• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

በሰላማዊ ሠልፉ ሰማያዊ ፓርቲና መንግሥት እየተወዛገቡ ነው

June 6, 2013 08:09 am by Editor Leave a Comment

ሰማያዊ ፓርቲ ከአንድ ወር በፊት በጠራውና ባለፈው እሑድ የተደረገውን ሰላማዊ ሠልፍ መንግሥት ሲያወግዝ፣ ሰላማዊ ፓርቲ ደግሞ የመንግሥት ውግዘት በተቃውሞ የተነሳውን ሕዝብ ከማሸማቀቅ ባለፈ የሕግ ድጋፍ እንደሌለው እየገለጸ ነው፡፡

ሰማያዊ ፓርቲ ሚያዝያ 29 ቀን 2005 ዓ.ም. ባስተላለፈው የሰላማዊ ሠልፍ ጥሪ፣ ግንቦት 25 ቀን 2005 ዓ.ም. በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጐች ወጥተው ተሰተውለዋል፡፡ አራት ኪሎ ቀበና አካባቢ ከሚገኘው የሰማያዊ ፓርቲ ጽሕፈት ቤት መነሻውን ያደረገው ሰላማዊ ሠልፉ በአራት ኪሎ፣ በፒያሳና በቸርችል ጐዳና አድርጐ ኢትዮ ኩባ የወዳጅነት መናፈሻ ደርሶ፣ እስከ ቀኑ ስምንት ሰዓት ድረስ የተለያዩ መፈክሮችንና ተቃውሞዎችን በመንግሥት፣ በመንግሥት መገናኛ ብዙኅንና በአንዳንድ የግል መገናኛ ብዙኅን ላይ አሰምተዋል፡፡

ሠልፈኞቹ ለመንግሥት ካቀረቧቸው ጥያቄዎችና መፈክሮች መካከል፣ ‹‹ዜጐችን ማፈናቀል የዘር ማጥፋት ወንጀል ነው፡፡ የህሊናና የፖለቲካ እስረኞች በአስቸኳይ ይፈቱ፣ የመደራጀት መብታችን ይረጋገጥ፣ በኑሮ ውድነት የጐበጠው ትከሻችን እረፍት ያስፈልገዋል፣ ሕገ መንግሥትን የሚፃረሩ አፋኝ አዋጆች ይሰረዙ፣ የመንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ መግባትን አጥብቀን እንቃወማለን፣ የሙስሊም መፍትሔ አፈላላጊዎች በአስቸኳይ ይፈቱ፣ ለፍትሕና ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት መስፈን የሚታገሉ ጋዜጠኞች ይፈቱና አትነሳም ወይ አትነሳም ወይ . . . ወኔ የሌለው የአገረ ሸክም ነው፣ ውሸት ሰለቸን . . . ›› የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

በሰላማዊ ሠልፉ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት ዓለም አቀፍ የሕግ ባለሙያው ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለ ማርያም እንደተናገሩት፣ አንድ ሕዝብ የሚገባውን መንግሥት ሊያገኝ ይገባል (A people get a government deserved)፣ ሥርዓቱን በትግል መለወጥ ካልተቻለ በትግል የምትፈልገውን ታገኛለህ ብለው፣ በ1997 ዓ.ም. ለዲሞክራሲ ሥርዓት ብቁ መሆኑን ያረጋገጠ ሕዝብ ኢሕአዴግ የሚመራው ሥርዓት እንደማይገባው ገልጸዋል፡፡

ለኢሕአዴግ ሥርዓት መለወጥ ወጣቱ ትልቅ ሚና እንዳለው፣ ‹‹መሬት ላራሹ›› ብሎ በመነሳት ኅብረተሰቡን ቀፍድዶ ይዞት ከነበው የፊውዳል ሥርዓት በማላቀቅ ትግል ውስጥ፣ ግንባር ቀደም እንደነበረ የገለጹት ዶ/ር ያዕቆብ፣ ደሙን ገብሮ ከጨፍጫፊው ደርግ ያላቀቀን ወጣት ዛሬ ነጥፏል የሚባለው አባባል፣ ከሰው ተፈጥሮና ከእውነት ውጭ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

‹‹ሽብርተኞች እንደምን አደራችሁ›› በሚል ምፀታዊ ሰላምታ ንግግራቸውን በዕለቱ ያሰሙት የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንት ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ደግሞ፣ ‹‹ይኼ የወጣቶች ሠልፍ ምልክትና መንገድ ነው፤›› ካሉ በኋላ፣ የእስልምና መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴዎች፣ ጋዜጠኞችና የፖለቲካ እስረኞች እስካልተፈቱ፣ ተፈናቃዮች ካሳ ተከፍሏቸው ወደ ቀያቸው እስካልተመለሱ፣ ሙስና እስካልጠፋ፣ የኑሮ ውድነትና ሥራ አጥነት ተገቢው የፖሊሲ ማስተካከያ እስካልተደረገባቸው ድረስ ሰማያዊ ፓርቲ ትግሉን በአስተዋይነት እንደሚቀጥል አስታውቀዋል፡፡ ለዚህም መስዋዕትነት ሊከፈል እንደሚችል በማከል ገዥው ፓርቲ የተባሉትን እንዲያስተካክል የሦስት ወራት ጊዜያት መስጠታቸውንም ገልጸዋል፡፡ ‹‹አሁን ያለው ሥርዓት ታሪካችንን፣ ክብራችንንና የዕውቀት ችሎታችንን አይመጥንም፤›› ካሉ በኋላ፣ ሕዝብ የመጠየቅ መብት እንዳለውና መንግሥት መፍትሔ የመስጠት ግዴታ እንዳለበትም አክለዋል፡፡

ሰላማዊ ሠልፉ በሰላም ተጀምሮ በሰላም በመጠናቀቁ መንግሥትም ዕውቅና የሰጠው ቢሆንም፣ በተለይ መንግሥት የሠልፉን ዓላማና እንቅስቃሴ በሚመለከት ‹‹ሕገ መንግሥቱን የጣሰ›› ብሎታል፡፡

የኢሕአዴግ ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የጠቅላይ ሚኒስትሩ የሕዝብ አደረጃጀትና ተሳትፎ አማካሪ ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ለመገናኛ ብዙኅን በሰጡት ማብራሪያ፣ በሃይማኖት ሽፋን ሲካሄድ የነበረው የፀረ ሕገ መንግሥት እንቅስቃሴ ቀድሞውንም ስውር አጀንዳ የነበረው መሆኑን፣ ሰማያዊ ፓርቲ በጠራው ሰላማዊ ሠልፍ ላይ መገለጡን ተናግረዋል፡፡

ፓርቲው ሠልፉን ላልተገባ ተግባር ማዋሉን የተናገሩት አቶ ሬድዋን፣ የፖለቲካ አቋምን በሃይማኖት ሽፋን አድርገውና ቀላቅለው እንዲንቀሳቀሱ ማድረጉና በፍርድ ቤት የተያዘን ጉዳይ በሰላማዊ ሠልፍና በሁካታ ለማቆም የደረጉት እንቅስቃሴ፣ ሕገ መንግሥቱን የጣሰና ተገቢ አለመሆኑን አብራርተዋል፡፡

አገር እመራለሁ የሚል ፓርቲ ከአጀንዳዎቹ አንዱ የሚሆነው የሕግ የበላይነትን ማረጋገጥ መሆኑን የገለጹት አቶ ሬድዋን፣ የሕግ የበላይነት የሚረጋገጠው ደግሞ የፍርድ ቤትን ነፃነት በማክበር መሆን እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡

ሰላማዊ ሠልፍ የሚወጣለትና ፍትሕ ሊጠየቅለት የሚችል ሰው በፍርድ እንዳይጠየቅ ሲደረግ፣ ሠልፍ የማይወጣለትና ፍትሕ ሊጠየቅለት የማይችል ሰው ዝም ሊባል የሚችልበት አካሄድ፣ ለአገር ሰላም ሊያሰፍን እንደማይችልና የዜጐችንም መብት ሊያረጋግጥ እንደማይችል አስረድተዋል፡፡ ሐሳብን በጽሑፍም ሆነ በሰላማዊ ሠልፍ መግለጽ ሕገ መንግሥታዊ መብት በኢትዮጵያ የተከበረ መሆኑን፣ ነገር ግን በፖለቲካ ሽፋንነት የአክራሪነት አጀንዳን ማራመድ የሕገ መንግሥቱን ድንጋጌዎች የሚጥስ መሆኑን አክለዋል፡፡

መንግሥት በሰላማዊ ሠልፉ ተደናግጦ ነገሮችን ከማቃለልና ሕዝቡን በፖለቲካ ንግግር ከማሸማቀቅ በስተቀር፣ የሕግ ድጋፍ እንደሌለው የተናገሩት የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ሲሆኑ፣ የመንግሥት ንግግር ፖለቲካዊ መሆኑን የሚያሳየው የተሰላፊዎቹን ቁጥር በሁለትና በአንድ ሺሕ አሳንሶ ሲናገር መታየቱ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ሰማያዊ ፓርቲም ሆነ ሕዝቡ ሕገ መንግሥቱን እንዳልጣሱ የገለጹት ኢንጂነር ይልቃል፣ ‹‹ጀሃዳዊ ሀረካት፣ አኬልዳማ›› በማለትና የተለያዩ ሕገወጥ ሥራዎችን በሕግ በተያዙ ጉዳዮች ላይ በመሥራት በፍርድ ቤቶች ላይ ተፅዕኖ የፈጠረው ራሱ መንግሥት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ሰላማዊ ሠልፉ የመንግሥትን በሃይማኖት ጣልቃ መግባትን ለመከላከል፣ ዜጐች አመለካከታቸውን የማራመድ፣ የፈለጉትን ሃይማኖት የመከተልና የማምለክ ሕገ መንግሥታዊ መብታቸው እንዲከበር ለማድረግ መሆኑን የገለጹት ኢንጂነሩ፣ የእምነት ነፃነት የመጀመሪያውና የጋራ ነፃነት በመሆኑ ያንን የመጠየቅ መብት እንዳላቸው አውስተዋል፡፡

መንግሥት ይኼንን ክፍል ለምን ነካችሁ ማለቱ እንዳስገረማቸው አስረድተው፣ ፓርቲው መጠየቅ ያለበት ኅብረተሰቡ ያነሳውን ጥያቄ ባያነሳ እንደነበርም አክለዋል፡፡ ኅብረተሰቡ በመንግሥት ትልቅ በደል እንደደረሰበት ሲናገር፣ እንደ ሰማያዊ ፓርቲ መንግሥትም ማንሳት እንዳለበትና ግዴታው መሆኑን ፕሬዚዳንቱ ገልጸው፣ ፓርቲያቸው ማንኛውንም እምነት የማክበርና ፓርቲያቸውም ዜጎች የእምነት ሥርዓታቸውን እንዲያካሂዱ እንደሚፈቅድ አስረድተዋል፡፡

ሕዝብና መንግሥትን ከሁለት ዓመታት በላይ አጣልቶ የቆየንና እስካሁንም ለውጥ ያልታየበትን ንፁኃንን ሽብርተኛ ማድረግ የመንግሥትን ተዓማኒነት ከማሳጣት በስተቀር ሌላ የሚያመጣው ነገር እንደሌለ መንግሥት ሊገነዘብ እንደሚገባ አስረድተዋል፡፡

አገርን እንደሚመራ ፓርቲ ኢሕአዴግ መሥራት ያለበት ሕዝብንና መንግሥትን የሚያቀራርብ ሥራ እንጂ፣ ማላገጥና ንግግር ማሳመር የሚያዋጣው እንዳልሆነ ኢንጂነር ይልቃል አስረድተዋል፡፡

‹‹ኢትዮጵያ ትልቅ ችግር ላይ ነች›› የሚሉት ፕሬዚዳንቱ የኑሮ ውድነቱ ሰማይ መድረሱን፣ ሙስና ተቋማዊ መሆኑን፣ የታሳሪዎች ብዛትና ያላግባብ የሚፈናቀሉ ዜጐች ከምንም በላይ ማሳያ መሆናቸውንና ዓለም ሁሉ ያወገዘው፣ ኢትዮጵያውያን በነፃነት የመነጋገር ሕገ መንግሥታዊ መብታቸውን ገፎታል ያሉት የፀረ ሽብርተኝነት ሕጉም ሌላው ችግር መሆኑን አክለዋል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲም ለመንግሥት የሚያቀርበው ጥያቄ እነዚህን ችግሮች ተመካክረን እናስተካክል የሚል መሆኑን ኢንጂነር ይልቃል ጠቁመዋል፡፡

በሰላም ተጀምሮ በሰላም የተጠናቀቀ ሰላማዊ ሠልፍን የፖለቲካ ንግግር በማሳመር ሕዝብን ለማሸማቀቅ መሞከር የገዥው ፓርቲ ድርጊት ብቻ ሳይሆን የአምባገነን መሪዎች ባህሪ በመሆኑ፣ ‹‹አትነሳም ወይ›› የሚለውን መዝሙር ሁሉም ወጣት እንዲያዳምጥና ሁሉም ከተኛበት ተነስቶ ለመልካም ዓላማ መሠለፍ እንደሚገባው ገልጸዋል፡፡ (ዘገባና ፎቶ ምንጭ፤ ሪፖርተር)

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: News Tagged With: Right Column - Primary Sidebar

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm
  • የተመሠረተው የፋኖ አደረጃጀት ዋነኛ ዓላማው ድርድር መሆኑ ተነገረ May 14, 2025 11:07 pm
  • ከፍተኛ የፋኖ አመራሮች መገደላቸው ተነገረ May 6, 2025 10:40 pm
  • ሃይማኖትን ለተራ የፖለቲካ ሸቀጥ ማዋል ውርደት ነው April 24, 2025 12:43 am
  •  የኬሪያ ኢብራሒም ኑዛዜ “ብትንትናችን ወጥቷል” April 22, 2025 12:08 am
  • ለወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዞን አመራሮች ወታደራዊ ሥልጠና ተሰጠ April 16, 2025 11:44 pm
  • ዓቅም እንደሌለው የገመገመው ሻዕቢያ ፊቱን ከጦርነት ወደ ዲፕሎማሲ እያዞረ ነው   April 15, 2025 12:32 am
  • “አንድ የፋኖ ተቋም (የእስክንድር) ተመሥርቷል፤ ሌሎቹ ደግሞ እንዲሁ አንድ ተቋም መሥርተው ወደዚህ ይመጡ” አበበ ጢሞ April 11, 2025 12:07 am
  • መለስ (ለገሰ) ዜናዊ – ተዋርዶ ያዋረደን! April 9, 2025 10:28 pm
  • የተከዜ ዘብ: የሉዓላዊነት መጠበቂያ April 8, 2025 11:49 pm
  • አዲስ አበባ አስተዳደር የሪፖርተርን የተዛባ መረጃ ኮነነ፤ ሕጋዊ እርምጃ እወስዳለሁ አለ April 8, 2025 10:06 pm
  • ሀሰተኛውን የሪፖርተር ዘገባ ንግድ ባንክ በጽኑ ተቃወመ፤ እርማትም ጠየቀ April 8, 2025 09:48 pm
  • “ኦሮሚያ ላይ ወይም ሌላ ቦታ ላይ ስታደርገው ከነበረ ትግራይ ወስጥም የማታደርግበት ምንም ምክንያት አይኖርህም” ነው ጌታቸው ረዳ April 7, 2025 10:22 pm
  • “TPLF’s belief in a strong federal government was always tied to its own dominance in Addis Ababa” April 7, 2025 10:15 pm
  • Counter-Video by EBC Challenges EBS Broadcast, Sparks Public Outcry Over Alleged Misinformation March 31, 2025 02:36 am
  • የኤሊያስ መሠረትን ፌክ መረጃ ማን ያጋልጥ? February 19, 2025 06:00 pm
  • አዘርባጃን፡ የሻዕቢያን ሸምቀቆ ማጥበቂያ?! February 19, 2025 12:29 am
  • የአሜሪካ ድምፅ/ቪኦኤ ይዘጋ ተባለ  February 12, 2025 03:37 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule