
ለሁለት ቀናት በኢትዮጵያ ጉብኝት ያደረጉት የአሜሪካው ፕሬዚዳንትና አጃቢዎቻቸው ለሁለት ቀን አዳር ለሆቴል ያወጡት ወጪ ከ27 ሚሊዮን ብር በላይ እንደነበር ተገለጸ፡፡
ፕሬዚዳንቱ በኢትዮጵያ የሚያደርጉት ጉብኝት በአንድ ሆቴል ብቻ እንደሚደረግ አስቀድሞ የተነገረ ቢሆንም የአስተዳደራቸው ከፍተኛ ባለሥልጣናት፣ አጃቢዎቻቸውና ሌሎች የደኅንነት ሠራተኞች በአራት ሆቴሎች ውስጥ አርፈው እንደነበር Weekly Standard የክፍያ ሰነዶችን በማስደገፍ ይፋ አድርጓል፡፡ አስቀድሞ የተለቀቀው መረጃ እንደሚያመለክተው የኦባማ ቡድን በሒልተን ሆቴል ቆይታ እንደሚያደርግና ወጪውም ብር 8,491,127.81 ወይም በግምት ዶላር $ 412,390.86 መሆኑን የሚያሳይ የኮንትራት ውል መፈረሙን ነበር፡፡
ከአሜሪካ መንግሥት የተጠያቂነት ቢሮ የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው የፕሬዚዳንቱ ቡድን ለሁለት ቀናት ያረፉት በአንድ ሆቴል ሳይሆን በአራት የተለያዩ ሆቴሎች ነበር፡፡ በዚህም መሠረት ከላይ ለተጠቀሰው የሒልተን ሆቴል ወጪ 1,280 የመኝታ ክፍል ምሽቶች ተከራይተዋል፡፡ 22 ማዞሪያ ከዋሪት ህንጻ ፊትለፊት በሚገኘው ካፒታል ሆቴልና ስፓ (Capital Hotel and Spa) ለ1,000 ክፍል ምሽቶች ብር 3,673,950 ወይም በዶላር $178,433.71፤ ካዛንቺስ በሚገኘው ኢሊሊ (Elilly) ሆቴል ለ120 የመኝታ ክፍሎች ብር 5,100,480 ወይም በዶላር $246,877.06፤ እንዲሁም በሸራተን አዲስ ለ1,236 የመኝታ ክፍል ምሽቶች ብር 10,050,826.13 ወይም በዶላር ግምት $488,141.14 ወጪ መደረጉ ተዘግቧል፡፡ ይህም ለአራቱ ሆቴሎች በድምሩ በዶላር ግምት 1,325,841 ወይም በብር 27,771,383.94 መሆኑ ጨምሮ ተገልጾዋል፡፡ ክፍያው አዲስ አበባ በሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ አስፈጻሚነት በውጭ ጉዳይ ሚ/ር መ/ቤት (ስቴት ዲፓርትመንት) መከናወኑ መረጃው በግልጽ ያስረዳል፡፡
ከፕሬዚዳንቱ ቡድን ጋር አብረው የተጓዙ በፍሎሪዳ ጠቅላይግዛት የሚገኙ ነጋዴ ለWeekly Standard እንዳሉት “(በአዲስ አበባ) አብሬአቸው ስሰራ የነበሩ በከተማዋ የሚገኙ አሜሪካውያን እንደነገሩኝ ኦባማ አዲስ አበባ በነበሩበት ጊዜ የአሜሪካ መንግሥት ሸራተንን እንዳለ ገዝቶት ነበር”፡፡ ኦባማ በሸራተን ለመቆየታቸው ደግሞ አብሯቸው የተጓዘው ፎቶ አንሺ Pete Souza የምስል ምስክርነቱን ሰጥቷል፡፡
ይህ የሆቴል ወጪ ብቻ ሲሆን ከዚህ ሌላ ለእጅ ስልክ ቀፎዎች ግዢ $7,540 ዶላር ወጪ መደረጉን አብሮ የተገኘው መረጃ ያስረዳል፡፡ ስልኮቹ የተገዙት በአሜሪካ ኤምባሲ በኩል ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኝ ኩባንያ ከውጪ ድርጅት ጋር ባደረገው ኮንትራት መሆኑን መረጃው ያሳያል፡፡ ስልኮቹን የሸጠው ኩባንያ ማንነት ተጠይቆ ቤተመንግሥቱ (ኋይት ሃውስ) መረጃ ከመስጠት ተቆጥቧል፡፡ ስልኮቹን ማን እንደተጠቀመባቸው ከጉብኝቱ በኋላ ደግሞ የት እንደደረሱ አይታወቅም፡፡
ኦባማ ኢትዮጵያን በጎበኙ ወቅት የወጣው ይህ ወጪ የሆቴል ኪራይና የስልክ ብቻ ሲሆን ሌላ እጅግ በርካታ የሆነ ከጉብኝቱ ጋር የተደረገ የደኅንነት፣ የጉዞ፣ የግንኙነት፣ የሚሊታሪ፣ ወዘተ ወጪዎችን የሚጠቀልል አይደለም፡፡
በሆቴሉ ወጪ ዙሪያ ለጎልጉል አስተያየታቸውን የሰጡ እንዳሉት “ካንበት ሁኔታ አኳያ ስተረጉመው ኦባማ ልማታዊ ጎብኚ ናቸው፤ ሥልጣናቸውን ከመልቀቃቸው አንድ ሁለቴ ጉብኝታቸውን ቢደግሙ የባንክ ዕዳችንን ከፍለን ጨርሰን ትርፋማ እንሆን ነበር፤ ሕገመንግሥታቸውን ቀይረው ለሦስተኛ ጊዜ ለፕሬዚዳንትነት ቢወዳደሩ መቶ በመቶ እደግፋቸዋለሁ፤ መቶ በመቶ እንደሚያሸንፉም እርግጠኛ ነኝ” ብለዋል፡፡ (የገጽ ፎቶ: Pete Souza)
ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው፡፡ ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (https://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን፡፡
So what? America is ever since the 1980s lier, destructive and arrogant?
የዚህ አይነት ሀገራችንን የሚመለከት ጽሁፍ እንዳለ ክውጭ ጋዜጣ ገልብጠን መጻፍ ያለብን አይመስለኝም። እንኳንስ 1000 ክፍሎች 300 ክፍሎች ያሉት ሆቴል እንኳ በአዲስ አባ የልም ። ይታረም።
ketma jifar
ዜናውን ከውጭ ጋዜጣ እንዳገኘነው ብንጠቅስም መረጃው ግን የተገኘው በፈጠራ ወይም በግምት አይደለም:: ለነገሩ እንዲህ ያለው ዜና የሚገኘው ህወሃት ከሚመራት ኢትዮጵያ ሊሆን እንደማይችል ግልጽ በመሆኑ ለርስዎም የተሰወረ አይደለም::
በዜናው ላይ እንዳሰፈርነው የአሜሪካ መንግሥት ለሆቴሎቹ የከፈለውን ወጪ ያደረገበት መረጃ በግልጽ ተቀምጦዋል:: ሆቴሎቹ ያንን ያህል ክፍል ይኑራቸው አይኑራቸው ማጣራቱ ሳይሆን የተከፈለው ወጪ መጠን የዜናው ቀዳሚ ዓላማ በመሆኑ የክፍሎቹ ብዛት ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ አልነበረም:: ከዚህ ሌላ ክፍያውን የፈጸመው ያሜሪካ መንግሥት ይፋ ባደረገው መሠረት የተከራየውንና የከፈለውን በገልጽ አስቀምጦዋል:: ዋናው ዜና ለሁለት ቀናት አዳር ይህንን ያህል ወጪ ለሆቴል መደረጉ ነው::
በእኛ በኩል የተፈጸመው ግድፈት በእንግሊዝኛው በሦስት አገላለጽ ማለትም – sleeping rooms, room nights and sleeping room nights – የሚሉትን በአንድ የአማርኛ አገላለጽ መጻፋችን ነው – ለዚህም እርምት ወስደናል::
ከዚህ በተረፈ የአሜሪካ መንግሥት ለሆቴሎቹ ወጪ ክፍያ ማድረጉ ይበልጥ ለመረዳት በየስሞቻቸው ላይ ከዚህ በታች ያሉትን ማጣቀሻዎች በመመልከት ማስረጃ እንዲያገኙ አስፍረናቸዋል::
ሸራተን አዲስ
ሒልተን
ካፒታል
ኢሊሊ
ከምስጋና ጋር
አርታኢ/Editor
ጎልጉል: የድረገጽ ጋዜጣ/Golgul: the Internet Newspaper
http://www.goolgule.com
editor@goolgule.com