም ጥሪ አቅርበዋል።
በዛሬው ዕለት (ዕሁድ) በወላይታ ሶዶ ከተማ በቁጥጥር ስር የዋሉት አመራሮችን ጨምሮ 26 ግለሰቦች መሆናቸውን አል አይን ዘግቧል።
ከዚሁ ጋር በተያያዘ ትናንት የዎላይታ ዞን ከፍተኛ አመራሮች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ተከትሎ በሶዶ ከተማ የተከሰተው አለመረጋጋት ዛሬም ጠዋት አንዳንድ ቦታዎች ቀጥሎ የነበረ ሲሆን በአሁን ሰዓት ከተማዋ አንጻራዊ ሰላም መኖሩን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
በወላይታ ዞን በአሁን ሰዓት ብጥብጥ አስነስታችኋል የተባሉ ሰዎች በመከላክያ ኃይል በቁጥጥር ሥር እየዋሉ እንደሆነና እስካሁን በተነሳው ግርግር ስንት ሰው እንደተጎዳ የታወቀ ነገር የለም ትላንት ምሽት ግን አንድ ሰው ሲሞት 14 መቁሰላቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ።
ወላይታ ሶዶ ከተማ ሙሉ በሙሉ አለመረጋጋቷን ማረጋገጥ ችለናል። አሁንም አልፎ አልፎ የተኩስ ድምፅ እንደሚሰማ የቲክቫህ ኢትዮጵያ አባላት አሳውቀዋል።
በዛሬው ዕለት (ሰኞ) ሁለት (2) ሰዎች መሞታቸውን ከአሶሼትድ ፕሬስ ጋዜጠኛ ኤልያስ መሰረት ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል። ሌሎች ግን የሟቾች ቁጥር ከ20 በላይ ነው ይላሉ።
በተጨማሪም ዛሬ በወላይታ ሶዶ ከተማ የንግድ እንዲሁም የትራንስፖርት እንቅስቃሴ አለመኖሩን የቲክቫህ ኢትዮ አባላት አሳውቀዋል።
ከወላይታ ሶዶ ከተማ ወደ ተለያዩ ወረዳዎች የሚደረግ ጉዞ ተቋርጧል/የለም። አሁንም ከፍተኛ ቁጥር ያለው የመከላከያ ሰራዊትና የደቡብ ክልል ልዩ ኃይል በከተማ ውስጥ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል።
(ከተለያዩ መደበኛና የማኅበራዊ ድረገጾች የተጠናቀረ ዘገባ ነው)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
” በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ሃላፊ አለማየሁ ባውዲ . . . ሀገር ለማፍረስ የሚሰሩ በማለት ከገለጿቸው ህወኃትና ኦነግ ሸኔ አካላት ጋር በድብቅ ሰው እየላኩ ስብሰባ እንደሚያደርጉ እና ተልዕኮ እንደሚቀበሉ ተናግረዋል። ለዚህም ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት መረጃዎች ተገኝተዋል ብለዋል”
የጎልኡል አርታኢ ከላይ እንደተጠቀሰው ይንን ያሉት ዓለማየሁ ባውዲ ናቸው፤ ነገር ግን ይጎልጉል “ዜና” አርዕስት መሆኑ ለምን ይሆን? በጥቅስ ምልክት ቢቀመጥም! እንግዲህ የማትወጡት አዳላጭ ዳገት ላይ ስለሆናችሁ ሸርተት በሉና ተደመሩ፤ በልጥጉ፤ ድሮም ካለኛ የለም የዜና ዘላን ነበራችሁ፤ አሁን ጥሩ የመደመር ግጦሽ መሬት ተግኝቷል
ታዛቢ
That is what we did.
Editor