• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ሉዓላዊነትና መብት

December 5, 2012 03:28 am by Editor Leave a Comment

ሶርያ አሮጌ አገር ነው፤ ታሪኩ ረጅም ነው፤ ከሶርያ ጋር ሲወዳደር አሜሪካ ሕጻን ነው፤ ነገር ግን ለብዙ ወራት በሶርያ ውስጥ የሚካሄደውን ጦርነትና በቅርቡ በአሜሪካ የተደረገውን ምርጫ ስንመለከትና ስናነጻጽራቸው፣ የሶርያ ሕዝብ እርስበርሱ ሲጨራረስ አሜሪካኖች በጥቂት ቀናት ውስጥ ሐዝቡ ድምጹን ሰጥቶ ምርጫው ተጠናቅቆ በሰላም የሥልጣን ርክክብ ተደረገ፤ ዕድሜ የመብሰል ምልክት ላይሆን እንደሚችልና ፍሬ-አልባ እንደሚሆን መረዳት እንችላለን፤ ከርሞ ጥጃ እየሆኑ ዕድሜ መቁጠር፤ በሶርያ የሚካሄደው ጦርነት ግን አንድ ሰው፣ በሺር አላሳድ፣ እስቲሞት ድረስ መጋደሉና አገር መፈራረሱ ይቀጥላል፤ ዓለምም፣ የተባበሩት መንግሥታትም፣ የአረብ ማኅበርም ሁሉም ከንፈሩን እየመጠጠ የሶርያን ሕዝብ ስቃይ ያያል፤ የፍልስጥኤማውያንንም ስቃይ እንዲሁ፡፡

ለምን አንዲህ ይሆናል? ምክንያቱ ሉዓላዊነት የሚባል ነገር ነው፤ ሉዓላዊነት ምን ማለት ነው? በመሠረቱ ሉዓላዊነት ሦስት ሀሳቦችን ያዘለ ይመስለኛል፤ አንዱ ሥልጣን ነው፤ ሁለተኛው ከበላዩ ሌላ ሥልጣንን የማይቀበል ነው፤ሦስተኛው አጥር ነው፤ በኋላ አንደምናየው ሥልጣንም፣ የበላይነትም አጥር አለው፤ ለወጉ ሉዓላዊነት ማለት ራስን ችሎ ከውጭ ድጋፍ ሳይፈልጉ መቆም ነው፤ ከውጭ ምንም ዓይነት የበላይ ሥልጣንን አለመቀበል ነው፤ በአገሮች መሀከል ተደጋግሞ የሚሰማው በራሳችን የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ አትግቡብን እየተባለ መከላከያ የሚሰጠው ከሉዓላዊነት መሠረት በመነሣት ነው፤ በዚህ ዓይነት መልኩ ብዙ ጊዜ ሥራ ላይ ቢውልም በሉዓላዊነት ሀሳብ አጠቃቀም ላይ የተለያዩ አመለካከቶች አሉ፡፡

ሉዓላዊነት የሚለው ሀሳብ ከሁለት በጣም ከተለያዩ መሠረቶች የሚነሣ ነው፤ በአንድ በኩል የሕዝብ ሉዓላዊነት አለ፤ በሌላ በኩል የአገዛዝ ሉዓላዊነት አለ፤ ሕዝብ የአገሩ ባለቤት በሆነበት፣ ሕዝብ በነጻነትና በሕጋዊ ሥርዓት በተካሄደ ምርጫ ተወካዮቹን ሰይሞ ራሱ የሚቆጣጠረውን መንግሥት ባቋቋመበት አገር ሉዓላዊነት ማለት የሕዝብ የሥልጣን የበላይነት ነው፤ ሉዓላዊ፣ የአገሩ ባለቤት፣ የአገሩ የበላይ ባለሥልጣን የሆነ ሕዝብ ማለት ነው፤ በአገሩ የበላይ ባለሥልጣን የሆነ ሕዝብ መንግሥት የሚባል ድርጅት ያቋቁምና ውክልና ይሰጠዋል፡፡

በአንጻሩ በአገዛዝ ስር ያለ ሕዝብ የአገሩ ባለቤት አይደለም፤ ሥልጣንም የለውም፤ የአገሩ ባለቤት ሆኖ ሙሉ ሥልጣንን የጨበጠው አገዛዙ ነው፤ ስለዚህም ሉዓላዊነት የሕዝቡ ሳይሆን የአገዛዙ ነው፤ ነገር ግን ከሕዝቡ የተለየ አገዛዝ የአገር ባለቤት ነው ማለት ለሰሚው ግራ ስለሚሆን የይስሙላ ምርጫ እየተደረገ አገዛዞች ሁሉ ሕዝቦቻቸውን እየረገጡ ለመግዛት (አንዳንዴም በ99.7 ከመቶ እያሸነፉ!) የሚረገጡትን ሕዝቦች ፈቃድ ያገኙ እያስመሰሉ ጡሩምባቸውን ይነፋሉ፤ የሚራብና የሚጠማ፣ የታረዘና የተጎሳቆለ፣ ከዓመት ዓመት በውጭ ምጽዋት የሚኖር፣ በየዕለቱ ግፍን የሚቀበል ሕዝብ ይህ ሁኔታ እንዲቀጥል ፈቃዱን ለአገዛዝ ሰጥቷል ብሎ የሚያምን አገዛዝ ብቻ ነው፡፡

ወደሶርያ ስንመለስ ሕዝቡ የአገሩ ባለቤት አይደለም፤ ስለዚህም ሕዝቡ ሉዓላዊነት የለውም፤ ሉዓላዊነቱን በጉልበት የጨበጠው አገዛዙ ነው፡፡

ዓለም በሙሉ፣ የተባበሩት መንግሥታትም ጭምር የሶርያን አገዛዝ ሉዓላዊ አድርገው ይመለከቱታል፤ እውነተኛው የሉዓላዊነት ባለቤት የሆነው የሶርያ ሕዝብ ሲደቆስ የሐዘን ስሜት ያድርባቸው እንደሆነ እንጂ ሕጋዊ አቅዋም ሊይዙና ሕጋዊ እርምጃ ለመውሰድ ይቸገራሉ፤ አይችሉም፤ ምክንያቱም የሶርያን ሕዝብ ሀብትና ጉልበት ለጊዜው የሚያዝዝበት አገዛዙ ነው፡፡

የተባበሩት መንግሥታት ለትክክለኛው የሉዓላዊነት ባለቤት፣ ለሕዝቡ እውቅና ለምን አይሰጥም? የቂል ጥያቄ ይመስላል፤ በተባበሩት መንግሥታት ውስጥ አብዛኛዎቹን ወንበሮች የያዙት አገዛዞች ናቸው፤ ስለዚህ አገዛዞቹ ለነሱ የተመቸውን ሁኔታ በመለወጥ ራሳቸውን የሚያሰናክሉበት ምክንያት ምን አለ? ይህ አንድ ምክንያት ነው፡፡

ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የአሜሪካና የአውሮፓ ዴሞክራሲያዊ አገሮችም ቢሆኑ በሦስተኛ ዓለም አገሮች ውስጥ የእነሱን ጥቅም ለማራመድ የሚሻላቸው አገዛዝ ነው፤ በዴሞክራሲ አገር ውስጥ ብዙ ውጣ-ውረድና ልፋት ያጋጥማቸዋል፤ ነጻ ጋዜጦች የተለያዩ ሀሳቦችንንና አስተያየቶችን ያናፍሳሉ፤ ምሁራን የተለያዩ ጥናቶችን ለሕዝብ እያቀረቡ ያስተምራሉ፤ የፖሊቲካ ቡድኖች የተለያዩ አስተያየቶችን ለሕዝብ ያስጨብጣሉ፤ እንዲህ ያለው ሁኔታ ለአሜሪካና ለአውሮፓ አገሮች አይመቻቸውም፤ ለእነሱ ቀላል የሚሆንላቸውና የሚመቻቸው ከአንድ አምባ-ገነን ጋር ለብቻ ተነጋግረው የሚያጎርሱትን አጉርሰውት እነሱ በፈለጉት አቅጣጫ የሚዘውሩትን ነው፤ ስለዚህም ለሕዝብ ሉዓላዊነት ግድም የላቸው፤ በአውሮፓና በአሜሪካ የሚገኙት የሰብአዊና የዴሞክራሲ ድርጅቶች ከመንፈሳዊና ከሰብአዊ መሠረት ተነሥተው ጠንካራ ቢሆኑም የፖሊቲካውን ኃይል ሙሉ ለሙሉ መቋቋም አይችሉም፤ ይህ የሚሆነው አምባ-ገነኑ ጠግቦ ወይም በአጋጣሚ ከኃያል መንግሥት ጋር አስኪላተም ድረስ ነው፤ ያን ጊዜ ጉዳቱ ከጥቅሙ ስለሚያመዝን ፊቱን ያዞርበታል፤ በሙባረክ ላይ የደረሰው ይህ ነው፤ ሕዝቡ የጠላው አምባ-ገነን ለአሜሪካና ለአውሮፓም አይበጅም፤ የአምባ-ገነኑን ተፈላጊነት ለማስመስከር ሲሞት ሕዝቡ እንዲያለቅስ ይደረጋል፡፡

ሦስተኛም ምክንያት አለ፤ እንደሩስያና ቻይና ያሉ ኃያላን የሆኑት አገዛዞች ትንሽ ትንሽ እያጎረሱ በንግድ በኩል የሚያገኙትን ጥቅም ለማስጠበቅ የሚመሳሰሏቸውን አገዛዞች ይደግፋሉ፤ ለዚህ ነው ሩስያና ቻይና የአል በሺርን ግፍ ዓይናቸውን ጨፍነው የሚደግፉት፤ እነሱም ቢሆኑ ምጥጥ ከአደረጉት በኋላ የሚጋጥ ነገር ሲጠፋ ወዳጅነታቸውም አብሮ ይጠፋል፡፡

ዓለም-አቀፍ ሕግ እውነተኛውንና በሕዝብ ሥልጣን ላይ የቆመውን ሉዓላዊነት ከመደገፍ ይልቅ ባለጉልበቱን አገዛዝ መደገፍ ይቀናዋል፤ ለዚህ ነው የሰብአዊ መብቶችን በመርገጥ ስማቸው የገነነ አገዛዞች እንኳን በተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ውስጥ አባል ሆነው የሚመረጡት፤ አንዱ ምክንያት እንደተገለጸው የተባበሩት መንግሥታት በአብዛኛው የአገዛዞች ስብስብ ስለሆነ ወር-ተራ እየገቡ በመረዳዳታቸው ነው፤ ሌላው ምክንያት ምናልባት ከስብሰባዎቹ ይማሩ ይሆናል የሚል አጉል ተስፋ ነው፡፡

ሉዓላዊነትን የምናይበት ሌላ መንገድም አለ፤ ሕዝብ ሉዓላዊ ነው ስንል ምን ማለታችን ነው? ሕዝብ ማለት እያንዳንዱ ዜጋ በእኩልነት ቆሞ የሚታይበት ስብስብ ነው፤ሰው በዜግነቱ ሰውነቱን አያጣም፤ ሰውነቱ የተፈጥሮ ሲሆን ዜግነቱ በሕግ የተከለለ ነው፤ ዜጋ ማለት በሕግ የታጠረ ሰው ነው፤ ግለሰብ የምንለው ነጠላው ሰው ሰውም ነው ዜጋም ነው፤ ስለዚህም ለአንድ አገርም ሆነ ለአንድ ሕዝብ የሉዓላዊነቱ መሠረት እያንዳንዱ ዜጋ ነው፤ ከሉዓላዊነት ተነሥተን ወደሰውነት ደረጃ ስንገባ (ሰዎችን ሁሉ እኩል አድርገን) እያንዳንዱ ሰው ሰብአዊ መብቶች አሉት፤ እነዚህ መብቶች የሰው ልጆችን ሁሉ በአንድ ላይ ይዘው በሰውነት የታጠሩ ናቸው፤ ቀጥለን ወደአገር ደረጃ ስንወርድ ደግሞ ሰብአዊ መብቶች ዜጎችን ሁሉ በእኩልነት ይዘው በዜግነት የታጠሩ ይሆናሉ፤ በሰውነት ደረጃ በሰዎች መሀከል ልዩነት የለም፤ በዜግነት ደረጃም በዜጎች መሀከል ልዩነት የለም፡፡

ወደሶርያ ጉዳይ ስንመለስ ተጽእኖ ለማድረግ የሚችለው የዓለም-አቀፍ ማኅበረሰብ ሶርያን የሚመለከተው በሰውነት ደረጃም ሆነ በዜግነት ደረጃ አይደለም፤በጥቅም መለኪያ ነው፤ ለዚህ ነው የሶርያ ሕዝብም ሆነ የፍልስጥኤማውያን ሕይወት ዋጋ-ቢስ የሆነው፤ ለዚህ ነው በአገሩ ውስጥ የባለቤትነት መብት የሌለው ግለሰብ በሕዝብነት ወይም በዜግነት ደረጃ ውስጥ ሲገባ ገለባ የሚሆነው፤ ለገለባ ማንም ግድ የለው፡፡

ሰብአዊ መብቶች ተጣሱ ወይም ተረገጡ የሚባለው በግለሰብ ደረጃ ያለውን አጥር፣ በዜግነት ደረጃ ያለውን አጥር፣ በሰውነት ደረጃ ያለውን አጥር የሚያፈርስ ለሕግ ግድ የሌለው ጉልበተኛ ሲነሣ ነው፤ ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ!

Mesfin Woldemariam Blog

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Opinions Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ባልደራስ የአገርን ደኅንነት አደጋ ላይ በመጣል ሊጠየቅ ይገባዋል ተባለ July 1, 2022 09:23 am
  • “ሚካኤል ችግኝ ነው። … ችግኝ ይተክላል” ቴዲ አፍሮ June 29, 2022 03:30 am
  • “የእኔን ልጆችና የልጅ ልጆች (22ቱንም) የቀበርኩት እኔ ነኝ” አቶ መሀመድ የሱፍ ከምዕራብ ወለጋ June 28, 2022 01:07 pm
  • የገዳ ሥርዓት እና የኦሮሞ ገዢ መደብ June 20, 2022 11:34 pm
  • “የወልቃይትን ጉዳይ ለድርድር የማናቀርበው ቀይ መስመራችን ነው” ርዕሰ መስተዳድር ይልቃል June 12, 2022 07:09 pm
  • የሰሜን ምዕራብ ዕዝና የአማራ ልዩ ኃይል ተከዜ ክፍለ ጦር ዕውቅናና ሽልማት ተሰጣቸው June 12, 2022 06:21 pm
  • ሀገር በቀል ባህላዊ የግጭት አፈታቶችን በተገቢው በመጠቀም ዘላቂ እርቅና ሰላምን ማምጣት ይቻላል June 12, 2022 05:40 pm
  • የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በገረጂና በቀበና ያስገነባቸውን የመኖሪያ አፓርትመንቶች አስመረቀ June 12, 2022 05:35 pm
  • በኦነግ ሸኔ ፈርሶ የነበረውና ወታደራዊ ጠቀሜታ ያለው ድልድይ ተጠግኖ አገልግሎት መስጠት ጀመረ June 10, 2022 09:13 am
  • ጃዋር በዳውድ ኢብሣ ቀይ መስመር ተሰመረለት June 8, 2022 12:59 pm
  • ወልቃይት: ቢመረንም ለመዋጥና ራሳችንን ለመመልከት እንሞክር June 8, 2022 11:53 am
  • እብድ ይሻለዋል እንጂ አይድንም፤ ሐጂ ጃዋር አሁን ለምን ብቅ አለ? June 8, 2022 05:59 am
  • ሕዝብ ድምፅ የነፈጋቸው “ፓርቲዎች” የሽግግር መንግሥት ይቋቋም አሉ June 7, 2022 01:11 am
  • “አድጌ እንደናንተ መሆን እፈልጋለሁ” June 5, 2022 06:58 pm
  • በሳምንት ለ100 ያህል ሕሙማን አገልግሎት የሚሰጥ የኩላሊት ዕጥበት ማዕከል ሥራ ጀመረ May 30, 2022 02:20 am
  • የጥቁር አንበሳ ዕጩ መኮንኖች (ካዴቶች) ተመረቁ May 29, 2022 04:01 pm
  • “ኢትዮጵያን መንካት አይቻልም!!” በሚል ቁጭት ነው እየሠራን ያለነው May 29, 2022 01:04 pm
  • “ከሞፈርና ቀንበር ወደ ትራክተር” በሚል መርህ ለአማራ ገበሬዎች የግብርና ሜካናይዜሽን ተሰጠ May 29, 2022 02:02 am
  • ኢትዮ 360 “የወያኔ፣ የጁንታ ሚዲያ ነው” – ባለከዘራው ጄኔራል May 27, 2022 02:51 am
  • “እኛ የምናውቀው ነገር የለም፤ የሚያጣሉን ፖለቲከኞች ናቸው” የአማራ ወዳጃቸውን አደራ ቤት የመለሱ የቅማንት ተወላጅ May 27, 2022 01:40 am
  • ትግራይን አገር እናደርጋለን፤ “በውይይት እና በጦርነት” ሁሉንም ጉዳይ እንቋጫለን – የወንበዴው መሪ ደብረጽዮን May 26, 2022 09:18 am
  • “ሁለቱ የምዕራብ ዕዝ ተዋጊ ዶክተሮች” May 26, 2022 08:19 am
  • ወደ ትህነግ ሊተላለፍ የነበረ አምስት ሚሊዮን ብር ከ20 ተጠርጣሪዎች ጋር ተያዘ May 25, 2022 01:57 am
  • የጦርነቱ ስትራቴጂያዊ እውነታዎች May 19, 2022 09:37 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2022 · Goolgule