• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ሽብርን በማሸበር!!

April 23, 2015 08:14 am by Editor 3 Comments

* ሕዝብ ዋስትናና መተማመን አጥቷል

ረቡዕ ዕለት ኢህአዴግ በጠራው ሰልፍ ዜጎች ስሜታቸውን ሲያንጸባርቁ የተሰጣቸው ምላሽ ሽብርን በአሸባሪነት አመጣጥኖ የመመለስ አይነት እንደሆነ ተጠቆመ፡፡ የሰላማዊ ሰልፉ አጠቃላይ ገጽታና የሕዝብ ስሜት በአገሪቱ የዋስትና ማጣት ስሜት እየገዘፈ መሄዱን የሚያሳይ ሆኗል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ሊታረድ ነው፤ በሰሜን አሜሪካ የሥራ ጉብኝት እያደረጉ ባሉት ይልቃል ላይ እዚያው እንዲቀሩ ተጽዕኖ ይደረጋል ተብሏል፡፡

በአይሲስ የታረዱትና የተረሸኑትን “ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን እያጣራሁ ነኝ” ሲል የነበረው ኢህአዴግ እንዴት እንዳጣራ ለሕዝብ ባያሳውቅም ወዲያው ሕዝባዊ ለመሆን በመመኘት በአገሪቷ ላይ የሐዘን ቀን ከማወጅ በተጨማሪ ሕዝቡ ሰላማዊ ሰልፍ እንዲወጣ ጥሪ አድርጎ ነበር፡፡ አንድ የጎልጉል አስተያየት ሰጪ “ሕዝቡ ለ24 ዓመታት በሐዘን ላይ ነው ሦስት ቀንማ ምን አላት” በማለት እንደተሳለቁት የተሰጠውን ትዕዛዝ ተከትሎ ሕዝቡ ገና ከጠዋቱ ጀምሮ ተንቀሳቅሷል፡፡ በየቦታው የኢህአዴግ ካድሬዎችና ፖሊሶች መሰለፍ የሚገባውን ከማይገባው ለመለየት ሙከራ ቢያደርጉም በእጅጉም አልተሳካላቸውም፡፡

ይህንን ሰላማዊ ሰልፍ ከሕዝቡ በተጨማሪ ኢህአዴግ የደፈነባቸውን የፖለቲካ ምህዳር በራሳቸው እያሰፉ የሚንቀሳቀሱት ጥቂት የተቀናቃኝ ፓርቲዎች ድጋፍ ሰጥተውታል፡፡ መድረክ እና ሰማያዊ ፓርቲ ሰልፉን እንደሚያከብሩ ድጋፍም እንደሚሰጡ በይፋ ባወጡት መግለጫዎች አስታውቀው ነበር፡፡ ይህም በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚደረገውን ሽብር የሚቃወሙ መሆናቸውን ለሚያሸብራቸው ኢህአዴግ በአገራዊ አጀንዳ ላይ አብረው እንደሚቆሙ ኅብረት ያሳዩበት እንደሆነ በብዙዎች ተስተውሏል፡፡

ይሁን እንጂ ሰልፉ ኢህአዴግ ቀደም ሲል በቀላጤው ሬድዋን አማካኝነት የሞቱት “ኢትዮጵያውያን ስለመሆናቸው” ዕውቅና ነፍጎ በሰጠው መግለጫ የተቆጣው ሕዝብ የሰልፉን ዓላማ ኢህአዴግ ከተመኘውና ከፈለገው ውጪ አድርጎታል፡፡

ከለቅሶ ቤት ጀምሮ “መንግሥትን አንፈልግም” በማለት ቁጣ የተሰነዘረ ሲሆን አብዛኞች ግን “መንግሥት የለንም” ሲሉ ድርብ ሃዘናቸውን ገልጸዋል፡፡

ገዳዩ ባለካራው አሸባሪ ድርጅት ለፈጸመው ወንጀል ይሉኝታ ሳይዘው እንደ ታላቅ ገድል በቪዲዮ አስደግፎ ሲያቅራራ ዓለም ምስሉን ባደባባይ አይቷል፡፡ ሚዲያዎችም ተቀባብለውታል፤ መንግሥት ነን ብለው የተቀመጡት እነሬድዋን እንደ አንድ ሰው ሚዲያዎችን ተከታትለው መረጃውን አግኝተውታል፡፡

ፎቶ Addis Fortune
ፎቶ Addis Fortune

በኢህአዴግ ቋንቋ “ህገወጥ” የሚባሉት ሥራ ፈላጊዎች ድንበር አቋርጠው ሲወጡ ህጋዊ የጉዞ ሰነድ የላቸውም፡፡ ኢህአዴግ በሊቢያ የቅርንጫፍ ጽ/ቤት የለውም፡፡ አፈቀላጤውና “የፌስቡኩ ሚ/ር” ዶሮ እንኳን የሞተች ሳይመስላቸው “እውነት ኢትዮጵያውያን ሞተው እንደሆነ እናጣራለን” በማለት የተናገሩት ከካራም በላይ የሕዝብን ስሜት ያረደ ስለመሆኑ አብዛኞች ይስማማሉ፡፡ የረቡዕ ተቃውሞና ቁጣም ብዙ የተከማቹ መነሻዎች ቢኖሩትም አስኳሉ ጉዳይ ግን ክህደቱ እንደሆነ ይታመናል፡፡

“ያገር አንበሳ የውጭ ሬሳ”፣

“እግዚአብሔር ነው ለእኛ ኃይላችን አንመካም በጉልበታችን”፣

“ደማችን ይመለስ፣ ይታፈስ”፣

“አቤት ቆሻሻ”፣

“አይሲስ በካራ እናንተ በዱላ”፣

“አትመጣም ወይ መንጌ አትመጣም ወይ”፣ …

የሚሉ መፈክሮችን በኢህአዴግ ቁልፍ የአስተዳደር ቦታዎች አጠገብ ሰልፈኞች ሲልፉ ማሰማታቸውና በተለይ “ደማችን ይታፈስ” ሲሉ የጮኹት ዛሬ የተወለደ መፈክር አይደለም፡፡ ኢትዮጵያውያን ስለ አሸባሪ ከመስማታቸው ውጪ አሸባሪ መሆኑ በታወቀ ድርጅት ኢትዮጵያ ጥቃት ደርሶባት አያውቅም፡፡ ዊኪሊክስ ምስጋና ይድረሰውና ማን አሸባሪ እንደሆነ፣ ማን እንደሚያፈነዳ፣ ማን አንደሚያስፈነዳ፣ ማን ቀጣሪ እንደሆነ፣ በግልጽ ታክሲ ውስጥ ማን ቦምብ እንደሚያፈነዳ በግልጽና ማስተባበያ ሊቀርብበት በማይችልበት መልኩ አስቀምጦታል፡፡ ሐቁ ይህ ይሁን እንጂ ኢህአዴግ ካዝናው በጎደለ ቁጥር ኢትዮጵውያንን እየማገደ ከአሸባሪዎች ጋር የገባው እሰጥ አገባ የሰላማዊ ነዋሪዎችን የዋስትና ስሜት ከድህነቱ ጋር አብሮ ሰልቦታል፡፡

ሚያዚያ 26፤ 2006ዓም (ሜይ 4፤ 2014) አንድነት በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ “ለሥራ ብለን አባል አንሆንም” እያሉ ያዜሙት ሰላማዊ ሰልፈኞች በገሃድ እንዳስታወቁት የስደቱ ምንጭ ድህነት ነው፡፡ ጥቂቶች ሲበሉ አብዛኞች የገንዳ ውስጥ ትራፊ እንኳን ስላረረባቸው ነው፡፡ መረራ ጉዲና እንዳሉት “የራበው ሕዝብ መሪዎቹን ይበላል” ነውና ነገሩ ይህ ሕዝብ ወደ በቀል ከመሄዱ በፊት ቢሳደብ በምን መስፈርት ጥፋተኛ ይባላል? አረመኔያዊ በሆነ ስሜት ሊቀጠቀጥና አስፋልት ላይ እንዲጎተት ይፈረድበታል? ስለምንስ በጅምላ ይታሰራል? እንዲህ ያለው ሽብርን ባሸባሪነት የመቃወም ስሜት ቁጣውን ያበርደዋል ወይስ ይጨምረዋል? ሕዝብ ስሜቱን እንዲገልጽ ተጋብዞ የተሰማውን ስሜት ሲገልጽ መቀጥቀጥና መጨፍጨፍ ካራን በዱላ የመቀየርና አይሲስ የሚለውን ስም ኢህአዴግ በሚለው ለውጦ ሕዝብን ከማሸበር በምን ይተናነሳል? ሕዝብን ለተቃውሞ ውጡ ብሎ ጋብዞ በጭስ እያፈኑ እንደ እባብ መቀጥቀጥ የቦታ ልዩነት ካልሆነ በስተቀር አዲስ አበባ ላይ የተቀጠቀጠው ሕዝብ በአሁኑ ጊዜ ሊቢያ ከታሰሩትና ከታገቱት በምን ይለያል?

ሁልጊዜ እንደሚባለው የማስተዋልና የሕዝብን ስሜት ጠብቆ የመጓዝ ነገር ለእኛ አገር እርም ሆኗል፡፡ ከዛሬ 24ዓመት ጀምሮ የሕዝብን ብሔራዊ ስሜት፣ ብሔራዊ ኩራት፣ ብሔራዊ ማንነት፣ የእምነት መከባበር፣ ኢትዮጵያዊ ጨዋነት ቀስ በቀስ ሥሩን እየበጣጠሰ በቂምና በቁርሾ በመተካት እዚህ ያደረሰን ኢህአዴግ ትላንትና የተመሠረተውን የሰማያዊ ፓርቲ ለዚህ ዓመጽ ተጠያቂ ማድረጉ ከፌዝ በላይ ፌዝ መሆኑን አብዛኛዎች ተናግረዋል፡፡ ሌሎች ፓርቲዎችን ቅርጫ ሲያደርገው እንደጸና የቀረውን የሰማያዊ ፓርቲን ኢህአዴግ ሊያርደው ቢላውን ስሎ መጨረሱን በቀላጤው አማካኝነት ይፋ አድርጓል፡፡ በአሁኑ ጊዜ የፓርቲው መሪ በሰሜን አሜሪካ በሥራ ጉብኝት ላይ በሚገኙት ይልቃል ጌትነት ላይ ተጽዕኖ በማድረስ እዚያው እንዲቀሩ የማድረጉን ሥራ ኢህአዴግ ከወዲሁ መጀመሪ ጎልጉል የደረሰው መረጃ ያመለክታል፡፡ ኢህአዴግ ተቀናቃኞቹን ከፊቱ በማራቅ የተካነ እንደመሆኑ እምቢ ያሉትን እስር ሲወረውር ሌሎችን አስፈራርቶ ወይም አበስ አድርጎ አገር ለቅቀው በመሄድ ከፊቱ እንዲርቁ ሲያደርግ የኖረበት አሠራር ነው፡፡

መቼ እንደሚባረሩና ከኢህአዴግ ጋር ያላቸው የሥራ ጊዜ እስከ መቼ እንደሚዘልቅ ያላወቁት አቶ ሬድዋን ሰማያዊ ፓርቲን የማረዱን ሥራ አረጋግጠዋል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ በጉዳዩ ላይ መግለጫ እንደሚያወጣ የሚጠበቅ ቢሆንም የአፈቀላጤ ሬድዋን ዛቻ “በሉ ተብለው” የታዘዙበት እንደሆነ ግን ግልጽ ነው፡፡


ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው፡፡ ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (https://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን፡፡

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: News Tagged With: Full Width Top, Middle Column

Reader Interactions

Comments

  1. በለው ! says

    April 24, 2015 10:30 am at 10:30 am

    >>> ፲፱፺፯ ምርጫ የቅንጅትን አባላት !ሰነጠቀ ከፋፈለ አተራመሰ በተነ አጠፋ!በላ …ኢህአዴግ ከስሕተቱ ይማራል ሲል ዛተ…፳፻፯ ምርጫ ሲቃረብ አንድንትን እና የመኢአድን ፓርቲዎች በበርጫ ቦርድ ሜንጫ ጭዳ አድርጎ ከከተፈ በኋላ የቀድሞ ወዳጁን ኦነግን(ጮሌ ለታ) አስገባለሁ ሲል…ከዳር ያስቀመጠውን መድረክ አቅፋለሁ ሲል፣ የቀድሞ አጋሬን ኢዴፓን እንደ ሶስተኛ አማራጭ አሰልጥኜ አዘምታለሁ፣ ብሎ ሲፎክር ሰማያዊ ፓርቲ ብቻውን ሲፈረጋጥ አሁን በግላጭ ተገኘ፣ አይሲስ ንፁሃንን በባህር ዳርቻ አንገት ሲቀላ ወያኔ በአደባባይ ዜጋ በቆመጥ ሲፈነክት፣ የድሃ ልጅ ሲሰብር፣ ተፎካካሪውን ሲያስር፣ ከሜንጫ ቦር የተረፈውን ሰማያዊ ፓርቲ በግርግር በአደባባይ አገኘሁ አለ ወደ መሰውያው ሊቀርብ ነው።ግን ሰማያዊ ፓርቲ አባላት በኢህአዴግ በጠራው ሰልፍ አንዳትገኙ የሚል ትዕዛዝ ደርሷቸው ነበር? ለመሆኑ አድናቆትን ያተረፉት ተለጣፊ፣ አጋር፣ ተደጋፊ፣ ፓርቲዎች የትኞቹ ናቸው!?

    **ኢህአዴግ በቀበሌ መታወቂያ ላይ ብሄር መበፃፍ..በቋንቋ በነገድ በጎሳ፣በቅንድብ ላይ ጭረት በግንባር ላይ ጠባሳ በቀለም በፀጉር እያንዳንዱን በምልክት ከመያዙም ባሻገር በአረማመድ፣ በእግርና በእጅ እንቅስቃሴ ሁሉ ሕዝቡን እንደቁም ከብት አቧድኖታል!ፓርቲ እንጂ መንግስት፣ክልል እንጂ ሀገር ያልሆነች፣ ነዋሪና አኗኗሪ እንጂ ዜጋ ያልሆነ ትውልድ…ብሄር እንጂ ብሔራዊ ስሜት አልባ እንዲሆን ተፈርዶበት፣ መከራው ሲበዛ ቢሰደድም መሪና ተቆርቋሪ ሀሳቢ እረኛ የለውምና የአውሬ እራት ሆኖ ይቀራል..ከእሳት ወደ እረመጥ!
    *** ሰሞኑን ኢትዮጵያዊ ዜጋ ለመሆናቸው የሚያውቅላቸው የጠፋው ተገዳይ ወገኖች ኃላፊነቱን የሚወስደው ሰማያዊ ፓርቲ ይላሉ አፈጮሌው ሬድዋን ሁሴን…”እንግዲህ ወገን በጭካኔ ባልሞተ የሀዘን የተቃውሞ ሰልፍ ባላስፈለገ”..በእርግጥ በሰማያዊ ፓርቲ የመልካም አሰትዳደር እጦት፣የሥራ ፈጠራ አለመሟላት፣አድልዎ፣ዘረኝነትና የሁለተኛ ዜግነት ስሜት ያደረባቸው ሁሉ የበይ ተመልካች፣ የመንገድ ዳር ችካል ከመሆን ሀገር ጥለው የጠፉት በሰማያዊ ፓርቲ ትዕዛዝ ነው ወይንስ ሀገሪቱን የሚመራው ሰማያዊ ፓርቲ ነበር? ኢህአዴግ በጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ፬ሚሊየን ህዝብ ከሚኖርባት አዲስ አባባ ከተማ የተገኘው በ፻ሺህ ብቻ ነው ሌላው የት ገባ? የወል አበል ስላልከፈለ ይሆን? ከእነዚህም ውስጥ በአብዛኛው በመንግስት ተቃውሞ ላይ ነበሩ። በፖሊስ በህብርት ተደበደቡ እንጂ ፓሊስ ይዘው የሚደበድቡም አልታዩም.. አርስ በእርሳቸው ሲሮጡ ተጋጭተው የተጎዱ ናቸው የሚለው አባራሪው የያዘው ቆመጥ ከጥጥ የተሰራ እንዳልሆነ ይታወቃል..በእርግጥ ይህ ሁሉ ህዝብ በኢህአዴግ እራሱ በጠራው ሰልፍ ላይ እንዲያምፅ ማድረግ አቅም ያለው ሰማያዊ ፓርቲ እድሉን ቢያገኝ ሀገር በሰላም ይመራል ብዙ ደጋፊ አለው ብሎ ኢህአዴግ እውቅና ሰጥቶታል ማለት ነው።
    “ያገር አንበሳ የውጭ ሬሳ”፣…በሁሉም ነገር ከአፍሪካ አንደኛ ከዓለም ሁለተኛ የሆነው ኢህአዴግ ተለጥጦ ያወራው ትርንስፎርሜሽን ግማሽ ሳይሳካ እንዲሁ ተጨፈረ!ላፍሪካና ለዓላም ምሳሌ የሆነው ሻዕቢያ ህወአት ሴት በመድፈር፣ባንክ በመዝረፍ፣ ቤተክርስቲአን በማቃጠል፣ታሪክ በመበረዝ፣ትውልድ በማፍዘዝ፣ ቅርሳቅርስ በማቃጠል ወደውጭ ሀገር በመሸጥ፣ሰው ከእነነፍሱ ገደል በመጨመር፣ሀፍረተ ሥጋ በማኮላሸት፣ ሴት እናቶች በመድኀኒት በማምከን፣ገድሎ በማርዳት ጎዝጉዞ በማፅናናት የተካነ ለመሆኑ ላለፊት ፵ዓመት አሳልፈነዋል ይህንንም ሌላው ሀገር በማድረጉ ይዝናናል እንጂ አያዝንም!። … መቶ እገላላሁ የሚለው ባልሽ..ሃምሳ እገላላሁ የሚለው ባልሽ ቅጠል ቢንኮሻከሽ ገደል ገባልሽ አሉ..“አይሲስ በካራ እናንተ በዱላ”፣ሕዝባችን ሲዋረድ ሲቃጠል ሲታረድ ኢህአዴግ ጫማ ጠራጊ የድሃ ልጅ ሆድና ችንቅላት በእርግጫ…አሮጊት ሴት ሕፃናት ላይ ይደነፋል!!እንደ እንስሳ መስተዋት ወስጥ ተደብቆ ያላዝናል! “አትመጣም ወይ መንጌ አትመጣም ወይ”፣ …ለመሆኑ እነኝህ ወጣቶች በኢህአዴግ ዘመን ተወልደው ያደጉ አደሉምን የድሮው ዘመን እንዴት ናፈቃቸው? ኢህአዴግ ታሪክ ቢፅፍም የነበረን ቢያቃጥልም ታሪክ ከውጭ ሰምተው አደጉ ይሆን ባለፉት ፳፬ዓመት ኢትዮጵያውያን በውጭ ያለን ክብርና የድሮው እንዴት ነበር? ባለቤቱን ካልናቁ…ማለት ይህ ነው። በእርገጥ መንግስቱ ቢኖር ደቡብ አፍሪካና የሊቢያ አምባሳደሮች ፸፪ ሰዓት በላይ ኢትዮጵያ ውስጥ ያድሩ ነበር? በእርግጥ የድሮ ፓሊስና ወታደር ለሀገሩ ነው ለግለሰቦች ሥም ለሆዱ ያደረ ነበር? በእርግጥ ለጣሊያን፣ ለሳውዲያ ዓረቢያ፣ ለደቡብ አፍሪካ፣ለሊቢያ ለግብፅ የወገኑ ሊበቀሉን፣ ሊያፈርሱን፣ከወስጥ የሚያባርሩና ቀድመውም የሚዘርፉ፣ የሚደርፍ፣ሩ የሚያሻሽጡ፣ ለግድያ የሚተባባሩ፣ በሀገር ውስጥ በጭራሽ ጅግና እዳይፈጠር ተግተው የሚሰሩ ቡድኖች፣ ከውስጥ እያባሉና አጋጣሚውን ጠብቀው ዜጋ ለመግደል የተዘጋጁ ባንዶች በፖሊስ ሠራዊቱ ውስጥ እንደሌሉ ምን ማረጋገጫ አለን!?በዚህ አጋጣሚ ግን ለእኛ የሞቱ ተጠቅላይ ሚ/ር በጥቁር መነፅር ተከልለው፣ በኪራይ ጥቁር ልብስ፣ ቤተመንግስት ንፍጥና ለሃጫቸውን እያዝረከረኩ ሲያቆሽሹ ነበሩ፣ ልመታዊ አርቲስቶች፣ ጋዜጠኞች፣ የፓለቲካ በታኞች፣ ኢንቤስተሮች፣ ካድሬዎች፣ታዋቂዎች ግን አላዋቂዎች ምሁራን፣ በከፍተኛና መካከለኛ፣ በአነስተኛና ጥቃቅን ትቅማጥቅም የተለከፉ ሁሉ የት ሄዱ አይ የተውሶ እንባ ደረቀ ወይንስ የአድር-ባይ ፣ የሆድ-አደር! እንባ ለእውነተኛ ዜጋ አይባክንም!? ወይንስ በወያኔ ሥልጠና እየወሰዱ ልምምድ እያደረጉ ይሆን!ለሁሉም ግዜ አለው ያነባሉ.. ለሰማያዊ ፕርቲ አባላት የታሰበው ካራ ይደንዝ! ኢህአዴግ በልቶ ከሚያባላ ሥራ ፈጥሮ ትውልዱ ሠርቶ፣ ሸምቶ፣ አብስሎ፣ የሚበላና የሚካፈል ትውልድ ይሁን አሜን።!!!

    Reply
  2. ዮናታን መኳንንት says

    May 2, 2015 05:48 pm at 5:48 pm

    በቦታው ለነበረ አካል እንዲህ ነው እንዲያ ነው ብሎ ለማጭበርበር መሞከር ተገቢ አይመስለኝም። ጥያቄያችሁ በፊትም ስትሉት እንደነበረ ስልጣን አካፍሉን ጥያቄ በጉልበት ህዝብን ከህዝብ ጋር በማጋጨት ደመረ እንዲፈስ በማድረግ ህልማችሁን እውነረ ለማድረግ እንደሆነ ሩጫችሁ በአሁኑ ጊዚ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ባንኖባችኃል። ስለዚህ ባትደክሙ ጥሩ መሰለኝ!!!በተረፈ ግን ሰላማዊ ሰልፉ ላይ እኛም ነበርን የነበረው ግን እናንተ እንደምትሉት አይደለም በትክክል ተልዐረኮ የናንተን ወስደው የመጡ ጥቂት ወጣቶች ለብቻ ሰብሰብ ብለው ሲያውኩ ሌላውንም ሲረብሹና ስርዓት አስከባሪው አጠገባቸው ቆሞ ዘም ብሎ እየጠበቀ ነበር ነገር ግን ተልዕኮ ስላላቸው የሚተላለፈውን መልዕክት አናዳምጥም ነገር ግን ሰብረን ካልሄድን ወደ ውስጥ ካልበጠበጥን ነው የነበረው ግርግሩ ይህ ደግሞ ማንም እዚያ የነበረ ድፍን የአአ ህዝብ በላኪው ተቃዋሚ ተቃውሞውን አሰምቶ የተመለሰበት ሰልፍ ነው ያየነውና በእውነት ሽማግሌው አሮጊቶቹም በዚህ ተቃዋሚ ንቀት ጉዳት በጥቂት ወጣቶች ደርሶባቸው እየተራገሙ ወደ ቤት ተመለሱ። እውነቱ ይህ ነው

    Reply
  3. shimels says

    May 21, 2015 03:44 pm at 3:44 pm

    EPLE //TPLF/ they was doing like ISIS

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ባልደራስ የአገርን ደኅንነት አደጋ ላይ በመጣል ሊጠየቅ ይገባዋል ተባለ July 1, 2022 09:23 am
  • “ሚካኤል ችግኝ ነው። … ችግኝ ይተክላል” ቴዲ አፍሮ June 29, 2022 03:30 am
  • “የእኔን ልጆችና የልጅ ልጆች (22ቱንም) የቀበርኩት እኔ ነኝ” አቶ መሀመድ የሱፍ ከምዕራብ ወለጋ June 28, 2022 01:07 pm
  • የገዳ ሥርዓት እና የኦሮሞ ገዢ መደብ June 20, 2022 11:34 pm
  • “የወልቃይትን ጉዳይ ለድርድር የማናቀርበው ቀይ መስመራችን ነው” ርዕሰ መስተዳድር ይልቃል June 12, 2022 07:09 pm
  • የሰሜን ምዕራብ ዕዝና የአማራ ልዩ ኃይል ተከዜ ክፍለ ጦር ዕውቅናና ሽልማት ተሰጣቸው June 12, 2022 06:21 pm
  • ሀገር በቀል ባህላዊ የግጭት አፈታቶችን በተገቢው በመጠቀም ዘላቂ እርቅና ሰላምን ማምጣት ይቻላል June 12, 2022 05:40 pm
  • የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በገረጂና በቀበና ያስገነባቸውን የመኖሪያ አፓርትመንቶች አስመረቀ June 12, 2022 05:35 pm
  • በኦነግ ሸኔ ፈርሶ የነበረውና ወታደራዊ ጠቀሜታ ያለው ድልድይ ተጠግኖ አገልግሎት መስጠት ጀመረ June 10, 2022 09:13 am
  • ጃዋር በዳውድ ኢብሣ ቀይ መስመር ተሰመረለት June 8, 2022 12:59 pm
  • ወልቃይት: ቢመረንም ለመዋጥና ራሳችንን ለመመልከት እንሞክር June 8, 2022 11:53 am
  • እብድ ይሻለዋል እንጂ አይድንም፤ ሐጂ ጃዋር አሁን ለምን ብቅ አለ? June 8, 2022 05:59 am
  • ሕዝብ ድምፅ የነፈጋቸው “ፓርቲዎች” የሽግግር መንግሥት ይቋቋም አሉ June 7, 2022 01:11 am
  • “አድጌ እንደናንተ መሆን እፈልጋለሁ” June 5, 2022 06:58 pm
  • በሳምንት ለ100 ያህል ሕሙማን አገልግሎት የሚሰጥ የኩላሊት ዕጥበት ማዕከል ሥራ ጀመረ May 30, 2022 02:20 am
  • የጥቁር አንበሳ ዕጩ መኮንኖች (ካዴቶች) ተመረቁ May 29, 2022 04:01 pm
  • “ኢትዮጵያን መንካት አይቻልም!!” በሚል ቁጭት ነው እየሠራን ያለነው May 29, 2022 01:04 pm
  • “ከሞፈርና ቀንበር ወደ ትራክተር” በሚል መርህ ለአማራ ገበሬዎች የግብርና ሜካናይዜሽን ተሰጠ May 29, 2022 02:02 am
  • ኢትዮ 360 “የወያኔ፣ የጁንታ ሚዲያ ነው” – ባለከዘራው ጄኔራል May 27, 2022 02:51 am
  • “እኛ የምናውቀው ነገር የለም፤ የሚያጣሉን ፖለቲከኞች ናቸው” የአማራ ወዳጃቸውን አደራ ቤት የመለሱ የቅማንት ተወላጅ May 27, 2022 01:40 am
  • ትግራይን አገር እናደርጋለን፤ “በውይይት እና በጦርነት” ሁሉንም ጉዳይ እንቋጫለን – የወንበዴው መሪ ደብረጽዮን May 26, 2022 09:18 am
  • “ሁለቱ የምዕራብ ዕዝ ተዋጊ ዶክተሮች” May 26, 2022 08:19 am
  • ወደ ትህነግ ሊተላለፍ የነበረ አምስት ሚሊዮን ብር ከ20 ተጠርጣሪዎች ጋር ተያዘ May 25, 2022 01:57 am
  • የጦርነቱ ስትራቴጂያዊ እውነታዎች May 19, 2022 09:37 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2022 · Goolgule