• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ሉዓላዊነትና መብት

December 5, 2012 03:28 am by Editor Leave a Comment

ሶርያ አሮጌ አገር ነው፤ ታሪኩ ረጅም ነው፤ ከሶርያ ጋር ሲወዳደር አሜሪካ ሕጻን ነው፤ ነገር ግን ለብዙ ወራት በሶርያ ውስጥ የሚካሄደውን ጦርነትና በቅርቡ በአሜሪካ የተደረገውን ምርጫ ስንመለከትና ስናነጻጽራቸው፣ የሶርያ ሕዝብ እርስበርሱ ሲጨራረስ አሜሪካኖች በጥቂት ቀናት ውስጥ ሐዝቡ ድምጹን ሰጥቶ ምርጫው ተጠናቅቆ በሰላም የሥልጣን ርክክብ ተደረገ፤ ዕድሜ የመብሰል ምልክት ላይሆን እንደሚችልና ፍሬ-አልባ እንደሚሆን መረዳት እንችላለን፤ ከርሞ ጥጃ እየሆኑ ዕድሜ መቁጠር፤ በሶርያ የሚካሄደው ጦርነት ግን አንድ ሰው፣ በሺር አላሳድ፣ እስቲሞት ድረስ መጋደሉና አገር መፈራረሱ ይቀጥላል፤ ዓለምም፣ የተባበሩት መንግሥታትም፣ የአረብ ማኅበርም ሁሉም ከንፈሩን እየመጠጠ የሶርያን ሕዝብ ስቃይ ያያል፤ የፍልስጥኤማውያንንም ስቃይ እንዲሁ፡፡

ለምን አንዲህ ይሆናል? ምክንያቱ ሉዓላዊነት የሚባል ነገር ነው፤ ሉዓላዊነት ምን ማለት ነው? በመሠረቱ ሉዓላዊነት ሦስት ሀሳቦችን ያዘለ ይመስለኛል፤ አንዱ ሥልጣን ነው፤ ሁለተኛው ከበላዩ ሌላ ሥልጣንን የማይቀበል ነው፤ሦስተኛው አጥር ነው፤ በኋላ አንደምናየው ሥልጣንም፣ የበላይነትም አጥር አለው፤ ለወጉ ሉዓላዊነት ማለት ራስን ችሎ ከውጭ ድጋፍ ሳይፈልጉ መቆም ነው፤ ከውጭ ምንም ዓይነት የበላይ ሥልጣንን አለመቀበል ነው፤ በአገሮች መሀከል ተደጋግሞ የሚሰማው በራሳችን የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ አትግቡብን እየተባለ መከላከያ የሚሰጠው ከሉዓላዊነት መሠረት በመነሣት ነው፤ በዚህ ዓይነት መልኩ ብዙ ጊዜ ሥራ ላይ ቢውልም በሉዓላዊነት ሀሳብ አጠቃቀም ላይ የተለያዩ አመለካከቶች አሉ፡፡

ሉዓላዊነት የሚለው ሀሳብ ከሁለት በጣም ከተለያዩ መሠረቶች የሚነሣ ነው፤ በአንድ በኩል የሕዝብ ሉዓላዊነት አለ፤ በሌላ በኩል የአገዛዝ ሉዓላዊነት አለ፤ ሕዝብ የአገሩ ባለቤት በሆነበት፣ ሕዝብ በነጻነትና በሕጋዊ ሥርዓት በተካሄደ ምርጫ ተወካዮቹን ሰይሞ ራሱ የሚቆጣጠረውን መንግሥት ባቋቋመበት አገር ሉዓላዊነት ማለት የሕዝብ የሥልጣን የበላይነት ነው፤ ሉዓላዊ፣ የአገሩ ባለቤት፣ የአገሩ የበላይ ባለሥልጣን የሆነ ሕዝብ ማለት ነው፤ በአገሩ የበላይ ባለሥልጣን የሆነ ሕዝብ መንግሥት የሚባል ድርጅት ያቋቁምና ውክልና ይሰጠዋል፡፡

በአንጻሩ በአገዛዝ ስር ያለ ሕዝብ የአገሩ ባለቤት አይደለም፤ ሥልጣንም የለውም፤ የአገሩ ባለቤት ሆኖ ሙሉ ሥልጣንን የጨበጠው አገዛዙ ነው፤ ስለዚህም ሉዓላዊነት የሕዝቡ ሳይሆን የአገዛዙ ነው፤ ነገር ግን ከሕዝቡ የተለየ አገዛዝ የአገር ባለቤት ነው ማለት ለሰሚው ግራ ስለሚሆን የይስሙላ ምርጫ እየተደረገ አገዛዞች ሁሉ ሕዝቦቻቸውን እየረገጡ ለመግዛት (አንዳንዴም በ99.7 ከመቶ እያሸነፉ!) የሚረገጡትን ሕዝቦች ፈቃድ ያገኙ እያስመሰሉ ጡሩምባቸውን ይነፋሉ፤ የሚራብና የሚጠማ፣ የታረዘና የተጎሳቆለ፣ ከዓመት ዓመት በውጭ ምጽዋት የሚኖር፣ በየዕለቱ ግፍን የሚቀበል ሕዝብ ይህ ሁኔታ እንዲቀጥል ፈቃዱን ለአገዛዝ ሰጥቷል ብሎ የሚያምን አገዛዝ ብቻ ነው፡፡

ወደሶርያ ስንመለስ ሕዝቡ የአገሩ ባለቤት አይደለም፤ ስለዚህም ሕዝቡ ሉዓላዊነት የለውም፤ ሉዓላዊነቱን በጉልበት የጨበጠው አገዛዙ ነው፡፡

ዓለም በሙሉ፣ የተባበሩት መንግሥታትም ጭምር የሶርያን አገዛዝ ሉዓላዊ አድርገው ይመለከቱታል፤ እውነተኛው የሉዓላዊነት ባለቤት የሆነው የሶርያ ሕዝብ ሲደቆስ የሐዘን ስሜት ያድርባቸው እንደሆነ እንጂ ሕጋዊ አቅዋም ሊይዙና ሕጋዊ እርምጃ ለመውሰድ ይቸገራሉ፤ አይችሉም፤ ምክንያቱም የሶርያን ሕዝብ ሀብትና ጉልበት ለጊዜው የሚያዝዝበት አገዛዙ ነው፡፡

የተባበሩት መንግሥታት ለትክክለኛው የሉዓላዊነት ባለቤት፣ ለሕዝቡ እውቅና ለምን አይሰጥም? የቂል ጥያቄ ይመስላል፤ በተባበሩት መንግሥታት ውስጥ አብዛኛዎቹን ወንበሮች የያዙት አገዛዞች ናቸው፤ ስለዚህ አገዛዞቹ ለነሱ የተመቸውን ሁኔታ በመለወጥ ራሳቸውን የሚያሰናክሉበት ምክንያት ምን አለ? ይህ አንድ ምክንያት ነው፡፡

ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የአሜሪካና የአውሮፓ ዴሞክራሲያዊ አገሮችም ቢሆኑ በሦስተኛ ዓለም አገሮች ውስጥ የእነሱን ጥቅም ለማራመድ የሚሻላቸው አገዛዝ ነው፤ በዴሞክራሲ አገር ውስጥ ብዙ ውጣ-ውረድና ልፋት ያጋጥማቸዋል፤ ነጻ ጋዜጦች የተለያዩ ሀሳቦችንንና አስተያየቶችን ያናፍሳሉ፤ ምሁራን የተለያዩ ጥናቶችን ለሕዝብ እያቀረቡ ያስተምራሉ፤ የፖሊቲካ ቡድኖች የተለያዩ አስተያየቶችን ለሕዝብ ያስጨብጣሉ፤ እንዲህ ያለው ሁኔታ ለአሜሪካና ለአውሮፓ አገሮች አይመቻቸውም፤ ለእነሱ ቀላል የሚሆንላቸውና የሚመቻቸው ከአንድ አምባ-ገነን ጋር ለብቻ ተነጋግረው የሚያጎርሱትን አጉርሰውት እነሱ በፈለጉት አቅጣጫ የሚዘውሩትን ነው፤ ስለዚህም ለሕዝብ ሉዓላዊነት ግድም የላቸው፤ በአውሮፓና በአሜሪካ የሚገኙት የሰብአዊና የዴሞክራሲ ድርጅቶች ከመንፈሳዊና ከሰብአዊ መሠረት ተነሥተው ጠንካራ ቢሆኑም የፖሊቲካውን ኃይል ሙሉ ለሙሉ መቋቋም አይችሉም፤ ይህ የሚሆነው አምባ-ገነኑ ጠግቦ ወይም በአጋጣሚ ከኃያል መንግሥት ጋር አስኪላተም ድረስ ነው፤ ያን ጊዜ ጉዳቱ ከጥቅሙ ስለሚያመዝን ፊቱን ያዞርበታል፤ በሙባረክ ላይ የደረሰው ይህ ነው፤ ሕዝቡ የጠላው አምባ-ገነን ለአሜሪካና ለአውሮፓም አይበጅም፤ የአምባ-ገነኑን ተፈላጊነት ለማስመስከር ሲሞት ሕዝቡ እንዲያለቅስ ይደረጋል፡፡

ሦስተኛም ምክንያት አለ፤ እንደሩስያና ቻይና ያሉ ኃያላን የሆኑት አገዛዞች ትንሽ ትንሽ እያጎረሱ በንግድ በኩል የሚያገኙትን ጥቅም ለማስጠበቅ የሚመሳሰሏቸውን አገዛዞች ይደግፋሉ፤ ለዚህ ነው ሩስያና ቻይና የአል በሺርን ግፍ ዓይናቸውን ጨፍነው የሚደግፉት፤ እነሱም ቢሆኑ ምጥጥ ከአደረጉት በኋላ የሚጋጥ ነገር ሲጠፋ ወዳጅነታቸውም አብሮ ይጠፋል፡፡

ዓለም-አቀፍ ሕግ እውነተኛውንና በሕዝብ ሥልጣን ላይ የቆመውን ሉዓላዊነት ከመደገፍ ይልቅ ባለጉልበቱን አገዛዝ መደገፍ ይቀናዋል፤ ለዚህ ነው የሰብአዊ መብቶችን በመርገጥ ስማቸው የገነነ አገዛዞች እንኳን በተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ውስጥ አባል ሆነው የሚመረጡት፤ አንዱ ምክንያት እንደተገለጸው የተባበሩት መንግሥታት በአብዛኛው የአገዛዞች ስብስብ ስለሆነ ወር-ተራ እየገቡ በመረዳዳታቸው ነው፤ ሌላው ምክንያት ምናልባት ከስብሰባዎቹ ይማሩ ይሆናል የሚል አጉል ተስፋ ነው፡፡

ሉዓላዊነትን የምናይበት ሌላ መንገድም አለ፤ ሕዝብ ሉዓላዊ ነው ስንል ምን ማለታችን ነው? ሕዝብ ማለት እያንዳንዱ ዜጋ በእኩልነት ቆሞ የሚታይበት ስብስብ ነው፤ሰው በዜግነቱ ሰውነቱን አያጣም፤ ሰውነቱ የተፈጥሮ ሲሆን ዜግነቱ በሕግ የተከለለ ነው፤ ዜጋ ማለት በሕግ የታጠረ ሰው ነው፤ ግለሰብ የምንለው ነጠላው ሰው ሰውም ነው ዜጋም ነው፤ ስለዚህም ለአንድ አገርም ሆነ ለአንድ ሕዝብ የሉዓላዊነቱ መሠረት እያንዳንዱ ዜጋ ነው፤ ከሉዓላዊነት ተነሥተን ወደሰውነት ደረጃ ስንገባ (ሰዎችን ሁሉ እኩል አድርገን) እያንዳንዱ ሰው ሰብአዊ መብቶች አሉት፤ እነዚህ መብቶች የሰው ልጆችን ሁሉ በአንድ ላይ ይዘው በሰውነት የታጠሩ ናቸው፤ ቀጥለን ወደአገር ደረጃ ስንወርድ ደግሞ ሰብአዊ መብቶች ዜጎችን ሁሉ በእኩልነት ይዘው በዜግነት የታጠሩ ይሆናሉ፤ በሰውነት ደረጃ በሰዎች መሀከል ልዩነት የለም፤ በዜግነት ደረጃም በዜጎች መሀከል ልዩነት የለም፡፡

ወደሶርያ ጉዳይ ስንመለስ ተጽእኖ ለማድረግ የሚችለው የዓለም-አቀፍ ማኅበረሰብ ሶርያን የሚመለከተው በሰውነት ደረጃም ሆነ በዜግነት ደረጃ አይደለም፤በጥቅም መለኪያ ነው፤ ለዚህ ነው የሶርያ ሕዝብም ሆነ የፍልስጥኤማውያን ሕይወት ዋጋ-ቢስ የሆነው፤ ለዚህ ነው በአገሩ ውስጥ የባለቤትነት መብት የሌለው ግለሰብ በሕዝብነት ወይም በዜግነት ደረጃ ውስጥ ሲገባ ገለባ የሚሆነው፤ ለገለባ ማንም ግድ የለው፡፡

ሰብአዊ መብቶች ተጣሱ ወይም ተረገጡ የሚባለው በግለሰብ ደረጃ ያለውን አጥር፣ በዜግነት ደረጃ ያለውን አጥር፣ በሰውነት ደረጃ ያለውን አጥር የሚያፈርስ ለሕግ ግድ የሌለው ጉልበተኛ ሲነሣ ነው፤ ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ!

Mesfin Woldemariam Blog

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ከፍተኛ የፋኖ አመራሮች መገደላቸው ተነገረ May 6, 2025 10:40 pm
  • ሃይማኖትን ለተራ የፖለቲካ ሸቀጥ ማዋል ውርደት ነው April 24, 2025 12:43 am
  •  የኬሪያ ኢብራሒም ኑዛዜ “ብትንትናችን ወጥቷል” April 22, 2025 12:08 am
  • ለወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን አመራሮች ወታደራዊ ሥልጠና ተሰጠ April 16, 2025 11:44 pm
  • ዓቅም እንደሌለው የገመገመው ሻዕቢያ ፊቱን ከጦርነት ወደ ዲፕሎማሲ እያዞረ ነው   April 15, 2025 12:32 am
  • “አንድ የፋኖ ተቋም (የእስክንድር) ተመሥርቷል፤ ሌሎቹ ደግሞ እንዲሁ አንድ ተቋም መሥርተው ወደዚህ ይመጡ” አበበ ጢሞ April 11, 2025 12:07 am
  • መለስ (ለገሰ) ዜናዊ – ተዋርዶ ያዋረደን! April 9, 2025 10:28 pm
  • የተከዜ ዘብ: የሉዓላዊነት መጠበቂያ April 8, 2025 11:49 pm
  • አዲስ አበባ አስተዳደር የሪፖርተርን የተዛባ መረጃ ኮነነ፤ ሕጋዊ እርምጃ እወስዳለሁ አለ April 8, 2025 10:06 pm
  • ሀሰተኛውን የሪፖርተር ዘገባ ንግድ ባንክ በጽኑ ተቃወመ፤ እርማትም ጠየቀ April 8, 2025 09:48 pm
  • “ኦሮሚያ ላይ ወይም ሌላ ቦታ ላይ ስታደርገው ከነበረ ትግራይ ወስጥም የማታደርግበት ምንም ምክንያት አይኖርህም” ነው ጌታቸው ረዳ April 7, 2025 10:22 pm
  • “TPLF’s belief in a strong federal government was always tied to its own dominance in Addis Ababa” April 7, 2025 10:15 pm
  • Counter-Video by EBC Challenges EBS Broadcast, Sparks Public Outcry Over Alleged Misinformation March 31, 2025 02:36 am
  • የኤሊያስ መሠረትን ፌክ መረጃ ማን ያጋልጥ? February 19, 2025 06:00 pm
  • አዘርባጃን፡ የሻዕቢያን ሸምቀቆ ማጥበቂያ?! February 19, 2025 12:29 am
  • የአሜሪካ ድምፅ/ቪኦኤ ይዘጋ ተባለ  February 12, 2025 03:37 am
  • የብልፅግና ፓርቲ ሹመኛ ካድሬዎች February 3, 2025 11:07 am
  • ትግሉን የጎዳው የእስክንድር ነጋ አካሄድ February 3, 2025 10:29 am
  • ኤሊያስ መሠረት “ጭምብሉ ዛሬ ወለቀ”፤ ተከፋይ ነው! February 2, 2025 05:32 pm
  • የፋሲል ግንብ እድሳት እንዴት ተካሄደ? የመንጣቱ ምክንያት? January 23, 2025 03:41 pm
  • ታሪካዊዉ የፋሲል ቤተመንግሥት ለምን ነጣ? January 23, 2025 03:04 pm
  • የኢትዮጵያ አየር መንገድ በተወልደ አስተዳደር ዘመን ለተሠራ ስህተት 425ሺ ዶላር ተቀጣ December 14, 2024 01:44 am
  • በትግራይ ከሞትና ከአካላዊ ጉዳት የተረፉት ለስደት ተዳርገዋል November 27, 2024 12:09 pm
  • የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት አሠራሩን እንዲያርም ጥብቅ መመሪያ ተሰጠው November 27, 2024 11:31 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule