• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ኢህአዴግ – ሌባ ወይስ አገር አስተዳዳሪ?

March 5, 2014 08:01 am by Editor Leave a Comment

ከላይ የጠየቅነው ጥያቄ ዛሬ የተነሳ አዲስ ነገር አይደለም። ኢህአዴግ መሰረቱን ዝርፊያ ላይ ያደረገ አገር አስተዳዳሪ መሆኑ ግብሩ ራሱ ምስክር ነውና “ሌባ አገር አስተዳዳሪ” ስለመሆኑ ማስተባበያ ሊያቀርብም አይቻለውም፤ አያስፈልገውም። ሌብነቱ አገርንና ህዝብን ወደ ገደል እየሰደደ መሆኑ ግን ሁሌም የሚያስጨንቅ ነውና ዛሬ እንደ አዲስ አነሳነው እንጂ!!

ኢህአዴግ ግዙፍ፣ ሃብቱ በዶላር ካልሆነ በብር የማይቆጠር፣ በህገወጥ ንግድ ሰላማዊ ነጋዴዎችን የሚውጥ፣ ለብቻው መግቢያና መውጪያ የተዘጋጀለት፣ የተለየ ጨረታና የነጻ ቀረጥ እድል የሚበጅለት፣ በየትኛውም ተቋም እንደፈለገ መጋለብ የሚችል ልጓም አልባ የሆነ፣ በፈለገው ቦታና ማህበረሰብ ጥቅም ላይ እንዳሻው ከበሮ እየደለቀ የሚጨፍር፣ ጡሩምባ ይዞ የሚያንጠራባ፣ የፈለገውን ማስወገድ፣ ማሳገድ፣ ማስከፈት፣ ማዘጋት የሚችል፣ ድንበርና ኬላ የማይዘው የንግድ ተቋም አለው። እወክላቸዋለሁ በሚላቸው የአንድ ክልል ሕዝብ ስም ባቋቋመው ሻርክ ኦዲት በማያውቀው የ”ንግድ” ተቋም አማካይነት አገሪቷን እየዘረፈና እየዋጠ ነው።

አገሪቱ አምጣ የምታገኘውን የውጪ ምንዛሬ በበላይነት ሲፈልግ ከራሱ ባንክ፣ ሲያሻው የራሱ ሰዎች በሚያዙበት የህዝብ ባንኮች በተራ ትዕዛዝ ያግበሰብሳል። በፋይናንስ ዘርፉ ውስጥ እጅና እግሩን ነክሮ እንዳሻው ያንቦጫርቃል። የሚቀናቀኑ ብቅ ሲሉ እየበለተ ይሰቅላቸዋል። ሲያሻው ፋይል አስከፍቶ በ”አጎብዳጅ ባንዳ” ዳኞች ያስፈርድባቸዋል። “ጸረ ልማት” ብሎ የፍየል ወጠጤ ያዘፍንባቸዋል።

እንቶኔን ያየ … በሚል አገር ወዳዶች ሸሽተው አለቁ። ምሁሩ አገሩን ከዳ። ነጋዴው ኮበለለ። ወጣቱ በኑሮ ጠኔ መጨረሻው በማይታወቅ ስደት የባህር ላይ ሞትን መረጠ። የቻሉ አረብ ምድር ገብተው በግፍ አለንጋ ተጠበሱ። ኢኮኖሚያዊ ቀውሱ የበረታባቸው ራሳቸውን ማጥፋት ጀመሩ። ይህ ሁሉ የማያስደነግጣቸው ህወሃትና ጭፍሮቹ በጥጋብ ያገሳሉ።

ተቀናቃኞቹን በሰበብ ለማላመጥ የተቋቋመው የፌደራል የስነ ምግባርና የጸረ ሙስና ኮሚሽን በቅርቡ በሰጠው ማረጋገጫ ያለ ህጋዊ ቀረጥ ከሚነግዱ ድርጅቶች መካከል ይኸው የህወሃት ድርጅት ግንባር ቀደም ነው። ነገር ግን ጠያቂ የለውም። ለምን ቢባል ባለቤቱ ራሱ አገር መሪ ነውና። ሌባ አገር አስተዳዳሪ ነውና!!

“አስገራሚውና አነጋጋሪው ጉዳይ ህወሃት መቼ ነው ዘርፎ የሚጠግበው?” የሚለው ነው። አንድ ነጻ አውጪ ድርጅት አገር መምራቱ በራሱ ይገርማል፤ ምን አልባትም በዓለም ላይ በነጻ አውጪ የምትገዛ ብቸኛ አገር ኢትዮጵያ ትሆናለች ። በዚህም ላይ ይህ “ነጻ አውጪ” ከፍተኛ አመራሮቹ እንደሚሉት ከበረሃ ጀምሮ ዘርፎ ዘርፎ አለመጥገቡ ያስደንቃል። ከሁሉም በላይ የሚያስገርመው ግን በየቀኑ የጠላቶቹን ቁጥር በሺህዎች እያባዘ ነገ ምን ሊገጥመው እንደሚችል ያለመገመቱ ነው።

እዚህ ላይ አጠንክረን የምንለው ይኖረናል። ህወሃት አንዱን ከሌላው በማጋጨት መሰረት ላይ በተከለው ፖለቲካ የትግራይ ህዝብ የሌላውን ብሔረሰብ ህዝብ ሙሉ በሙሉ እንዲጠረጥርና ራሱን እንዲከላከል እየሰራ መሆኑን እናውቃለን። የማያውቁና መረጃ የሌላቸው ከግምት በላይ ይረዱታል። ይህ ሰይጣናዊ አካሄድ ዋጋው አስቀድመን እንዳልነው “ደም” ነውና ከወዲሁ ማርገቢያ እንዲበጅለት እናሳስባለን።

በቁጥር እየከፋፈሉ በምስጢር ከየአይነቱ በማስታጠቅ የትግራይ ህዝብን ከሌላው ህብረተሰብ ጋር ለማጋደል በምርጫ 97 ወቅት ሟቹ አቶ መለስ የሰጡትን ትዕዛዝ አጠንክሮ መያዝ አሁንም መዘዙ የከፋ ነውና ህዋሃት ከዚህ ተግባሩ እንዲታቀብ እንመክራለን። በወቅቱ “ራስህን ተከላከል፣ ሊያጠፉህ ነው” በሚል በመታጠቅ በየቀበሌው ለመተላለቅ መመሪያ የተጠበቀበት ደረጃ ተደርሶ እንደነበር ለምናውቅ ድርጊቱን ስናስበው ይቀፈናል። ያመናል። ያስበረግገናል። ተከስቶ ቢሆን ኖሮ ጠባሳው ምን ያህል በከፋ ነበር?

የትግራይ ህዝብ እንደ ህዝብ እንደ ማንኛውም የተረገጡ ዜጎች ሁሉ የስርዓት ለውጥ ያስፈልገዋልና ሌላው ህብረተሰብ ከጭፍን ጥላቻ ራሱን እንዲያርቅ እንመክራለን። የትግራይ ልሂቃንም በገለልተኛ ሚዛን በራሳቸው ላይ እንዲሆን የማይፈቅዱት በሌሎች ላይ እየተደረገ መሆኑንን በመቃወም በህዝብ መካከል የተረጨውን መርዝ በማምከን ተግባር ላይ ሊሰማሩ እንደሚገባ ለመጠቆም እንወዳለን። ዙሪያችንን የከበቡን ጠላቶች ይበቁናልና!!

ኢህአዴግ እንደ ገዢ ያለው አቅም ተቦርቡሯል። ሟርት ነው ካልተባለ የኑሮ ብሶት፣ ሌብነትና በሌላው ህዝብ ላይ የሚፈጽመው የግፍ ክምር ሊንደው ተቃርቧል። የሚመካበት የጦር ሃይልም ቢሆን ወገን አለውና አንድ ቦታ ከተፈረከሰ አደጋው የአገር ነው። በቡድን አደራጅቶ መሳሪያ በማደል በጎጥ ወኔ የህዝብን ቁጣና ምሬት መቋቋም የሚታሰብ አይደለምና ህወሃት በመፈክር አታሎ በጨረሳቸው ታጋዮች ደም ላይ የሚደንሰውን ከልክ ያለፈ የጥጋብ ጭፈራ ይግታው። በነጻ አውጪ ስም አገር እየመሩ ዝርፊያ ተራ የማፊያ ተግባር እንጂ አገር እምራለሁ ከሚል ወገን የሚጠበቅ አይደለምና ያደባባይ ዝርፊያ ይቁም!! ኢህአዴግ ሌባ ወይስ አገር አስተዳዳሪ በማለት የሚጠይቁ ሁሉ እውነት አላቸውና ልብ ያለው ልብ ይበል።

በግብር የምናየው ኢህአዴግ ከተዘፈቀበት ችግር ራሱን ከማጽዳት፣ ህዝብ የሚበጀውን እንዲመርጥ መንገድ ከማመቻቸትና አገሪቱን ወደ መልካም ጎዳና ከማሸጋገር ይልቅ፣ ህዝብን በጅምላ “ለሃጫም” እያለ መስደብ የሚያስደስተው ነው። ህዝብን “ጠባብ፣ አሸባሪ፣ ጸረ ልማት፣ …” በማለት መፈረጅ የድል ያህል የሚያስፈነድቀው ነው። ራሱ ስራ ፈት ያደረገውን ትውልድ “ቦዘኔ” ሲልና ሲሳደብ የስኬት ገድል ያስመዘገበ ያህል ይመስለዋል። ከሁሉም በላይ የህወሃት የእጅ ስራ ውጤት የሆኑ አሻንጉሊት ካድሬዎች እንደ ጌቶቻቸው “ለሃጫም” እያሉ ህዝብን ሲሰድቡ ሽልማት ለመስጠት ይሽቀዳደማል። ህዝብ ሲያኮርፍና ሲበሳጭ ይደሰታል። አገሪቱን ባህር አልባ አድርጎ ስለቀረቀረባት ኩራት ደረቱን ይነፋል። በማያገባው ጦርነት ምስኪን ወገኖችን ማሽጨፍጨፉ ልዩ ገድል ሆኖ ይታየዋል። ድንግል መሬት በሳንቲም ሲቸበቸበ ልማት ነው ይላል፡፡ ነዋሪዎችን ለትውልድ ከኖሩበት እያፈናቀለ መሬታቸውን ለውጪ ባለሃብቶች እየሰጠ “እስካሁን ያልሸጥነው መሬት ነው የሚያሳስበን” በማለት በሰው ደም ይቀልዳል፡፡ በዚህ ሁሉ ትዕቢቱ ላይ ንጹሃንን እያሰረ ማሰቃየቱ፣ መግረፉና መግደሉ፣ አሁን አሁን ይፋ የሆነበት የመርዝ ጣጣ ጀብድ ሆኖበታል። በልክ በልኩ የሰራቸውን አሻንጉሊት ተላላኪዎቹ ሰብስቦ በሚሰራው ድራማ መደነሱና ውሸታም አገር አስተዳዳሪ መሆኑ የኩራቱ ሁሉ ኩራቱ ነው። በዚህ ሁሉ ሲደመር ዜሮ በሚሆን ትምክህት ውስጥ ሆኖ አገር መምራቱ በእጅጉ ያሳስበናል፣ ያስጨንቀናል፣ ወደፊት የሚመጣውን ስናስበው እንደ ዜጋ ያስበረግገናል። ለዚህ ነው “ኢህአዴግ ሌባ – ወይስ አገር መሪ” ስንል የጠየቅነው። መልሱን የሚሰጥ ሁሉ እንዳመላለሱ ትግሉን ሊያካሂድ ይገባዋል እንላለን፡፡


ይህ ርዕሰ አንቀጽ የ“ጎልጉል: የድረገጽ ጋዜጣ®” አቋም ነው፡፡

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Editorial Tagged With: Left Column

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm
  • የተመሠረተው የፋኖ አደረጃጀት ዋነኛ ዓላማው ድርድር መሆኑ ተነገረ May 14, 2025 11:07 pm
  • ከፍተኛ የፋኖ አመራሮች መገደላቸው ተነገረ May 6, 2025 10:40 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule