
እንዴት ስነበታችሁ? ስሞኑን በሀገራችን ዙሪያ ከሰማናቸው አስደማሚ ነገሮች አንዱ የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሸን ጉዳይ ነው:: ለዚህም ነው ይህን አጭር ጽሁፍ መሳይ ነገር – የስኳር ነገር ብዬ መስየሜ:: እንግዲህ እንደሰማነው የሰኴር ኮርፖሬሸን ከመከላክያ ብረታ ብረት ኢንጅነሪንግ (ሜቴክ) ጋር በመሳለጥ 77 ቢሊዮን ብር (3. 8 ቢሊዬን የአሜሪካን ዶላር) እንደሰለቀጡ ነው የኦዲት ቢሮም፣ ባለስልጣናቱም ጀባ ያሉን:: በስራ አጋጣሚ ከኮርፖሬሽኑ እና ከሜቴክ ጋር በነበረኝ ግንኝነት ስለ ጉዳዩ የማውቀውን ያህል ለማካፈል እየሞከርኩ ነው:: ከዚህ ጥረቴ አንዱ በቅርቡ በሜይ 23, 2016 በኢሳት አምስተርዳም ስቱዲዮ እንወያይ በሚለው ፕሮግራም ላይ ተካፍዬ ነበር። የዚህ ጽሁፍ አላማም በውውይቱ የጠቀሰኳቸውን ጉዳዬች በተጨማሪም በሰአት ጥበት ምክንያት አልተጠቀሱም ብዬ ያሰብኳቸውን ጉዳዬች ለመዳስስ ነው።
እንግዲህ በህወሐት ጐራ ላለፉት ስድስት (ሰባት) አመታት በትልቁ ሲጐሰሙ ከነበሩ ትላልቅ (ሜጋ) ፕሮጅክቶች የስኳር ኰርፖሬሽን ዋንኛው ነው። በተጨባጭ መረጃዎች መሰረት በላዪም የመንግስት ቱባ ባለስልጣናት እንዳመኑት የስኳር ነገር “ወፍ የለም” እንደሚሉት ከሆነ ከራርሞአል፡፡ አይደለም ሰባት አዳዲስ የስኳር ፋብሪካዎች ይቅርና የነበሩትን “ማስፋፊያ ፕሮጀክት” ብለው ነካክተው ምስቅልቅሉን አውጥተውታል፡፡ “ጥድቁ ቀርቶ በቅጡ በተኰነንኵ” እንዲሉ::
ላለፉት ስባት እና ስድስት አመታት እከሌ የሚባለው ኘሮጀክት ይህን ያህል ተጠናቋል፤ ያኛዉ ደግሞ በሚቀጥለው አመት ማምረት ይጀምርና ይህን ያህል ሚሊዬን ኩንታል ስኳር ወደ ዉጭ አገራት እንልካለን፤ እና የመሳሰሉትን የመግለጫ ጋጋታዎች ለሕዝቡ በስኳር ኰርፖሬሽን እና በሜቴክ የተጋቱ እንደ ስኳር ነጭ የሆኑ ዉሸቶች ናቸዉ። ለምን ይዋሻል? እንጠይቃለን። እስከመቼስ? በዉሸት እንዲህ ያሰከሩንስ ምን ሆኑ? ለዚህ ሁሉ ዉሸት ሐላፊነት ማን ወሰደ? አሁንም እንጠይቃለን። መልስ እስኪገኝ።
ባከነ የተባለዉ ገንዘብስ? 77 ቢሊዬን ብር (3.8 ቢሊዬን ዶላር)። ባከነ የሚለዉ ቃል ለእኔ ብዙ አይመስጠኝም። አማረኛ ማሳመሩን ትተን እዉነቱን በግልፅ አማርኛ መተንፈስ ነው የሚያዋጣው። ስለዚህ ተዘረፈ። ተሰረቀ። ነው የሚባለው። ሜቴክ በስኳር ኳርፖሬሽን ኘሮጀክቶች ስም ከኢትዬጵያ ሕዝብ ላይ ብሎም በሕዝብ ስም የተገኘውን የብድር ብር ዘረፈው ብንል እውነታውን በተሻለ መልኩ ይገለፃል። እንደ እኔ አሁን አማርኛ የምናጣፍጥበት ወቅት ላይ አይደለንም። 20 ሚሊዬን ሕዝብ ተርቦ የሚላስ የሚቀመስ ጠፍቶ፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ለተረጂ ወገኖቻችን የ 1.5 ቢሊዬን ዶላር ያለህ እያለ ሲጮህ፣ ሜቴክ ደግሞ 3.8 ቢሊዬን ዶላር ላፍ አድርጐ አየሁሽ አላየሁሽ እያለ ሲያፌዝብን የምን አማርኛ ማሳመር ነዉ? ምንስ ሊበጀን?
በግሌም ከኮርፖሬሽኑ ጋር ለመስራት የተስማሙ የውጭ ኩባንያዎችን በመወከል እሰራ ስለነበር የዘረፋውን ሒደት ለመታዘብ ችያአለሁ። የውጭ ኩባንያዎችን ወክዬ ከኮርፖሬሽኑ ጋር የተወሰኑትን ፕሮጀክቶች ለመውሰድ ስደራደር፣ ሜቴክ ከኋላ “ቀይዋን ያየ” በሚመስል ጨዋታ ስኳር ኮርፖሬሽን ሆኖ ብቅ አለ። ለካስ ኮርፖሬሽኑ ለስሙ ነው እንጂ ሙሉ በሙሉ በሜቴክ ቁጥጥር ስር ነው። ድርድሩንም፣ ብሩንም ወደ እኔ አለን ሜቴክ በወታደራዊ ቀጭን ትእዛዝ። ያው ወታደሮች አይደል የሚመሩት ወዴት እንደሆነ ባይታወቅም። የሜቴክ ሐላፊዎች የድፍረታቸው ድፍረት ገንዘቡን ብቻ ሳይሆን፣ በብድር ከሚገኘው ገንዘብ ላይ ኢንተረስት ሬትን ለመቀሸብ ሳይቀር ይደራደራሉ!? ወይ ድፍረት! አጃኢብ የሚያሰኝ ነው። በነገራችን ላይ ይህ ብድር በኢትዬጵያ ሕዝብ ስም እና በኢትዬጵያ ሶቨሪን ጋራንቲ (ዋስትና) የሚገኝ ነው። የማላስቸግራችሁ ከሆነ እና በግሌ ከሜቴክ ጋር የገባሁበትን እሰጥ እገባ ወይም ውዝግብ ለማወቅ ከፈለጋችሁ ከኢሳት ጋር ባደረኩት ውይይት በዚህ ማስፈንጠሪያ መኰምከም ይቻላል።
ጐበዝ ይኼ የሙስና ጉዳይ ብቻ አይደለም። በሙስና በሚታሙ አገሮች ሰርቼአለሁ። በእነዚህ አገራት ሌላው ቢቀር ሙስናው እንዴት እንደተከወነ ማየት የሚቻልበት መዋቅር (structure) አለ። በኢትዬጵያ ሁኔታ ይኸ ፈፅሞ አይታይም። ዘረፋው እጅግ አስፈሪ እና አደገኛ ነው። ሕወሐት አገሪቱን በኢኮኖሚ ሴክተሮች በመከፋፈል በምርቃና ፕሮጀክቶች ስም ሰቅዞ ያለማቋረጥ እየዘረፈ እና እየሰረቀ ነው። ስለዚህ ወይ ጉድ!? ወይ ሜቴክ? ወይ ስኳር ኮርፓሬሽን? እያልን በመደመም እንደ ተከታታይ ፊልም የምናየው የሙስና ጉዳይ ብቻ አይደለም። ኢትዬጵያ በዝርፊያ እየተናጠች ነው። የዝርፊያው መጠን እና አካሔድ እንደ አገር የመዝለቃችንን ነገር ፈተና ውስጥ ያስገባ ውስብስብ ቀውስ ነው።
ዳሩ ለውጥ አይቀሬ ነው። እንዲያው በዘገየ ቁጥር ለለዋጩ ሐይል አዲስ ጉልበት ሲጨምር፣ ለተለዋጩ ግን ወደ ማይወጡት ማጥ ውስጥ መነከር ነው። እንዲህ በአገር ላይ እያፌዙ መቀጠል ከቶ አይዘልቅም፣ አያዛልቅም። ለዘራፊዎች ግን አንድ ነገር ልበል። በቅርቡ አቶ አሰፋ ጨቦ “የትዝታ ፈለግ” የሚለውን መጽሐፍቸውን አስመልክተው አንድ ቃለ-መጠይቅ ሲሰጡ የተናገሩት ገጠመኝ ትዝ አለኝ። ደርግ ወድቆ ህወሐት አዲስ አበባን በተቆጣጠረበት ወቅት ነው አሉ። አዲስ አበባ ቀውጢ ሆናለች። እሳቸውም ከእስር የተፈቱበት ሰሞን ነው። እናም የጓደኛቸውን መኪና ይዘው ለመንዳት በአካባቢው ያገኙትን ሰው ቤንዚን የት ማግኘት እንደሚችሉ ይጠይቃሉ። ሰውየውም የት ማግኘት እንደሚችሉ ጠቁሟቸው፣ አንድ ነገር ግን ጠየቃቸው “ለመሆኑ ቤንዚኑን ቀድተህ መኪናውን የት ልትነዳው ነው በዚህ በቀውጢ ጊዜ?” እኔም ኢትዬጵያን እየዘረፉ ያሉትን ዘራፊ ባለስልጣናት ተመሳሳይ ጥያቄ ልጠይቅ። ለመሆኑ ይኼን ሁሉ ዘርፋችሁ የት እና መቼ ልትበሉት ነው?? ሊበላ?! አለች አሉ።
አገራችንን ፈጣሪ ይባርክ።
ወንድማአገኝ እጅጉ። ከ-ስቶኰልም፤ ስዊድን
“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡
Leave a Reply