
ሠራዊታችን እንደ አገር ሊቃጣብን የሚችልን ማንኛውም ትንኮሳና ጥቃት በብቃት መመከት በሚያስችል የዝግጁነት ደረጃ ላይ እንደሚገኝ የሰሜን ምዕራብ ዕዝ ዋና አዛዥ ጀኔራል ጌታቸው ጉዲና ተናገሩ።
የትህነግ ቡድን ከጀሌዎቹ ጋር በማበር የከፈተውን አገር የማፍረስ እቅድ መከላከያ ሰራዊቱ በውስብስብ ሁኔታ ውስጥ ሆኖ ማክሸፍ መቻሉን ያስታወሱት ጀኔራል ጌታቸው ከዘመቻ በኋላ የተገኘውን አንፃራዊ ሰላም በመጠቀም ተቋሙ በሞራል፣ በሰው ሃይል፣ በብቃትና በማቴሪያል የተሟላና ግዙፍ ኃይል እንዲሆን ማድረግ ተችሏል ብለዋል።
ሠራዊታችን እያንዳንዷን ሰዓት በስልጠና ላይ በማዋል መቺና ድልን በአስተማማኝ መልኩ ማምጣት በሚችል ቁመና ላይ እንዲደርስ ማድረግ ተችሏል ያሉት ጄነራል መኮንኑ አገራችንን ለመድፈር በሚያስቡ አካላት ላይ መንግስት በሚያስቀምጠው አቅጣጫ መሰረት የማያዳግም እርምጃ እንደሚወስድ አሳስበዋል።
ተቋሙ በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያዊ የሆነ ሰራዊት የመገንባት ሂደቱን ያሳካና አገራዊ ፍቅርና ስሜት ያለው ሰራዊት የገነባ በመሆኑ ለቀጣይ የግዳጅ አፈፃፀም ስኬታማነት ድርሻው የጎላ መሆኑን ገልፀዋል ሲል የመከላከያ ሠራዊት መረጃ አመላክቷል።
በየትኛውም የኢትዮጵያ አካባቢ የሚነሳ እሳት እያንዳንዳችንን እንደሚያቃጥለን መረዳት ከኹሉም ኢትዮጵያዊ የሚጠበቅ ተግባር መሆኑን ጄነራል ጌታቸው ጉዲና ገልፀው የተለያዩ ምክንያቶችን መነሻ በማድረግ ለጁንታውና አጋሮቹ ድጋፍ በመስጠት አገራችን አደጋ ላይ እንድትወድቅ የሚሰሩ አካላት ቆም ብለው ማሰብ እንዳለባቸውም ጀኔራል ጌታቸው ጉዲና ተናግረዋል። (አዲስ ማለዳ)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply