• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

በሰላማዊ ሠልፉ ሰማያዊ ፓርቲና መንግሥት እየተወዛገቡ ነው

June 6, 2013 08:09 am by Editor Leave a Comment

ሰማያዊ ፓርቲ ከአንድ ወር በፊት በጠራውና ባለፈው እሑድ የተደረገውን ሰላማዊ ሠልፍ መንግሥት ሲያወግዝ፣ ሰላማዊ ፓርቲ ደግሞ የመንግሥት ውግዘት በተቃውሞ የተነሳውን ሕዝብ ከማሸማቀቅ ባለፈ የሕግ ድጋፍ እንደሌለው እየገለጸ ነው፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ ሚያዝያ 29 ቀን 2005 ዓ.ም. ባስተላለፈው የሰላማዊ ሠልፍ ጥሪ፣ ግንቦት 25 ቀን 2005 ዓ.ም. በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጐች ወጥተው ተሰተውለዋል፡፡ አራት ኪሎ ቀበና አካባቢ ከሚገኘው የሰማያዊ ፓርቲ ጽሕፈት ቤት መነሻውን ያደረገው ሰላማዊ ሠልፉ በአራት ኪሎ፣ በፒያሳና በቸርችል ጐዳና አድርጐ ኢትዮ ኩባ የወዳጅነት መናፈሻ ደርሶ፣ እስከ ቀኑ ስምንት ሰዓት ድረስ የተለያዩ መፈክሮችንና ተቃውሞዎችን በመንግሥት፣ በመንግሥት መገናኛ ብዙኅንና በአንዳንድ የግል መገናኛ ብዙኅን ላይ አሰምተዋል፡፡

ሠልፈኞቹ ለመንግሥት ካቀረቧቸው ጥያቄዎችና መፈክሮች መካከል፣ ‹‹ዜጐችን ማፈናቀል የዘር ማጥፋት ወንጀል ነው፡፡ የህሊናና የፖለቲካ እስረኞች በአስቸኳይ ይፈቱ፣ የመደራጀት መብታችን ይረጋገጥ፣ በኑሮ ውድነት የጐበጠው ትከሻችን እረፍት ያስፈልገዋል፣ ሕገ መንግሥትን የሚፃረሩ አፋኝ አዋጆች ይሰረዙ፣ የመንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ መግባትን አጥብቀን እንቃወማለን፣ የሙስሊም መፍትሔ አፈላላጊዎች በአስቸኳይ ይፈቱ፣ ለፍትሕና ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት መስፈን የሚታገሉ ጋዜጠኞች ይፈቱና አትነሳም ወይ አትነሳም ወይ . . . ወኔ የሌለው የአገረ ሸክም ነው፣ ውሸት ሰለቸን . . . ›› የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

በሰላማዊ ሠልፉ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት ዓለም አቀፍ የሕግ ባለሙያው ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለ ማርያም እንደተናገሩት፣ አንድ ሕዝብ የሚገባውን መንግሥት ሊያገኝ ይገባል (A people get a government deserved)፣ ሥርዓቱን በትግል መለወጥ ካልተቻለ በትግል የምትፈልገውን ታገኛለህ ብለው፣ በ1997 ዓ.ም. ለዲሞክራሲ ሥርዓት ብቁ መሆኑን ያረጋገጠ ሕዝብ ኢሕአዴግ የሚመራው ሥርዓት እንደማይገባው ገልጸዋል፡፡

ለኢሕአዴግ ሥርዓት መለወጥ ወጣቱ ትልቅ ሚና እንዳለው፣ ‹‹መሬት ላራሹ›› ብሎ በመነሳት ኅብረተሰቡን ቀፍድዶ ይዞት ከነበው የፊውዳል ሥርዓት በማላቀቅ ትግል ውስጥ፣ ግንባር ቀደም እንደነበረ የገለጹት ዶ/ር ያዕቆብ፣ ደሙን ገብሮ ከጨፍጫፊው ደርግ ያላቀቀን ወጣት ዛሬ ነጥፏል የሚባለው አባባል፣ ከሰው ተፈጥሮና ከእውነት ውጭ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

‹‹ሽብርተኞች እንደምን አደራችሁ›› በሚል ምፀታዊ ሰላምታ ንግግራቸውን በዕለቱ ያሰሙት የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ደግሞ፣ ‹‹ይኼ የወጣቶች ሠልፍ ምልክትና መንገድ ነው፤›› ካሉ በኋላ፣ የእስልምና መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴዎች፣ ጋዜጠኞችና የፖለቲካ እስረኞች እስካልተፈቱ፣ ተፈናቃዮች ካሳ ተከፍሏቸው ወደ ቀያቸው እስካልተመለሱ፣ ሙስና እስካልጠፋ፣ የኑሮ ውድነትና ሥራ አጥነት ተገቢው የፖሊሲ ማስተካከያ እስካልተደረገባቸው ድረስ ሰማያዊ ፓርቲ ትግሉን በአስተዋይነት እንደሚቀጥል አስታውቀዋል፡፡ ለዚህም መስዋዕትነት ሊከፈል እንደሚችል በማከል ገዥው ፓርቲ የተባሉትን እንዲያስተካክል የሦስት ወራት ጊዜያት መስጠታቸውንም ገልጸዋል፡፡ ‹‹አሁን ያለው ሥርዓት ታሪካችንን፣ ክብራችንንና የዕውቀት ችሎታችንን አይመጥንም፤›› ካሉ በኋላ፣ ሕዝብ የመጠየቅ መብት እንዳለውና መንግሥት መፍትሔ የመስጠት ግዴታ እንዳለበትም አክለዋል፡፡

ሰላማዊ ሠልፉ በሰላም ተጀምሮ በሰላም በመጠናቀቁ መንግሥትም ዕውቅና የሰጠው ቢሆንም፣ በተለይ መንግሥት የሠልፉን ዓላማና እንቅስቃሴ በሚመለከት ‹‹ሕገ መንግሥቱን የጣሰ›› ብሎታል፡፡

የኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የጠቅላይ ሚኒስትሩ የሕዝብ አደረጃጀትና ተሳትፎ አማካሪ ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ለመገናኛ ብዙኅን በሰጡት ማብራሪያ፣ በሃይማኖት ሽፋን ሲካሄድ የነበረው የፀረ ሕገ መንግሥት እንቅስቃሴ ቀድሞውንም ስውር አጀንዳ የነበረው መሆኑን፣ ሰማያዊ ፓርቲ በጠራው ሰላማዊ ሠልፍ ላይ መገለጡን ተናግረዋል፡፡

ፓርቲው ሠልፉን ላልተገባ ተግባር ማዋሉን የተናገሩት አቶ ሬድዋን፣ የፖለቲካ አቋምን በሃይማኖት ሽፋን አድርገውና ቀላቅለው እንዲንቀሳቀሱ ማድረጉና በፍርድ ቤት የተያዘን ጉዳይ በሰላማዊ ሠልፍና በሁካታ ለማቆም የደረጉት እንቅስቃሴ፣ ሕገ መንግሥቱን የጣሰና ተገቢ አለመሆኑን አብራርተዋል፡፡

አገር እመራለሁ የሚል ፓርቲ ከአጀንዳዎቹ አንዱ የሚሆነው የሕግ የበላይነትን ማረጋገጥ መሆኑን የገለጹት አቶ ሬድዋን፣ የሕግ የበላይነት የሚረጋገጠው ደግሞ የፍርድ ቤትን ነፃነት በማክበር መሆን እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡

ሰላማዊ ሠልፍ የሚወጣለትና ፍትሕ ሊጠየቅለት የሚችል ሰው በፍርድ እንዳይጠየቅ ሲደረግ፣ ሠልፍ የማይወጣለትና ፍትሕ ሊጠየቅለት የማይችል ሰው ዝም ሊባል የሚችልበት አካሄድ፣ ለአገር ሰላም ሊያሰፍን እንደማይችልና የዜጐችንም መብት ሊያረጋግጥ እንደማይችል አስረድተዋል፡፡ ሐሳብን በጽሑፍም ሆነ በሰላማዊ ሠልፍ መግለጽ ሕገ መንግሥታዊ መብት በኢትዮጵያ የተከበረ መሆኑን፣ ነገር ግን በፖለቲካ ሽፋንነት የአክራሪነት አጀንዳን ማራመድ የሕገ መንግሥቱን ድንጋጌዎች የሚጥስ መሆኑን አክለዋል፡፡

መንግሥት በሰላማዊ ሠልፉ ተደናግጦ ነገሮችን ከማቃለልና ሕዝቡን በፖለቲካ ንግግር ከማሸማቀቅ በስተቀር፣ የሕግ ድጋፍ እንደሌለው የተናገሩት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ሲሆኑ፣ የመንግሥት ንግግር ፖለቲካዊ መሆኑን የሚያሳየው የተሰላፊዎቹን ቁጥር በሁለትና በአንድ ሺሕ አሳንሶ ሲናገር መታየቱ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲም ሆነ ሕዝቡ ሕገ መንግሥቱን እንዳልጣሱ የገለጹት ኢንጂነር ይልቃል፣ ‹‹ጀሃዳዊ ሀረካት፣ አኬልዳማ›› በማለትና የተለያዩ ሕገወጥ ሥራዎችን በሕግ በተያዙ ጉዳዮች ላይ በመሥራት በፍርድ ቤቶች ላይ ተፅዕኖ የፈጠረው ራሱ መንግሥት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ሰላማዊ ሠልፉ የመንግሥትን በሃይማኖት ጣልቃ መግባትን ለመከላከል፣ ዜጐች አመለካከታቸውን የማራመድ፣ የፈለጉትን ሃይማኖት የመከተልና የማምለክ ሕገ መንግሥታዊ መብታቸው እንዲከበር ለማድረግ መሆኑን የገለጹት ኢንጂነሩ፣ የእምነት ነፃነት የመጀመሪያውና የጋራ ነፃነት በመሆኑ ያንን የመጠየቅ መብት እንዳላቸው አውስተዋል፡፡

መንግሥት ይኼንን ክፍል ለምን ነካችሁ ማለቱ እንዳስገረማቸው አስረድተው፣ ፓርቲው መጠየቅ ያለበት ኅብረተሰቡ ያነሳውን ጥያቄ ባያነሳ እንደነበርም አክለዋል፡፡ ኅብረተሰቡ በመንግሥት ትልቅ በደል እንደደረሰበት ሲናገር፣ እንደ ሰማያዊ ፓርቲ መንግሥትም ማንሳት እንዳለበትና ግዴታው መሆኑን ፕሬዚዳንቱ ገልጸው፣ ፓርቲያቸው ማንኛውንም እምነት የማክበርና ፓርቲያቸውም ዜጎች የእምነት ሥርዓታቸውን እንዲያካሂዱ እንደሚፈቅድ አስረድተዋል፡፡

ሕዝብና መንግሥትን ከሁለት ዓመታት በላይ አጣልቶ የቆየንና እስካሁንም ለውጥ ያልታየበትን ንፁኃንን ሽብርተኛ ማድረግ የመንግሥትን ተዓማኒነት ከማሳጣት በስተቀር ሌላ የሚያመጣው ነገር እንደሌለ መንግሥት ሊገነዘብ እንደሚገባ አስረድተዋል፡፡

አገርን እንደሚመራ ፓርቲ ኢሕአዴግ መሥራት ያለበት ሕዝብንና መንግሥትን የሚያቀራርብ ሥራ እንጂ፣ ማላገጥና ንግግር ማሳመር የሚያዋጣው እንዳልሆነ ኢንጂነር ይልቃል አስረድተዋል፡፡

‹‹ኢትዮጵያ ትልቅ ችግር ላይ ነች›› የሚሉት ፕሬዚዳንቱ የኑሮ ውድነቱ ሰማይ መድረሱን፣ ሙስና ተቋማዊ መሆኑን፣ የታሳሪዎች ብዛትና ያላግባብ የሚፈናቀሉ ዜጐች ከምንም በላይ ማሳያ መሆናቸውንና ዓለም ሁሉ ያወገዘው፣ ኢትዮጵያውያን በነፃነት የመነጋገር ሕገ መንግሥታዊ መብታቸውን ገፎታል ያሉት የፀረ ሽብርተኝነት ሕጉም ሌላው ችግር መሆኑን አክለዋል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲም ለመንግሥት የሚያቀርበው ጥያቄ እነዚህን ችግሮች ተመካክረን እናስተካክል የሚል መሆኑን ኢንጂነር ይልቃል ጠቁመዋል፡፡

በሰላም ተጀምሮ በሰላም የተጠናቀቀ ሰላማዊ ሠልፍን የፖለቲካ ንግግር በማሳመር ሕዝብን ለማሸማቀቅ መሞከር የገዥው ፓርቲ ድርጊት ብቻ ሳይሆን የአምባገነን መሪዎች ባህሪ በመሆኑ፣ ‹‹አትነሳም ወይ›› የሚለውን መዝሙር ሁሉም ወጣት እንዲያዳምጥና ሁሉም ከተኛበት ተነስቶ ለመልካም ዓላማ መሠለፍ እንደሚገባው ገልጸዋል፡፡ (ዘገባና ፎቶ ምንጭ፤ ሪፖርተር)

Filed Under: News Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

Recent Posts

  • ለሱዳንና ኤርትራ ሲከራከሩ የነበሩት አበባው ባለመመረጣቸው “በጣም ተድጃለሁ” አሉ June 26, 2026 12:29 am
  • “ትህነግ ወደ ዓለምአቀፍ ወንጀለኛነትና አሸባሪነት እየተምዘገዘገ ነው” June 25, 2026 01:00 am
  • አሜሪካ በሕገወጡ ትህነግ አመራሮች ላይ ጠንካራ የቪዛ እገዳ ጣለ June 18, 2026 10:29 am
  • እንደ ሌሊት ወፏ የሚንቀሳቀሰው ኢህአፓ/ትብብር   June 18, 2026 09:36 am
  • የታርጋ ጫጫታ June 15, 2026 05:16 pm
  • ፋንታኹን ዋቄ ከአሜሪካ የሃይማኖት እልቂት አወጁ June 15, 2026 02:12 am
  • ሕገወጡ ትህነግ ወጣቶችን ለዳግም ዕልቂት እያሰናዳ ለፈረንጆች “ኢትዮጵያን አውግዙልኝ” እያለ ነው June 11, 2026 12:57 am
  • በሐዘንና ግልፅ ደብዳቤ ስም የተሸፈነ የድህረ ምርጫ ሀገር የማተራመስ ስትራቴጂ June 10, 2026 12:19 am
  • የጽምዶ ልክፍት June 9, 2026 12:49 am
  • ገዳዩ ማነው? አስገዳዩስ ማነው? June 5, 2026 02:37 pm
  • ጽንፈኝነት ግን በኢትዮጵያ ምድር ፈጽሞ ቦታ የለውም! June 5, 2026 01:47 pm
  • የትብብሩ “ብናሸንፍም ፓርላማ አንገባም” መግለጫ “ወንበር ስታጡ ነው” የሚል ከፍተኛ ተቃውሞ አስነሳ June 4, 2026 12:04 am
  • አዲሱ የትራምፕ የምርጫ መመሪያ፡ የአሜሪካ ዲፕሎማቶችን አፍ ያስዘጋ፤ ተቃዋሚዎች ተስፋ ያስቆረጠ June 3, 2026 08:50 pm
  • “ኢህአፓ ከምርጫው በኋላ ይሰነጠቃል” May 29, 2026 07:07 pm
  • ሪፖርተር፡ “ስውር ተልዕኮ” – በከባድ ወንጀል ሊከሰስ May 6, 2026 11:55 pm
  • የፋኖ ኃይል በደረሰበት ጉዳት ሃምሳ ሺህ የሚጠጋ ትጥቅ ጥሎ ጠፋ April 29, 2026 02:27 pm
  • አዲሱ የቴድሮስ ካሳሁን 888 ኮድ፤ እንደ 666?! April 15, 2026 05:53 am
  • ምኑ ነው ያሳቃችሁ፤ ያስደሰታችሁ? April 2, 2026 10:52 am
  • የጀዋር መሃመድ የፖለቲካ ማንነት እና የባዕዳን ተልዕኮ April 2, 2026 10:16 am
  • ከግብፅ በዳያስፖራ ትርምስ ጠማቂዎች በኩል ፋኖ ወደ አዲስ አበባ የላከው “ስጦታ” March 27, 2026 09:14 am
  • “ሰላማዊ ታጋዮቹ” እነ ልደቱ ከአራጁ ሸኔ ጋር ተጣምረዋል March 25, 2026 01:04 pm
  • ጸረ-ኢትዮጵያዊ የሆነው የሪፖርተር አዘጋገብ March 19, 2026 11:54 am
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ የኦሮሚያ የልማት ድርጅቶች March 18, 2026 10:48 am
  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
Copyright © 2026 · Goolgule